Quantcast
Channel: አስተያየት
Viewing all 720 articles
Browse latest View live

የግል ባንኮቹ የትርፍ ዕድገታቸውን ማስቀጠል ችለዋል

$
0
0

በአገሪቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የግል ባንኮች በ2009 የሒሳብ ዓመት አፈጻጸማቸውን የሚያሳዩ ግርድፍ መረጃዎች፣ አሁንም በአትራፊነት መዝለቃቸውን ያመለክታሉ፡፡ 16ቱ የግል ባንኮች በጥልቅ ከ7.8 ቢሊዮን ብር በላይ ያተረፉ ሲሆን፣ ይህም ከቀዳሚው የሒሳብ ዓመት ጋር በንጽጽር ሲታይ ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ ብልጫ ያለው ትርፍ ማስመዝገባቸውን ያመላክታል፡፡ በቀደመው ዓመት ባንኮቹ አትርፈው የነበረው 6.4 ቢሊዮን ብር ነበር፡፡ እንደ ግርድፍ መረጃው ከ16ቱ ባንኮች ውስጥ ሦስቱ ከ2008 የሒሳብ ዓመት ያነሰ ትርፍ ያገኙ ቢሆኑም፣ የቀሪዎቹ 13ቱ የግል ባንኮች ያስመዘገቡት የትርፍ ዕድገት ጭማሪ አጠቃላይ የአገሪቱ የግል ባንኮችን ዓመታዊ የትርፍ መጠን  ዕድገቱን ይዞ እንዲጓዝ ማድረጉን ያሳያል፡፡

በሒሳብ ዓመቱ አሁንም ከፍተኛውን ትርፍ በማትረፍ ቀዳሚ የሆነው አዋሽ ባንክ ሲሆን፣ ከታክስና ከሌሎች ተቀናሾች በፊት ያስመዘገበው ትርፍ ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ዳሸን ባንክ ደግሞ ዘንድሮ ዓመታዊ የትርፍ መጠኑን ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ በማሳደግ ሁለተኛው የግል ባንክ ሊሆን ችሏል፡፡ በግል ባንኮች ዓመታዊ የትርፍ መጠን መረጃ መሠረት ለመጀመሪያ ጊዜ አንድ የግል ባንክ ከታክስና ከሌሎች ተቀናሾች በፊት ዓመታዊ ትርፉን ከአንድ ቢሊዮን ብር ማድረስ የተቻለው ባለፈው ዓመት ነው፡፡ ይህንንም ትርፍ ያስመዘገበው አዋሽ ባንክ ሲሆን፣ ዘንድሮ ደግሞ ዳሸን ባንክ 1.06 ቢሊዮን ብር በማትረፍ የትርፍ መጠኑን ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ማድረስ የቻለ ሁለተኛው ባንክ ሆኗል፡፡ ባንኩ ባለፈው የሒሳብ ዓመት ያስመዘገበውን የ987 ሚሊዮን ብር ጥቅል ትርፍ በ7.4 በመቶ በማሳደግ 1.06 ቢሊዮን ብር ማትረፍ ችሏል፡፡

እንደ ዓምናው ሁሉ ዘንድሮም ከአገሪቱ የግል ባንኮች ከፍተኛውን ትርፍ በማስመዝገብ ቀዳሚ የሆነው አዋሽ ባንክ የዘንድሮ የትርፍ መጠኑን ከ1.4 ቢሊዮን ብር በላይ አድርሷል፡፡ ዓምና 1.004 ቢሊዮን ብር ማትረፍ የቻለው ባንኩ ዘንድሮም የትርፍ መጠኑን በ43.7 በመቶ ወይም ከ439 ሚሊዮን ብር በላይ ብልጫ ያለው ትርፍ በማግኘት አሁንም ከግል ባንኮች ቀዳሚ መሆን መቻሉን ይኸው ግርድፍ መረጃ ያሳያል፡፡

ቀሪዎቹ ባንኮች በ2009 የሒሳብ ዓመት ያገኙት የትርፍ መጠን ከቀዳሚው የሒሳብ ዓመት ከ2.8 በመቶ እስከ 61 በመቶ የሚደርስ ጭማሪ ያለበት ትርፍ ማግኘታቸውን ይኸው የባንኮቹን የሥራ አፈጻጸም የሚያሳየው ግርድፍ መረጃ ያመለክታል፡፡

በበጀት ዓመቱ ከቀዳሚ የሒሳብ ዓመት ብልጫ ያለው ትርፍ በማግኘት ቀዳሚ የሆነው ወጋገን ባንክ ሲሆን፣ ከዓምናው 61 በመቶ ብልጫ ያለው ትርፍ በማግኘት የ2009 የሒሳብ ዓመት ከታክስና ከሌሎች ተቀናሾች በፊት ያገኘው ትርፍ 760 ሚሊዮን ብር ማድረስ ችሏል፡፡ በቀዳሚው ዓመት ከታክስና ከሌሎች ተቀናሽ ወጪዎች በፊት አግኝቶ የነበረው ትርፍ 472 ሚሊዮን ብር እንደነበር ይታወሳል፡፡ በተመሳሳይ ከወጋገን ባንክ ቀጥሎ የትርፍ መጠኑን በማሳደግ ሁለተኛው ባንክ ሆኖ የተቀመጠው አቢሲኒያ ባንክ ሲሆን፣ በ2008 የሒሳብ ዓመት አግኝቶ ከነበረው የትርፍ መጠን የ278 ሚሊዮን ብር  ብልጫ ያለው ትርፍ ማግኘት ችሏል፡፡ ባንኩ በ2008 ሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት አስመዝግቦት የነበረው የትርፍ መጠን 472 ሚሊዮን ብር ነው፡፡

ካለፈው ሒሳብ ዓመት ከ54.1 በመቶ ብልጫ ያለው ትርፍ ማስመዝገቡ የተገለጸው ሌላው ባንክ ደግሞ እናት ባንክ ነው፡፡ እናት ባንክ በ2008 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት 110 ሚሊዮን ብር ያተረፈ ሲሆን፣ በ2009 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት ያገኘው ትርፍ 169 ሚሊዮን ብር ደርሷል፡፡

ይህም የዘንድሮ ትርፍ በ56 ሚሊዮን ብር መጨመሩን ያሳያል፡፡ እንደ ግርድፍ መረጃው ከሆነ ከ16ቱ ባንኮች ዓመታዊ የትርፍ መጠናቸውን ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ማድረስ የቻሉ ሰባት ባንኮች ሆነዋል፡፡ እነሱም አዋሽና ዳሸን ባንኮች ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ በማትረፍ በቀዳሚነት ሲቀመጡ፤ ወጋገን፣ አቢሲኒያና ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ደግሞ ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፍ መቻላቸውን መረጃው ያሳያል፡፡ ኅብረትና ብርሃን ባንኮች ደግሞ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ትርፍ በማግኘት ተጠቃሽ ሆነዋል፡፡ በተለይ ብርሃን ኢንተርናሽናል ባንክ ባለፈው ዓመትም የትርፍ መጠኑን በከፍተኛ ደረጃ በማሳደግ የተጠቀሰ ሲሆን፣ በ2009 የሒሳብ ዓመትም ለመጀመሪያ ጊዜ ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ በማትረፍ ከቀዳሚዎቹ ሰባት ባንኮች አንዱ ሊሆን ችሏል፡፡

ብርሃን ባንክ በ2008 የሒሳብ ዓመት ከታክስና ከሌሎች ተቀናሾች በፊት አትርፎ የነበረው 364 ሚሊዮን ብር ሲሆን፣ በ2009 የሒሳብ ዓመት ደግሞ ትርፉን በ142 ሚሊዮን ብር በማሳደግ 506 ሚሊዮን ብር ማድረስ ችሏል፡፡

ከእነዚህ ሰባት ባንኮች ሌላ ዘጠኙ ባንኮች ከታክስ በፊት ያስመዘገቡት ዓመታዊ ትርፍ መጠን ከ75 ሚሊዮን እስከ 380 ሚሊዮን ብር ነው፡፡

ከቀደመው ዓመት ያነሰ ትርፍ በማስመዝገብ የተጠቀሱት ሦስት ባንኮች ደግሞ ዘመን፣ ደቡብ ግሎባል ባንክና የኦሮሚያ ኅብረት ሥራ ባንኮች ናቸው፡፡ 

Standard (Image)

አራት ዘመናዊ የአውቶብስ መናኸሪያ ዲፖዎች ሊገነቡ ነው

$
0
0

 

ከአዲስ አበባ የትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ ሊተገበሩ ይገባቸዋል ተብለው ከሚታሰቡ መሠረት ልማቶች መካከል አንዱ የሆነው፣ የተሽከርካሪዎች መናኸሪያና ከዚሁ ጋር የተቀናጀ አገልግሎት የሚሰጡ ማዕከሎች ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የከተማ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች የራሳቸው የሆነ የተሽከርካሪዎች መናኸሪያ ወይም ዲፖ የላቸውም፡፡ የተደራጀ የተሽከርካሪዎች ማሳረፊያ ያለው ድርጅት ካለ የአንበሳ አውቶብስ ድርጅት ቢሆንም፣ እያደገ ከመጣው የአውቶብሶች ቁጥር አንፃር እሱም በቂ የሆነ የተሽከርካሪዎች ማቆያና መናኸሪያ የለውም፡፡ በአውቶብሶች የትራንስፖርት አገልግሎት እየሰጡ ያሉ ድርጅቶች የተሽከርካሪዎች ማቆሚያ ሥፍራ የሌላቸው መሆኑ ደግሞ፣ በተቋማቱ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ራሱን የቻለ ተፅዕኖ እያሳረፈባቸው ስለመሆኑ በተለያዩ አጋጣሚዎች ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡ ይህንን ችግር በጊዜያዊነትና ለዘለቄታ ለመቅረፍ የትራንስፖርት ድርጅቶቹ የተለያዩ ዕርምጃዎችን እየወሰዱ ቢሆንም፣ ጊዜያዊ መፍትሔያቸው ግን ከወጪና ከእንግልት አላወጣቸውም፡፡ ከእነዚህ የትራንስፖርት ድርጅቶች ውስጥ በአዲስ አበባ ከተማ የሚታየውን የትራንስፖርትን ችግር ለመቅረፍና ለመንግሥት ሠራተኞች የትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅቶች የተቋቋመው የፐብሊክ ሰርቪስ ሠራተኞች የትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅት አንዱ ነው፡፡ ድርጅቱ የተደራጀ ጥገና አገልግሎት የሚሰጥበትም ማዕከል ስለሌለው በአገልግሎት አሰጣጡ ላይ የራሱ የሆነ ተፅዕኖ ስለማሳረፉም እየተነገረ ነው፡፡

በዋናነት ለመንግሥት ሠራተኞች በነፃ የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት ከተቋቋሙ የፐብሊክ ሰርቪስ ሠራተኞች ትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅት የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን አምባቸው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የተሽከርካሪዎች ማረፊያ የሚሆን ቦታ ያለመኖሩ ትልቅ ፈተና መሆኑን ነው፡፡

ድርጅቱ የሚያስተዳድራቸው አውቶብሶች በሙሉ ለማደሪያ የሚሆን ቦታ የላቸውም፡፡ ቀን ላይ ቋሚ የሆነ ማረፊያም ስለሌላቸው በየቦታው እየዞሩ ነው ማቆሚያ የሚያፈላልጉት፡፡ ማታ ማታም ቋሚ የማደሪያ ቦታ ስሌላቸው ተለያዩ ድርጅቶች ትብብር እየተጠየቁ እንዲያድሩ ይደረጋል፡፡ እንዲህ ባለው መንገድ ማደራቸው ደግሞ ደኅንነታቸውን ለማስጠበቅ አስቸጋሪ የሚሆንበት አጋጣሚ ይፈጥራል፡፡ ለተሽከርካሪዎች የሚደረግ ጥበቃም ቢሆን ፈታኝ ነው፡፡ ሹፌሮች ከሥራ በኋላ ተሽከርካሪዎችን የት እንደሚያቆሙ እንኳን ስለማያውቁ፣ በቦታ መረጣ ረዥም ጉዞ የሚጓዙ በመሆኑ ሥራቸውን አሰልቺ በማድረግ ጭምር እየፈተናቸው ነው፡፡

የመናኸሪያው እጦቱ የተሽከርካሪዎችን ደኅንነት ለመጠበቅ ፈታኝ ከመሆኑ ሌላ፣ ማረፊያ ቦታ ለማግኘት ከአንዱ የከተማው ክፍል ወደ ሌላው ሲጓዙ የሚያቃጥሉት ነዳጅ ለአላስፈላጊ ወጪ ስለመዳረጉም ይኼ ያገኘነው መረጃ ያስረዳል፡፡ እንዲህ ያለ የማቆያ ቦታ እጦት የፐብሊክ ሰርቪስ ድርጅትን የራሱ የሆነ የተሽከርካሪዎች ዲፖ ለማስገንባት ወደሚያስችለው ምዕራፍ እንዲሸጋገር እያደረገው ነው፡፡ ሥራውን  ለማቀላጠፍም የተሽከርካሪዎች በማኸሪያና ዴፖ መግባት ወሳኝ በመሆኑ፣ ይህንኑ እውን ለማድረግ የሚያስችለው እንቅስቃሴ ውስጥ ገብቷል፡፡

ከድርጅቱ የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው፣ በአሁን ወቅት ትልቅ ችግር እየሆነ የመጣውን የተሽከርካሪዎች ማረፊያ እጦት ለመቅረፍ ዘመናዊ የተሽከርካሪዎች ዴፖ ለመገንባት የሚያስችል የግንባታ ዲዛይን በማሠራት ላይ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርም ችግሩን በመገንዘብ በአዲስ አበባ ከተማ በአራት ቦታዎች ዘመናዊ መናኸሪያ ዴፖ ለመገንባት የሚያስችሉ ቦታዎች ለመሰጠት ፍቃደኛ በመሆኑ፣ የአራቱ ቦታዎች መረጣ ተጠናቅቆ ተከልሏል፡፡ ቦታዎቹም ጀሞ፣ ሸጎሌ፣ አቃቂና ሜክሲኮ አደባባይ አካባቢ ናቸው፡፡ ወደ ግንባታ ለመግባት በአሁኑ ወቅት የቦታዎቹን ባለቤትነት የሚያረጋግጥ የካርታ ሥራዎች ብቻ ይቀራቸዋል ተብሏል፡፡ እንደ አቶ ሰለሞን ገለጻም፣ አስተዳደሩ ለግንባታ የሚውሉትን ቦታዎች በመፍቀድ የተባበረ ሲሆን፣ በቅርቡም ካርታ ተሠርቶ ድርጅቱ እንደሚረከባቸው እምነት አላቸው፡፡ እነዚህ አራት ቦታዎች ላይ  የሚገነቡት ዘመናዊ ዴፖዎችን ዲዛይንና አጠቃላይ ግንባታውን ለማከናወንም ከግዙፉ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ጋር ውለታ መፈጸሙን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በኮርፖሬሽኑና በድርጅቱ መካከል በተደረሰው ስምምነት በአዲስ አበባ በአራት የተመረጡ ቦታዎች ሊገነባ የታሰበውን ልዩ መናኸሪያ ዲፖ የዲዛይን ሥራውንና  ግንባታውን አጠቃሎ ለመሥራት የሚያስችል ነው፡፡

የኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ኃይለ መስቀል ተፈራ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከፐብሊክ ትራንስፖርት ጋር በደረሰነው ስምምነት መሠረት የዴፖዎቹ ዲዛይን የተለያዩ አገልግሎቶችን ለመስጠት በሚያስችል መልኩ እየተሠሩ ሲሆን፣ የመጀመሪያው ደረጃ ዲዛይን ሥራውም ተጠናቋል፡፡ እንዲሠሩ የታቀዱት መናኸሪያዎች በተለመደው ዓይነት የመናኸሪያ አገነባብ የሚሠሩ ያለመሆኑን የጠቆሙት አቶ ኃይለ መስቀል፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቁ የፐብሊክ አውቶብሶች ዴፖ በሚሰጡት ዓይነት አገልግሎት ታሳቢ ተደርገው እንደሚገነቡ ተናግረዋል፡፡ እነዚህ ዴፖዎች ለተሽከርካሪዎች ማቆሚያነት ከሚሰጡት አገልግሎት በላይ ዘመናዊ የተሽከርካሪዎች ጥገና ለመስጠት የሚያችሉ ማሽኖችን የያዙ ይሆናሉ፡፡ የራሳቸው መካኒካል ወርክ ሾፖችንና የተለያዩ ማሽነሪዎች የሚኖራቸው ሲሆን፣ ትልልቅ የሚባሉና ተሽከርካሪዎችን በቀላሉ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ማንቀሳቀስ የሚችሉ ክሬኖች ጭምር የሚኖራቸው ናቸው፡፡ ዘመናዊ የትራንስፖርት አገልግሎትን ከመስጠት አኳያ እነዚህ ዴፖዎች እንደ ስምሪት ማዘዢያ የሚያገለግሉም ይሆናሉ፡፡ እነዚህ የተሽከርካሪዎች ዴፖዎች ለሌሎች ተመሳሳይ ዴፖዎች ሞዴል ሊሆኑ በሚችል ደረጃ የሚገነቡ እንደሚሆኑም ያገኘነው መረጃ ያስረዳል፡፡ አቶ ሰለሞንም ዴፖዎቹ ጋራዥ፣ የተሽከርካሪዎች እጥበት አገልግሎት፣ ሱፐርማርኬትና ለቢሮ አገልግሎት የሚውሉ ሕንፃዎችንም አካትተው የሚሠሩ ዘመናዊ ዴፖዎች ስለመሆናቸውና የሚሰጡት አገልግሎት ዘርፈ ብዙ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

እነዚህን ዘመናዊ የፐብሊክ ዴፖዎች ለመገንባት የተለያዩ አገሮችን ልምድ ለማየት እንደተሞከረ የጠቀሱት አቶ ኃይለ መስቀል፣ ለምሳሌ የቤጂንግ ከተማ የፐብሊክ ባስን ጠቅሰዋል፡፡ በፐብሊክ ባስ የሚሠሩት ዴፖዎች ለሌሎች ተመሳሳይ አገልግሎት ለሚሰጡ ተቋማት አገልግሎት የሚሰጡበት ዕድል ሊኖር እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡ የትራንስፖርት ማኔጅመንት ቅንጅት ይጠይቃል ያሉት አቶ ኃይለ መስቀል፣ አገልግሎቱን የሚሰጡ የትራንስፖርት ድርጅቶች በግለሰብ፣ በኩባንያም ሆነ በመንግሥት የተያዙም ቢሆን አገልግሎቱን የሚሰጡት ለሕዝብ ስለሆነ በቅንጅት መሥራት ስለሚኖርባቸው በሒደት ዘመናዊ ዴፖዎች ሌሎችም የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎችን በሚጠቅም ደረጃ የሚያገለግሉ ሊሆኑ ይችላሉ ብለዋል፡፡ የእነዚህ ዴፖዎች ሥራ መጀመር አሁን የሚታዩትን ችግር ከመቅረፍ አልፎ ድርጅቱ ካላስፈላጊ ወጪ እንዲድን ያደረገዋል ያሉት አቶ ሰለሞን፣ በዘመናዊ የትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጥ ረገድም ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡ እነዚህ የዴፖ ግንባታ ፕሮጀክቶች ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ ናቸው ተብሏል፡፡ አቶ ኃይለ መስቀል እንደገለጹት ደግሞ፣ ፕሮጀክቱ ብዙ አዳዲስ ነገሮችን ያካተተ ስለሆነ የግንባታ ወጪው ከሦስት እስከ አራት ቢሊዮን ብር ይፈጃል ተብሎ ይገመታል፡፡

የፐብሊክ ሰርቪስ ሠራተኞች ትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅት በአሁኑ ወቅት ከ410 በላይ በሚሆኑ አውቶብሶች አገልግሎት  እየሰጠ ሲሆን፣ ለመንግሥት ሠራተኞች በነፃ የሚሰጠው የትራንስፖርት አገልግሎት በቀን በአማካይ 70 ሺሕ ሠራተኞችን እያጓጓዘ ስለመሆኑ አቶ ሰለሞን ጠቅሰዋል፡፡

ሦስት ዋና ዋና ዓላማዎችን በመያዝ እየተንቀሳቀሰ ያለው ይህ ተቋም፣ የመንግሥት ሠራተኛውን በነፃ ማጓጓዝና በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚታየውን የትራንስፖርት ችግር ለመቅረፍ በተመጣጣኝ ዋጋ የታክሲ የትራንስፖርት አገልግሎት መስጠት በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ፡፡

የመንግሥት ሠራተኞችን በነፃ ከማስተናገድ ጎን ለጎን የከተማውን የትራንስፖርት ተጠቃሚ ለማገልገል የሚሰጠው የታክሲ አገልግሎት፣ በከተማዋ ያለውን የትራንስፖርት ችግር በማቃለል ረገድ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ አድርጎታል፡፡ ይህ የታክሲ አገልግሎት የሚሰጡት አውቶብሶች ሠራተኛውን ካደረሱ በኋላ ወዲያው የታክሲ አገልግሎት እንዲሰጡ በማድረግ ሲሆን፣ የተወሰኑ አውቶብሶች ደግሞ በሥራ መውጫና መግቢያ ሰዓት ላይ የታክሲ አገልግሎት  እንዲሰጡ በማድረግ ጭምር ነው፡፡ አገልግሎቱም 135 በሚሆኑ አውቶብሶች ይሰጣል ተብሏል፡፡

በታክሲ አገልግሎቱ የሚጠቀሙ መኪኖች ቁጥር እያደገ ሲሆን፣ በ2009 በጀት ዓመት ብቻ ከሦስት ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ተጓዦች የድርጅቱን የታክሲ አገልግሎት ማግኘታቸው ተገልጿል፡፡

Standard (Image)

የታክስ ግምቱና የአነስተኛ ነጋዴዎች እሮሮ

$
0
0

በብርሃኑ ፈቃደና በዳዊት እንደሻው

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን በደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋዮች ላይ ባስቀመጠው አዲስ የታክስ ምጣኔ ሳቢያ በአዲስ አበባ ከተማ አራቱም ማዕዘናት ከፍተኛ እሮሮ እየተደመጠ ይገኛል፡፡ በርካቶች በቀን ገቢ ግምት ስሌት እንዲሁም በዓመታዊ ሽያጫቸው መሠረት የተጣለው ታክስ  በየተጋነነ ነው በማለት፣ ቅሬታውን ለማቅረብ የክፍለ ከተማና የወረዳ ጽሕፈት ቤቶችን ሲያጨናንቁ ታይተዋል፡፡

ሰሞኑን በተፈጠረው በዚሁ የታክስ ግርግር ሳቢያ በርካታ ክስተቶች ተስተናግደዋል፡፡ በርካቶች ሲላቀሱ ታይተዋል፡፡ በየቀበሌው በድንጋጤ አቅላቸውን ስተው የሚዘረሩ ሰዎችም አልታጡም፡፡ ሪፖርተር በተጨባጭ ለማረጋገጥ ባይቻለውም በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 ውስጥ ነዋሪ የሆኑ ግለሰብ በቀን ግምት የሦስት ሺሕ ብር ታክስ ተጥሎባቸው ከድንጋጤ ብዛት መፀዳጃ ቤት ውስጥ ሞተው እንደተገኙ የአካባቢ ሰዎች ሲናገሩ የተመደጠ፣ የሰሞኑ የመነጋገሪያ ርዕሰ ጉዳይ ሆኖ ሰንብቷል፡፡

ወ/ሮ ራሔል ስጦታው 24 ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በምግብ ንግድ ሥራ የምትተዳደር ስትሆን፣ አምስት ጠረጴዛዎችና 17 ወንበሮችን በምትይዘው ‹‹ቁርስ ቤቷ›› በቀን ከ15 እስከ 20 እንጀራ በመሸጥ ላለፉት ሦስት ዓመታት ስትሠራ እንደቆየች ለሪፖርተር ገልፃለች፡፡ ወ/ሮ ራሔል እንደጠቀሰችው፣ እነዚህን ዓመታት ከሰዎች በመደበር የጀመረችውን ሥራ ለማደራጀትና ቤተሰቧን ለማስተዳደር ስትጣጣር ቆይታለች፡፡ እስካሁንም ገንዘብ ላበደሯት ሰዎች ዕዳዋን ለመመለስ በምትሯሯጥበት ወቅት፣ የቤት ኪራይ ስለተጨመረባት የንግድ ፈቃዷን በመመለስ ምግብ ቤቷን ለመዝጋት እየተዘጋጅ ባለችበት ወቅት አዲሱ የታክስ ዱብ ዕዳ እንደመጣባት ትናገራለች፡፡ በወር ስምንት ሺሕ ብር ኪራይ የምትከፍልበት ንግድ ቤት፣ ወደ 15 ሺሕ ብር ብር ጨምሯል በመባሏ ነበር ሥራውን ለማቆም የወሰነችው፡፡  

ወትሮውንም በወር ይህን ያህል የቤት ኪራይ እየከፈለች ስትሠራ የቆየችው የተበደረችውን ዕዳ መክፈል ግድ ስለሆነባት እንጂ፣ አቅሙ ኖሯት ሥራውን እንዳልገባችበት ገልፃለች፡፡ ከሰዎች 40 ሺሕ ብር ያህል ተበድራ፣ ሥራውን ስትጀምር የስድስት ወር ቅድሚያ ክፍያ መጠየቋ ነበር የመጀመሪያው ችግር፡፡ በብድር ካገኘችው ገንዘብ ላይ ቀናንሳ ብትከፍልም ሥራው የታሰበውን ያህል አልሆነም፡፡

በዚያም ላይ የኩላሊት በሽተኛ በመሆኗ እና እንደልቧ ጎንበስ ቀና ብላ መሥራት ባለመቻሏ፣ ሥራውን በአግባቡ ለማስኬድ መቸገሯን ጠቅሳለች፡፡ እንዲህ እየተፈተነች ባለችበት ወቅት፣ በዓመት 49 ሺሕ ብር የታክስ ዕዳ ሲመጣባት የምትጨብጠው፣ የምትይዝ የምትሆነው እንዳጣች እንባዋን እያዘራች ገልጻለች፡፡ በየዓመቱ 5,700 ብር ያህል ስትከፍል ብትቆይም ይህም ቢሆን ከአቅሟ በላይ ሆኖባት ስትፍጨረጨር መቆየቷን አስታውሳ፣ አዲስ የተጠየቀችውን የምትከፍልበት የሥራ እንቅስቃሴ እንደሌለ በመግለጽ አቤቱታ ማስገባቷንም ገልጻለች፡፡

‹‹እኔ ይህንን ያህል መክፈል አልችልም፡፡ ተቀጥሬም ሆነ እንደሌሎች ጓደኞቼ ስደት ሄጄ መሥራት አልችልም፡፡ በሽተኛ ነኝ ስላቸው እጄን ይዘው አስወጡኝ፡፡ የሚሰማን ሰው የለም፡፡ አታፍሪም ብትችይ አይደል እንዴ ይህን ያህል ጊዜ ስትሠሪ የቆየሽው? ካልቻልሽ ለምን በስድስት ወር ውስጥ አትዘጊውም ነበር፤›› እንዳሏት እሷም ‹‹ነገ የተሻለ እሠራለሁ በማለት የተሸጠው ተሽጦ የተረፈውን በልቼ ማደሬን እንጂ ትርፍ እስካሁን አላገኘሁም፡፡ እስካሁን የተሳካልኝ ነገር ቢኖር የነበረብኝን ብድር መመለስ መቻሌ ነው፤›› ያለችው ራሔል፣ ኑሮ ይባስ እየተወደደ፣ በመጣበት ወቅት ሁለት መንታ ልጆቿን ጨምሮ እናትና አባት የሌላቸው እህት ወንድሞቿን ለማስተዳደር ቀና ደፋ በምትልበት ወቅት እንዲህ ያለው ጉድ ያውም ከመንግሥት መምጣቱ ቅስሟን ከመስበር አልፎ፣ በሕይወት ተስፋ እንዳይኖራት ማድረጉን ጠቅሳለች፡፡ 

እንዲህ ያሉ ታሪኮች የተደመጡበት የዚህ ዓመት የታክስ ጉዳይ የሁሉም ሰው መነጋገሪያ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ በርካቶች በመንግሥት ላይ ብሶታቸውን እያሰሙ ይገኛሉ፡፡ ከስድስት ዓመታት በፊትም እንዲሁ ተመሳሳይ ቅሬታዎች በመንግሥት ላይ ሲሰነዘሩ እንደነበር ይታወሳል፡፡ የአሁኑን ይበልጥ አሳሳቢ ያደረገው ግን መንግሥት ባሻሻለው የታክስ ምጣኔ መሠረት ከታችኛው ክፍል ወደ ላይ መሔድ የሚገባቸው በርካታ ግብር ከፋዮችን ለማግኘት በማሰብ፣ የታክስ መሠረቱን የማስፋት ዕርምጃው አካል እንደሆነ አስታውቋል፡፡

በመሆኑም የደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋዮች ዓመታዊ የሽያጭ መጠን እስከ 500 ሺሕ ብር እንዲሆን በመደረጉ፣ በዚህ መደብ ውስጥ የሚገቡት ነጋዴዎች ምንም እንኳ የገቢ መጠናቸው ዝቅተኛ ነው ቢባልም መክፈል የሚገባቸው የታክስ መጠን ላይ የተደረገው ማሻሻያ ግን ከአቅማቸው በላይ መሆኑን በምሬት እያስተጋቡ ይገኛሉ፡፡

ሪፖርተር ስለዚሁ ጉዳይ ተዘዋውሮ መረጃ ካጠናቀረባቸው አካባቢዎች መካከል አንዱ ቦሌ ቡልቡላ ነው፡፡ በዚህ አካባቢ የሚገኙ አነስተኛ ነጋዴዎችም እንደሌሎቹ አካባቢዎች ሁሉ ‹‹ታክስ አንፈልም አላለንም፡፡ ለዓመታት ስንከፈል ኖረናል፡፡ የአሁኑ ግን ከሚታሰበው በላይ ቅጥ ያጣና ከምናገኘው ገቢ ጋር ፈጽሞ የማይመጣጠን ነው፤›› ያሉት በቦሌ ቡልቡላ በአነስተኛ መደብር ውስጥ ነጠላ ጫማና ሌሎችም የፕላስቲክ ውጤቶችን የሚሸጡት አቶ አበራ ተሰማ ናቸው፡፡  አቶ አበራም ሆኑ በርካታ የእሳቸው ብጤ ነጋዴዎች የጋራ ቋንቋቸው የተጣለው የገቢ ግምት የአካባቢውን እንቅስቃሴ ከግምት ውስጥ ያላስገባ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በዓመት 450 ብር ሲከፍሉ የነበረው የታክስ መጠን በአዲሱ ተመን መሠረት ከፍተኛ ጭማሪ እንዲኖረው በመደረጉ ተማረዋል፡፡

ጌሾና ብቅል የሚሸጡ፣ ጉልት የሚቸረችሩ፣ የ‹‹አርከበ ሱቅ›› በሚባሉት አነስተኛ መደብሮች ልዩ ልዩ ሸቀጦችን የሚነግዱ በጠቅላላው የታክስ ግመታው ከተጣለባቸው ከ150 ሺሕ የሚጠጉ ነጋዴዎች ውስጥ አብዛኛው በመንግሥት ላይ እሮሮውን እያሰማ፣ በየወረዳው ማመልከቻ ለመስገባት ሲጣደፉ ታይተዋል፡፡ ሆኖም አብዛኞቹ ከሦስት ወር በፊት ምላሽ እንደማያገኙ እየተነገራቸው፣ ጥቂት የማይባሉትም በአግባቡ የሚያስረዳቸው በማጣት መንገላታታቸውን ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡

የምሁራን ምልከታ

መንግሥት አብዛኛው ከታክስ መረብ ውጭ የሆነውን ነጋዴ ብቻም ሳይሆን፣ በታክስ ሥርዓቱ ውስጥ ተካቶም ተገቢውን ታክስ አልከፈለም ብሎ ባሰበው ክፍል ላይ የተከተለው አካሔድ ከግልጽነት ጀምሮ የአተገባበር ወጣ ገባነት እንደሚታይበት ሲገለጽ ይታያል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሕዝቡ እንዲዘጋጅበት የሚመጣው የታክስ ምጣኔ ድንገተኛ ከሚሆን ይልቅ ወቅቱን በጠበቀ መልኩ ካለው የኑሮ ውድነት ጋር እየተገናዘበ የሚጣል መሆን ሲገባው፣ በአንድ ጊዜ ያውም ከስድስት ዓመታት ቆይታ በኋላ እንዲህ ከፍተኛ ጭማሪ አስከትሎ መምጣቱ ተቀባይነት እንደሌለው ከሚገልጹት ባለሙያዎች መካከል አንዱ ዶ/ር ታደሰ ሌንጮ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ታክስ ሥርዓት ውስጥ የዳበረ ልምድ ያላቸው ዶ/ር ታደሰ በኢትዮጵያ የታክስ ግመታ የሚካሔደበትን ሥርዓትና የሚጣለውን የግምት ታክስ መጠን ኮንነዋል፡፡

እንዲህ ያለው ሒደት በአንድ ጀምበር እንደማይከናወን፣ ይልቁንም የታክስ ግምቱ ከመቀመጡ በፊት ሰፊ የማጣራት ሥራዎች መከናወን እንደነበረባቸው አብራርተዋል፡፡ ለታክስ ግመታው የሚረዱ ሳይንሳዊ ዘዴዎች ቢተገበሩ ኑሮ የስህተት ደረጃውን ሊቀንሱት ይችሉ እንደነበር በመግለጽ፣ የታክስ ግመታው ከመደረጉ ቀደም ብሎም ከነጋዴው ማኅበሰረብ ጋር በመነጋገርና መግባባት ላይ በመድረስ ለግምት ስለሚጠቀምባቸው ዘዴዎችና የአተማመን ሒደቶች አመላካች ነጥቦችን ማብራራት ይጠበቅበት እንደነበርም ጠቅሰዋል፡፡ ‹‹በትክክል ሠርተውት ቢሆን ኑሮ ይህ ሁሉ ሰው አይቃወማቸውም ነበር፤›› ብለዋል፡፡ ይልቁንም የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋናው ዓላማ የታክስ ገቢውን ማሳደግ ብቻ እንዳስመሰለውም ከመግለጽ አልተቆጠቡም፡፡ በመሆኑም የተከተሉት የትመና ሥርዓት ሳይንሳዊ እስካልሆነ ድረስ፣ የሕዝቡም ተቃውሞ እስከቀጠለ ድረስ ፖለቲካዊ ሚና ሊኖረው እንደሚችልም አሳስበዋል፡፡ በመሆኑም የታክስ አስተዳደሩ ባለሥልጣናት ከበላይ ስልክ ተደውሎላቸው ተዉ ሊባሉ እንደሚችሉም ከሚታየው የሕዝቡ ቅሬታና ተቃውሞ በመነሳት ግምታቸውን በማስቀመጥ መንግሥት የተመነውን የታክስ መጠን ሊያነሳ እንደሚችል ጠቅሰዋል፡፡

የተቃማዊ ፓርቲዎች መግለጫ

ሆኖም ሰሞኑን መግለጫ የሰጡት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የታክስ ፕሮግራም ምክትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ነፃነት አበራ፣ ሰዎች ቅሬታ ካላቸው በተናጠል እንደሚስተናገዱ ተናግረዋል፡፡ በቡድን ለሚቀርብ የትኛውም ዓይነት ጥያቄ ምላሽ እንደማይሰጥ የጠቀሱት ወ/ሮ ነፃነት፣ ታክስ ከፋዮችን በተናጠል በመገምገም የታክስ ግምቱ እንደተጣለባቸው በማስታወቅ የሚቀርብ ቅሬታ ካለም በዚሁ አግባብ ብቻ እንደሚስተናገድ ገልጸዋል፡፡

እሳቸው ይህን ይበሉ እንጂ በተናጠልም ቢሆን የሚቀርበው ቅሬታ ተገቢውን ምላሽ እንደማያገኝ ታክስ ከፋዮች እየተናገሩ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር አሁን ታክስ ከፋዮቹ አሁን የተጠየቁት የታክስ መጠን ሙሉውን እንዳልሆነና በመጪው በጀት ዓመት ሙሉውን መጠን መክፈል እንደሚጠበቅባቸው እየተነገራቸው በመሆኑ፣ ቅሬታቸውን እያባባሰው እንደሚገኝ ሲገልጹ ይደመጣል፡፡

የሰሞኑን የታክስ ግርግር በመንተራስ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) እና ሰማያዊ ፓርቲ (ሰማያዊ) ሰኔ 29 ቀን 2009 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ፣ ‹‹በአዲስ አበባ ነጋዴዎች ላይ የተተመነው ከአቅም በላይ የሆነ የግብር ዕዳ እንዲሻሻል አጥብቀን እንጠይቃለን፤›› ብለዋል፡፡ በፓርቲዎቹ መግለጫ መሠረት ይህ የግብር ዕዳ ዜጎች በአገራቸው ነግደው ለማደር ያላቸውን ተስፋ የሚያሟጥጥና ለስደት የሚዳርግ ከመሆኑም በላይ በስደት የሚገኙ ወገኖችም ወደ አገር ቤት ለመመለስ ፈቃደኛ እንዳይሆኑ ከሚያደርጉ ምክንያቶች መካከል ዋነኛው እንደሚሆን እና መንግሥትም ልብ ሊለው እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

በተጣለባቸው ከፍተኛ የግብር ጫና ምክንያት የንግድ ፈቃድ ለመመለስና ከሥራ ለመውጣት የጠየቁ ነጋዴዎች እስከ ጥቅምት ወር 2010 ዓ.ም. ድረስ መመለስ እንዳይችሉ መከልከላቸውን ፓርቲዎቹ ተቃውመው፣ መመለስ ቢችሉ እንኳ ሥራ ካቆሙበት ጊዜ ጀምሮ ንግድ ፈቃዳቸውን እስከመለሱበት ጊዜ ድረስ ያለውን የገቢ ግብር በአዲሱ ተመን መሠረት መክፈል እንዳለባቸው መቀመጡንም ኮንነዋል፡፡ በመሆኑም መኢአድና ሰማያዊ የመንግሥትን ድርጊት በማውገዝ ባለአራት ነጥብ የአቋም መግለጫውን ይፋ አድርገዋል፡፡

ምንም እንኳ ነጋዴዎቹም ሆኑ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ምሁራንም ጭምር የመንግሥትን የግምት ታክስ አሠራር ቢቃወሙም፣ መንግሥት ግን ሊከፈለው የሚገባ በርካታ ገንዘብ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ሰኔ 30 ቀን 2009 ዓ.ም. በፓርላማ መዝጊያ ንግግራቸው፣ ይህ የታክስ አሠራር እንደሚቀጥል ቆፍጠን ባለመንገድ አስታውቀዋል፡፡

በሚቀጥለው በጀት ዓመት መንግሥት ከከተማው ታክስ ከፋዮች እንደሚሰበስብ ያስታወቀው የታክስ መጠን 26 ቢሊዮን ብር ነው፡፡ ባለፈው በጀት ዓመት ባለሥልጣኑ የሰበሰበው መጠን 129.6 ቢሊን ብር ሲሆን ከዕቅዱ የ18 ቢሊን ብር ያህል ቅናሽ ያሳየ መጠን እንደሆነም አስታውቋል፡፡ አብዛኛውን አገሪቱን የልማት ወጪዎች በራስ አቅም ለመሸፈን ባለው አቋም መሠረት 80 በመቶ ያህል ወጪዎቹን በዚሁ አግባብ ከአገር ውስጥ ምንጮች ለመሸን እንደቻለም ሲገልጽ ይደመጣል፡፡ ይሁንና አሁንም ድረስ በታክስ መረብ ውስጥ ያልተካተተ ሰፊ የንግድ ማኅበሰረብ እንደሚገኝ ሲገልጽ ዋናው መደበቂያ ደግሞ የደረጃ ‹‹ሐ›› ግብር ከፋዮች ውስጥ የሚገኙት እንደሆኑ አስታውቋል፡፡ ከዘጠኝ ሺሕ ያላነሱ ነገር ግን ከፍተኛ ግብር ከፋይ መሆን የሚገባቸው ነጋዴዎች እንደሚገኙ መንግሥት ያምናል፡፡

በሌላ በኩል ከተቀጣሪዎች የሚሰበሰበው የታክስ መጠን ከፍተኛ የመሆኑን ያህል ከነጋዴው የሚገኘው ከሚጠበቀው ይልቅ አነስተኛ መሆኑ ብቻም ሳይሆን አብዛኛው ኅብረሰተብ ታክስ የመክፈል ልማድ ባለማዳበሩ ችግሮች እንደሚከሰቱ ይገልጻል፡፡ ምንም እንኳ መንግሥት በግምት የሚጣለውን የታክስ ሥርዓት እንደማያምንበት ከዚህ ቀደም ቢያስታውቅም፣ አማራጭ ስሌለው ግን ይህንኑ መንገድ እንደተከተለም ይጠቅሳል፡፡

ይህም ሆኖ ባለሥልጣኑ ታክስ ከፋዩ ‹‹ባመነው ልክ ይክፈል፤›› የሚል አሠራር እንደሚከተል በዚሁ አግባብም ታክስ እንደሚያስከፍል ቢናገርም፣ በተግባር ግን ልምድ የሌላቸው ገማቾችን በየመደብሩ በማሰማራት ግምት ማውጣቱ ሲኮነን ቆይቷል፡፡ ከስድስት ዓመታት በፊት እንደተደረገው ዘንድሮም ተመሳሳዩ አካሔድ የተተገበረ ሲሆን፣ የዘንድሮው ግን ሁለት ጊዜ እንደተካሔደ ይታወቃል፡፡ በመጀመሪያው ዙር የተደረገው ግመታ ተቀባይነት በማጣቱ በድጋሚ እንዲገመት የተደረገበት አግባብም በአብዛኛው ነጋዴ እሮሮ እንዲነሳበት ምክንያት ሆኗል፡፡

Standard (Image)

አኮር ሆቴሎች ግሩፕ ተጨማሪ ብራንድ ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት ተስማማ

$
0
0

ለአኮር ሆቴሎች ግሩፕ አራተኛ የሆነውንና ኤምጋለሪ ባይ ሶፊቴል የተባለውን ብራንድ ከሁለት ዓመት በኋላ ሥራ ለማስጀመር ከኢትዮጵያው ፀሜክስ ሆቴሎችና ቢዝነስ ኩባንያ ጋር ስምምነት ላይ መድረሱን አስታወቀ፡፡

የአኮር ሆቴሎች ግሩፕ በቅርቡ ለሪፖርተር በላከው መግለጫ መሠረት፣ ስምምት የተደረገበት የሆቴል ብራንድ 218 ክፍሎች የሚኖሩት ኤምጋለሪ ባይ ሶፊቴል የተባለው ብራንድ እስካሁን ወደ ኢትዮጵያ ካስገባቸው እንደ ኖቮቴል፣ ፑልማን እንዲሁም ኢቢስ የተባሉ ብራዶች በተጨማሪ አራተኛው እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

ስምምነቱን የፈረሙትና የሆቴሉ ባለንብረት የሆኑት አቶ ረዘነ አያሌው ስለ ስምምነቱ ለማነጋገር በተደጋጋሚ የተደረገው ሙከራ ባይሳካም፣ የአኮር ግሩፕ የአፍሪካና የመካከኛው ምሥራቅ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ስቴቨን ዴይንስ እንዳስታወቁት፣ ባለ 218 ክፍሎች የሆነውን ኤምጋለሪ ባይ ሲፊቴልን ጨምሮ የአኮር ሆቴሎች ብራንድ የሆኑትና በኢትዮጵያ ሥራ የሚጀምሩት ሆቴሎች በጠቅላላው ከ1000 በላይ ክፍሎች የሚኖሯቸው ይሆናሉ፡፡ ለአነስተኛ፣ ለመካከለኛ እንዲሁም ለከፍተኛ በጀት ተጠቃሚዎች ግልጋሎት የሚሰጡት ሆቴሎችን ጨምሮ በአፍሪካ የሚደረጉት የሆቴል ኢንቨስትመንቶች ለመዝናናት የሚመጡ ጎብኚዎችን ቁጥር ለማበራከት እንደሚያግዝ አብራርተዋል፡፡  

ከዚህ ቀደም በተደረገ ስምምነት መሠረት ፀሜክስ ሆቴሎች ከዓለም አቀፉ ክራውን ፕላዛ ጋር ባደረገው ድርድር መሠረት የዚህን ሆቴል ብራንድ በማምጣት በልደታ አካባቢ እያስገነባው በሚገኘው ሕንፃ ሥራ እንደሚያስጀምር ሲዘገብ ቆይቷል፡፡ ይሁንና በይገባኛል የፍርድ ቤት ክርክር ሳቢያ በተፈጠረ መጓተትና በሌሎችም ምክንያቶች የቀደመውን ስምምነት በመወተው ከአኮር ሆቴሎች ግሩፕ ጋር አዲስ ስምምነት ለማድረግ እንደተገደደ የሚጠቅሱ መረጃዎች እየተደመጡ ነው፡፡ ይሁንና ይፋዊ ምክንያቱ ምን እንደሆነ በፀሜክስ ሆቴሎች ኩባንያ በኩል አልተገለጸም፡፡

218 ክፍሎች የሚኖሩት አዲሱ ኤምጋለሪ ባይ ሶፊቴል፣ የሙሉ ቀን የምግብ አገልግሎት የሚሰጥ ሬስቶራንትን ጨምሮ ሦስት ቡና ቤቶች፣ መዋኛ፣ ጂም እንዲሁም ስፓ እንደሚኖረው ይጠበቃል፡፡

ኤምጋለሪ ባይ ሶፊቴል በ24 አገሮች ውስጥ የሚንቀሳቀስ ብራንድ ሲሆን፣ አኮር ሆቴሎች ግሩፕ የሚያተዳድራቸው በርካታ ብራንድ ሆቴሎች ብዛት በጠቅላላው 2500 ሆቴሎች በ95 አገሮች ውስጥ አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡

 

 

Standard (Image)

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ 27 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያላቸውን ምርቶች አገበያየ

$
0
0

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በ2009 በጀት ዓመት ከ27 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያለው ግብይት ማስፈጸሙ ተገለጸ፡፡ ዘመናዊ የግብይት ሥርዓትን በመከተል ከዘጠኝ ዓመታት በላይ የዘለቀው የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በ2009 በጀት ዓመት ያስፈጸመው ግብይት ከቀዳሚው ዓመት ከአራት ቢሊዮን ብር በላይ ብልጫ አለው፡፡

ከምርት ገበያው የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በ2008 በጀት ዓመት ያስፈጸመው የግብይት መጠን 23 ቢሊዮን ብር እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ በወቅቱም በምርት ገበያው በኩል የተገበየው የምርት መጠን 705 ሜትሪክ ቶን ነበር፡፡ በ2009 በጀት ዓመትም ከ730 ሜትሪክ ቶን በላይ የሚሆን ምርት ማገበያየት እንደተቻለ ታውቋል፡፡ ምርት ገበያው በዋናነት ቡናን በማገበያየት የሚጠቀስ ቢሆንም፣ ሰሊጥ ሽንብራ፣ ቦሎቄና የመሳሰሉ ምርቶችን  በማገበያየት ላይ ይገኛል፡፡

በዓመቱ ውስጥ ካስፈጸማቸው ግብይቶች ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘውም ቡና መሆኑን የሚያመለክተው መረጃ፣ አዳዲስ ምርቶችንም በምርት ገበያው በኩል ለማገበያየት ውጥን አለው፡፡ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ምርት ገበያ አዳዲስ አሠራሮችን በማከል አገልግሎቱን የሚቀጥል ሲሆን፣ የቡና ሪፎርምን ተከትሎ የሚተገበሩ አዳዲስ አሠራሮችን መተግበር እንደሚጀምር ታውቋል፡፡

ይህንንም ለማከናወን የኢትዮጵያ ምርት ገበያ የተቋቋመበት አዋጅ ተሻሽሎ ባለፈው ሳምንት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸድቋል፡፡ ከዚህ ቀደም ማንኛውም ዓይነት የቡና ግብይት ሊፈጸም የሚችለው በምርት ገበያው ብቻ እንደበር የሚታወስ ሲሆን፣ በተሻሻለው አዋጅ ግን በምርት ገበያው በኩል መገበያየት ግድ የማይሆኑ የቡና ዓይነቶች ይኖራሉ፡፡ እነዚህም ‹‹ልዩ ቡና›› የሚል መጠሪያ ያላቸው ምርቶች ሲሆኑ፣ ‹‹ልዩ ቡና›› የሚያሰኛቸውን መስፈርቶች ማሟላታቸው ከተረጋገጠ ከምርት ገበያው የግብይት ሥርዓት ውጭ ግብይት እንዲፈጸም የሚያስችል ነው፡፡

‹‹ልዩ ቡና›› ተብለው የሚለዩበትም የራሱ የሆነ አሠራር የሚኖረው ሲሆን፣ ምርት ገበያው ‹‹ልዩ ቡና››ን በአስገዳጅነት ማገበያየት አያስችለውም፡፡ 

Standard (Image)

የባንኮች የሞባይል ባንኪንግ አገልግሎት በጋራ ሊተሳሰር ነው

$
0
0

ዘመናዊ የባንክ አገልግሎትን ለማስፋፋት እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው ኢትስዊች ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የሁሉንም ባንኮች የሞባይል ባንኪንግ አገልግሎት በማስተሳሰር በአንድ ላይ መስጠት የሚያስችለውን አዲስ አገልግሎት ለመጀመር በዝግጅት ላይ መሆኑ ተገለጸ፡፡

እንደ ኢትስዊች ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ብዙነህ በቀለ ገለጻ፣ ይህንን አገልግሎት በአዲሱ ዓመት የመጀመርያዎቹ ሁለት ወራት ውስጥ ለማስጀመር የሚያስችል ዝግጅት እየተጠናቀቀ ነው፡፡

በቀጣይ ሳምንታት የሙከራ ሥራዎችን በመጀመር ከተፈተሸ በኋላ የሁሉም ባንኮች የሞባይል ባንኪንግ አገልግሎትን በማስተሳሰር፣ የየትኛውም ባንክ የሞባይል ባንኪንግ ተጠቃሚ ደንበኛ ከአንዱ ባንክ ወደ ሌላ ባንክ ክፍያ መፈጸም የሚያስችል ይሆናል፡፡

በባንክ ኢንዱስትሪ ውስጥ ከፍተኛ የሆነ አስተዋጽኦ ያበረክታል የተባለው ይህ ዘመናዊ የባንክ አገልግሎት፣ ማንኛውም የሞባይል ባንኪንግ አገልግሎት ተጠቃሚ ደንበኛ ሊገለገልበት ይችላል፡፡

አገልግሎቱ ሲጀመር በግለሰብ ደረጃም ሆነ በኩባንያ ደረጃ የተመዘገበ ደንበኛ በየትም ቦታ ሆኖ በሞባይል ባንኪንግ አገልግሎቱን የሚያገኝ ሲሆን፣ ሞባይሉን ተጠቅሞ ለየትኛውም ባንክ ደንበኛ ክፍያ መፈጸምና መቀበል ይችላል፡፡ ማንኛውም ግለሰብም ሆነ ኩባንያዎች በሞባይል ባንኪንግ አገልግሎቱ የተለያዩ ክፍያዎችን በየትኛውም ባንክ በኩል ለመፈጸም ይችላሉ፡፡

የሁሉም ባንኮች የሞባይል ባንኪንግ በማስተሳሰር ደንበኞች ገንዘባቸውን በሞባይል እንዲያንቀሳቅሱ የሚያስችላቸው ይህ አገልግሎት፣ ቋሚና ጊዜያዊ ክፍያዎችን በቀላሉ ለማስተላለፍ ያስችላል ተብሏል፡፡

አንድ የሞባይል ባንኪንግ ደንበኛ ወርኃዊ ክፍያዎችን በቀጥታ በዚህ አገልግሎት አማካይነት ለመክፈል፣ አገልግሎት ተቀባዩ የሞባይል ባንኪንግ ተጠቃሚ መሆን እንደሚገባውም ለማወቅ ተችሏል፡፡

የሁሉም ባንኮች የሞባይል ባንክ አገልግሎት በመጀመራቸው፣ በኩባንያ ደረጃ ክፍያዎችን መፈጸም ያስችላል ተብሏል፡፡ እንደ ምሳሌ የተጠቀሰውም ግብርን በሞባይል ባንኪንግ አገልግሎት በመጠቀም መክፈል መቻሉ ነው፡፡

ወደፊትም እንደ ውኃ፣ ኤሌክትሪክና የመሳሰሉት የአገልገሎት ክፍያዎች በዚሁ የሞባይል ባንኪንግ በኩል መፈጸም እንደሚቻል ታውቋል፡፡ እንደ የትምህርት ቤት  ክፍያዎችም ቢሆኑ በዚህ የሞባይል ባንኪንግና ወደፊት በሚጀመረው የኢንተርኔት ባንኪንግ በኩል መፈጸም ይቻላል፡፡ ባንኮች አሁን ለደንበኞቻቸው የሚሰጡት የሞባይል ባንኪንግ አገልግሎት ለባንኩ ደንበኞች ብቻ የሚያገለግል እንደነበር ይታወቃል፡፡

ኢትስዊች የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክን ጨምሮ ሁሉንም የአገሪቱ ባንኮች በባለአክሲዮንነት ይዞ የተቋቋመ ኩባንያ ነው፡፡ እስካሁን የሁሉንም ባንኮች የኤቲኤም አገልግሎት በማስተሳሰር የአንዱ ባንክ ደንበኛ በየትኛውም ባንክ የኤቲኤም ማሽን መጠቀም ያስቻለ ሲሆን፣ ኢትዮ ፔይ የተባለ ብሔራዊ የክፍያ ካርድ በማዘጋጀትም ለአገልግሎት አብቅቷል፡፡ 

Standard (Image)

የአሜሪካ መንግሥት ኢትዮጵያን ያገለለ የ639 ሚሊዮን ዶላር የሰብዓዊ ዕርዳታ ለአራት አገሮች ይፋ አደረገ

$
0
0
  • በየአገሮቹ የተከሰቱት ቀውሶች ከኢትዮጵያ የባሱ ናቸው ተብሏል

የአሜሪካ ፕሬዚዳንት በደቡብ ሱዳን፣ በሶማሊያ፣ በናይጄሪያና በየመን ጉዳት ላይ የሚገኙ አሥር ሚሊዮን ሕዝቦችን ለመደገፍ የ639 ሚሊዮን ዶላር ተጨማሪ ፈንድ ፕሬዚዳንት ዶናልንድ ትራምፕ መፍቀዳቸውን አስታወቀ፡፡ አስቸኳይ ድጋፍ እንዲደረግላት ስትወተውት የቆየችውና 7.8 ሚሊዮን ሕዝቦች ለአስቸኳይ የምግብ እጥረት የተዳረጉባት እንዲሁም ከ800 ሺሕ በላይ ስደተኞችን ያስጠለለችው ኢትዮጵያ፣ የዚህ ዕርዳታ ተጠቃሚ አለመሆኗ ታውቋል፡፡

ሐምሌ 3 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሔደ የቴሌፎን ኮንፈረንስ ይፋ እንደተደረገው ከሆነ፣ አሜሪካ ለእነዚህ አገሮች ቅድሚያ በመስጠት ከሚገኙበት አስከፊ የሰብዓዊ ቀውስና የእርስ በርስ ግጭት እንዲወጡ ተብሎ የተመደበ ተጨማሪ ፈንድ ነው፡፡ ዓለም ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ ያላየችውን አሰቃቂ የሰብዓዊ ቀውስ እያስተናገደች እንደምትገኝ የገለጹት፣ በአሜሪካ የዓለም አቀፍ የልማት ቢሮ ለዴሞክራሲ፣ ለግጭትና ለሰብዓዊ ጉዳዮች ዕርዳታ ቢሮ ተጠባባቂ ምክትል አስተዳዳሪ የሆኑት ሮበርት ጀንኪንስ ናቸው፡፡

ምክትል አስተዳዳሪ ጀንኪንስ በቴሌ ኮንፈረንሱ ወቅት እንደገለጹት፣ ለአገሮቹ የተመደበው ገንዘብ እ.ኤ.አ. በ2017 ለተያዘው የድጋፍ መጠን ተጨማሪ በመሆኑ ለአራቱ አገሮች የሚከፋፈለውን የገንዘብ መጠን በጠቅላላው 1.8 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያደርሰው ታውቋል፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን ከ639 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ ለደቡብ ሱዳን የሚሰጠው የገንዘብ መጠን ከ190 ሚሊዮን ዶላር እንደሆነና በ2017 ለአገሪቱ የሚሰጣት የዕርዳታ መጠን በጠቅላላው 650 ሚሊዮን ዶላር እንደሆነም ጀንኪንስ ገልጸዋል፡፡

በአንፃሩ በኢትዮጵያ ለምግብ እጥረት የተጋለጡና ተጨማሪ የአስቸኳይ ዕለት ደራሽ ዕርዳታ ለ7.8 ሚሊዮን ሕዝቦች እንደሚያስፈልግ ያስታወሱት ምክትል አስተዳዳሪው፣ የአሜሪካ መንግሥት በዚህ ዓመት ብቻ የ225 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማደረጉን አብራርተዋል፡፡ ጀንኪንስ ይህን ያብራሩት ኢትዮጵያ ከ639 ሚሊዮን ዶላር የዕርዳታ ገንዘብ ተጠቃሚ መሆን ያልቻለችባቸው ምክንያቶችን እንዲያብራሩ በተጠየቁበት ወቅት ነበር፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ የዚህ ዕርዳታ አካል አልሆነችም ማለት ተዘንግታለች ማለት አይደለም፡፡ ሆኖም በኢትዮጵያ ካለው ይልቅ በአራቱ አገሮች ውስጥ የተከሰቱት ቀውሶች እጅግ አሳሳቢ በመሆናቸው ቅድሚያ ስለተሰጣቸው ነው፤›› ብለዋል፡፡

የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ትብብር ኤጀንሲ (ዩኤስኤኣይዲ) ባጠናቀረው መረጃ መሠረት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ለ7.8 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን የድርቅ ተጎጂዎች ያስፈልጋል ካለው ተጨማሪ 540 ሚሊዮን ዶላር ባሻገር፣ አስከፊ የተመጣጠነ የምግብ ዕጥረት ለታየባቸው ሦስት ሚሊዮን ሰዎች የሚውል የ55 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ከደቡብ ሱዳን፣ ከሶማሊያና ከኤርትራ አሁንም ድረስ እየመጡ የሚገኙ ከ800 ሺሕ በላይ ስደተኞች በኢትዮጵያ የተለያዩ መጠለያዎች ይገኛሉ፡፡ ስደተኞቹ በካምፕ ከመኖር ባሻገር ከአገሬው ሕዝብ ጋር ተሰባጥረው የሚኖሩበት፣ የሚማሩበትና ሥራ ሠርተው የሚውሉበት አሠራር ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት በአሁኑ ወቅት በድርቅ ለተጎዱትም ሆኑ ባለፈው ከሁለት ዓመት በፊትም በምግብ እጥረት ለተጎዱ 10.2 ሚሊዮን ሰዎች የሚውል ትርጉም ያለው የዕርዳታ ድጋፍ ከውጭ ለማግኘት መቸገሩን በተደጋጋሚ ሲያስታውቅ ቆይቷል፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት ለፓርላማው የመንግሥታቸውን ሪፖርት ያቀረቡት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በአፍሪካ ቀንድ፣ በምዕራብ አፍሪካ እንዲሁም በመካከለኛው ምሥራቅ የተከሰቱ ቀውሶች ለኢትዮጵያ ችግሮች ድጋፍ የማግኘት ጥሪዎቿን ምላሽ አልባ እንዳደረጋቸው አስታውቀው እንደነበር ይታወሳል፡፡

ፕሬዚዳንት ትራምፕ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላም ለዕርዳታ የሚውል ድጋፍ ላይ ቅናሽ መደረጉ ሲዘገብ ቆይቷል፡፡ ቅናሹ በእጅጉ ከሚመለከታቸው አገሮች መካከል ኢትዮጵያ በግንባር ቀደምትነት መቀመጧም ሲነገር ነበር፡፡ እ.ኤ.አ. በ2017 ብቻ የ200 ሚሊዮን ዶላር ቅናሽ እንደሚደረግባት መረጃዎች መውጣታቸውን በማስመልከት ሪፖርተር መዘገቡ ይታወሳል፡፡ በአዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ዘገባውን ያስተባበለው፣ በወቅቱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የበጀት ቀመራቸውን ይፋ ባላደረጉበት የወጣ ዘገባ መሆኑን በመጥቀስ፣ በጀቱ ይፋ ሲደረግ የሚታይ ነው በማለት ነበር፡፡

አሜሪካ በየዓመቱ ከ60 ቢሊዮን ዶላር ያነሰ የዕርዳታ ድጋፍ ለመላው ዓለም የምትሰጥ ቢሆንም፣ በአንፃሩ ከግማሽ ትሪሊዮን ዶላር በላይ ለወታደራዊ ተልዕኮዎች የምትመድብ በመሆኗ ለሰብዓዊ ድጋፎች የምትሰጠው ድጋፍ እጅግ አነስተኛ መሆኑ እያስተቻት ይገኛል፡፡ ከዚሁ ከ60 ቢሊዮን ዶላሩም ቢሆን በአዲሱ የፕሬዚዳንት ትራምፕ በጀት እስከ 20 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ቅናሽ እንደሚታይ ከወዲሁ እየተነገረ ነው፡፡ ሆኖም በእረፍት ላይ የሚገኘው የአሜሪካ ኮንግረስ ለሰብዓዊ ዕርዳታ የሚመደበው ገንዘብ ላይ የቀረበውን የቅነሳ ዕቅድ በመመልከት ውሳኔ እንዲሰጥበት እየተጠበቀ ይገኛል፡፡ አብዛኛውን የሰብዓዊና የልማት ሥራዎች የሚያከናውነው ዩኤስኤኣይዲ ሲሆን፣ ይህ ተልዕኮ የአሜሪካን መልካም ገጽታ ጭምር አደጋ ውስጥ የሚከት አካሔድ መሆኑን በመግለጽ፣ ፕሬዚዳንቱ ያቀረቡትን የተቀናሽ በጀት ዕቅድ በርካታ የኮንግረስ አባላት ሲቃወሙ መቆየታቸውም ይታወቃል፡፡ 

Standard (Image)

ትራንስ ኢትዮጵያ በ372 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባው የዋና መሥሪያ ሕንፃ ሥራ ጀመረ

$
0
0

 

  • ጎማ ማምረቻ የመገንባት ውጥን አለው

የትግራይ የመልሶ ማቋቋም ኢንዶውመንት ፈንድ (ኤፈርት) በትግርኛው ምኅፃረ ቃል ትዕምት፣ በሥሩ ከሚያስተዳድራቸው ኩባንያዎች መካከል አንዱ የሆነው ትራንስ ኢትዮጵያ በአዲስ አበባ ከተማ የሚገለገልበትን የዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ ግንባታ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት አበቃ፡፡

ትራንስ ኢትዮጵያ ሐሙስ፣ ሐምሌ 6 ቀን 2009 ዓ.ም. ያስመረቀው ባለሰባት ወለል ሕንፃ፣ ሳሪስ አካባቢ የሚገኝና ከዚህ ቀደም ወይራ ትራንስፖርት ድርጅት እያስገነባ የነበረውን ጅምር ሕንፃ በጨረታ ገዝቶ ተጨማሪ ግንባታዎችን አክሎበት ለአገልግሎት ያበቃው ነው፡፡

ከ260 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገዛው ይህ ሕንፃ፣ ከ112 ሚሊዮን ብር በላይ ተጨማሪ ወጪ ወጥቶበት እንደተጠናቀቀ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከዚሁ ሕንፃ ምርቃት ጎን ለጎን በቃሊቲ ክራውን ሆቴል አካባቢ ፒሬሊ ከተሰኘው የተሽከርካሪ ጎማ አምራች ኩባንያ ጋር በመሆን ያስገነባውን የፒሬሊ የጎማ አገልግሎት መስጫ ማዕከልም በዚሁ ዕለት ለአገልግሎት በቅቷል፡፡

በሁለቱም የምረቃ ፕሮግራሞች ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የትዕምት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ አዜብ መስፍን እንደገለጹት፣ ለአገልግሎት የበቁት ግንባታዎች የትራንስ ኢትዮጵያን ዕድገት ማሳያ ሞዴሎች ናቸው፡፡

ከመነሻው ከተሰማራበት የጭነት አገልግሎት ዘርፍ በተጨማሪ ፒሬሊ ጎማና ጃፓን ስታር የመኪና ባትሪ ሽያጭ አገልግሎቶችን በማካተት እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው ትራንስ ኢትዮጵያ፣ በሎጂስቲክና በሌሎችም አዳዲስ የቢዝነስ መስኮች ውስጥ በመግባት ሥራውን እያስፋፋ ነው፡፡   

የትራንስ ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ተፈሪ ዘውዱ እንደገለጹትም፣ ትራንስ ኢትዮጵያ ቢዝነሶቹን ከማስፋፋት በተጨማሪ፣ የኩባንያውን ሀብት በማሳደግ አኳያም በዕለቱ የተመረቀውን ሕንፃ በጨረታ ገዝቶ፣ ግንባታውን በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ማብቃቱ አንዱ መገለጫው ነው፡፡

ስለጎማ አገልግሎት ማዕከሉ አቶ ተፈሪ ሲናገሩ፣ የዘመናዊ ተሽከርካሪዎች ቁጥር እያገደ ከመምጣቱ አንፃር ማዕከሉ መቋቋሙ እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የማዕከሉ ዋና ዋና ጥቅሞቹ ብለው የገለጹት በአገሪቱ ውስጥ ዘመናዊ የጎማ ማኔጅመንት ባህል እንዲዳብር፤ ከጎማ ጥራት ጋር ተያያዥነት ያላቸውን አደጋዎች ለመቀነስ፣ ለመቆጣጠርና የመንገድ ደኅንነትን ለማረጋገጥ አጋዥ መሆኑ ነው፡፡

ከዚህም ሌላ እንዲህ ዓይነት ማዕከል መቋቋሙ የጎማ አገልግሎትን ለማራዘምና ለጎማ የሚደረገውን ወጪ ለመቀነስ የሚያስችል ስለሚሆን ጠቀሜታው የጎላ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡ ለዚህ ማዕከል ግንባታና ለማሽነሪዎቹ ግዥ ከአሥር ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገ ጠቅሰዋል፡፡

ትራንስ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ለስካኒያ ምርት የኢትዮጵያና የጂቡቲ ወኪል በመሆን የስካኒያ አውቶብስ፣ የጭነት ተሽከርካሪዎችና ሞተሮችን በማስመጣት በማከፋፈል ላይ እንደሚገኝ የጠቀሱት የድርጅቱ ኃላፊዎች፣ አሁንም ኩባንያውን የማስፋፋት ዕቅድ እንዳላቸው አመልክተዋል፡፡  

ወ/ሮ አዜብም ትራንስ ኢትዮጵያ አሁን በያዘው ሥራ ብቻ የሚቆም ሳይሆን፣ ተጨማሪ ሥራዎችን እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡ አሁን ከሚያንቀሳቅሰው ግዙፍ ኢንቨስትመንት በበለጠ በትራንስፖርትና መሰል አገልግሎቶች ላይ ለመሰማራት ዝግጀቱን ስለማጠናቀቁም ሳይገልጹ አላለፉም፡፡

ትራንስ ኢትዮጵያ በትዕምት ሥር ካሉ ግዙፍ ኩባንያዎች በየጊዜው ፈጣን የሆነ ዕድገት እያሳየ ነው በማለት የገለጹት ወ/ሮ አዜብ፣ ባለፉት አምስት ዓመታት በተከታታይ ፈጣን ዕድገት በማሳየት በአገሪቱ የትራንስፖርት ዘርፍ በአሠራርና በአደረጃጀቱ ውጤታማ በመሆን ከቀዳሚዎቹ አንዱ ሆኗል ብለዋል፡፡

ትራንስ ኢትዮጵያ ከትዕምት በውጤታማነቱ ቀዳሚ ተጠቃሽ መሆኑን የገለጹት ወ/ሮ አዜብ፣ ኩባንያው ጥንካሬውን ይዞ እንደሚቀጥል በመግለጽ ‹‹ትራንስ ወርቅ ኩባንያችን ነው፤›› በማለት ኩባንያው በዕድገት ላይ መሆን ለማሳየት ከዛሬ 20 ዓመት በፊት ይዞት የተነሳው የ100 ሚሊዮን ብር ካፒታል አሁን ከ1.6 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱ ምስክር ነው ብለዋል፡፡

ከፒሬሊ ጎማ ጋር ያለውን የንግድ ትስስር በተመለከተ ተጨማሪ ማብራሪያ የሰጡት ወ/ሮ አዜብ፣ ሁለቱ ኩባያዎች በአሁኑ ወቅት ካላቸው የቢዝነስ ግንኙነት የበለጠ ለመሥራት መታቀዱንና ይህም ጎማ ማምረቻ መገንባትን እንደሚያካትት ጠቁመዋል፡፡

 

Standard (Image)

ወጋገን ባንክ በአዲስ ዓርማ በ800 ሚሊዮን ብር ወዳስገነባው ሕንፃ ሊገባ ነው

$
0
0

 

ወጋገን ባንክ ላለፉት 20 ዓመታት ሲገለገልበት የቆየውን የንግድ ዓርማ በመቀየር በአዲሱ ዓመት ከ800 ሚሊዮን ብር በላይ ያወጣበትንና ግንባታው የተጠናቀቀውን የዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ መገልገል እንደሚጀምር ይፋ አደረገ፡፡  

ባንኩ እስካሁን ሲገለገልበት የቆውን ዓርማ በአዲስ መተካቱን በማስመልከት ሐሙስ ሐምሌ 6 ቀን 2009 ዓ.ም. አዲሱን ዓርማ በይፋ ባስተዋወቀበት ሥነ ሥርዓት ወቅት እንደተገለጸው፣ ባንኩ አዲሱን ዓርማ ይዞ ወደ አዲሱ ሕንፃ በቅርቡ ይገባል፡፡ ባንኩ 20ኛ ዓመቱንም በአዲስ ሕንፃና በአዲስ ዓርማ ታጅቦ ያከብራል ተብሏል፡፡

የወጋገን ባንክ ዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ተፈሪ ዘውዱ እንደገለጹት፣ አዲስ ዓርማ የባንኩን እሴቶች፣ እ.ኤ.አ. በ2025 በአፍሪካ ከሚገኙት አሥር ስመ ጥርና ተፎካካሪ ባንኮች መካከል አንዱ ለመሆን ያስቀመጠውን ራዕይ በሚያንፀባርቅ መልኩ የተነደፈ ነው፡፡

‹‹ለ20 ዓመታት ያገለገለውን የልዩ ምልክት ዓርማ በአዲስ ለመተካት ስንወስን ያለፉት ዓመታት ስኬት፣ የወደፊቱ ብሩኅ ተስፋና ዛሬ የደረስንበትን ጽኑ መሠረት እንዲያንፀባርቅ እንዲሁም የመጪውን ስሜትና ዝንባሌ ከግምት ያስገባ ለውጥ ነው፤›› በማለት አቶ ተፈሪ ገልጸዋል፡፡

የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ ዓርአያ ገብረ እግዚአብሔርም፣ ‹‹አዲሱ የባንኩ መግለጫ ዓርማ ለደንበኞችና ለሌሎች ባለድርሻ አካላት የባንኩ ራዕይ፣ ተልዕኮ፣ እሴቶች፣ ያለፈውን ስኬትና የወደፊቱን ግብ በሚወክል ከሌሎች ተወዳዳሪዎች በቀላሉ ለይተው እንዲያውቁትና እንዲያስታውሱት ያደርጋል፤›› በማለት ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም የባንኩን ገጽታም በወጥነት ለማስተዋወቅና ትኩረት በመሳብ ባንኩን ለማስተዋወቅ የሚደረገውን ጥረት እንደሚደግፍ ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል፡፡

አዲሱ ዓርማ ሁለት ዋና ዋና መገለጫዎች እንዳሉት ሲገለጽ፣ ‹‹ወጋገን›› ከሚለው ስያሜ አማርኛ ፊደላት ውስጥ ‹‹››ን በመውሰድና ከእንግሊዝኛው ‹‹Wegagen›› ከሚለው ቃል ደግሞ ‹‹W››ን በመሳብ፣ ሁለቱን በአንድ አቀናጅቶ በመያዝ የተቀረጸው አዲሱ ዓርማ፣ በክብ ቅርፅ ውስጥ ፀሐይን የሚወክል ሲሆን፣ በክቡ ውስጥ ወደ ጎን የተሰመረው ቀስት ደግሞ በማለዳ የሚታየውን የሰማይና የምድር መጋጠሚያ አድማስ እንደሚያመላክት ተብራርቷል፡፡ የዓርማው ትርጉም አሸናፊነትን፣ መስፋፋትን እንዲሁም የአገልግሎት ተደራሽነትና የባንኩን ስኬት እንደሚገልጽ የባንኩ ኃላፊዎች ተናግረዋል፡፡

አዲሱን ዓርማ ወደ ገበያ ይዘው ከመውጣታቸው በፊት ሁሉም የባንኩ ባለድርሻ አካላት የመከሩበት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ባለአክሲዮኖች፣ የተመረጡ ደንበኞች፣ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላትና ሠራተኞች ተወያይተውበት አስተያየታቸው እንዲካተት ተደርጎ አሁን ይፋ ሊሆን መቻሉ ታውቋል፡፡ ይህ ሎጎ ላለፉት 12 ወራት ሲዘጋጅ ቆይቶ መጨረሻ ላይ የተመረጠው ዓርማ በአዕምሯዊ ንብረት ጽሕፈት ቤት ተመዝግቧል፡፡

የባንኩን አዲስ ዓርማ የሠራው በመስኩ ልምድ ያካበተው ስቱዲዮኔት የተባለው አገር በቀል አማካሪ ድርጅት እንደሆነም ታውቋል፡፡

እንደ አቶ ተፈሪ ገለጻ ባንኩ ያካበታቸውን ነባር እሴቶች ጠብቆ የዘመኑን የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ፍላጎት ለማርካት አልሞ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ላይ መሠረት ያደረገውን አዲስ የአገልግሎት አሰጣጥ ብራንድ ስትራቴጂ በሚያንፀባርቅ መልኩ የተሠራ ነው፡፡ አዲሱ የብራንድ ስትራቴጂና ዓርማ ባንኩ አሁን የደረሰበትን የዕድገት ደረጃና ገጽታ በማጉላት ተጠቃሚዎች በአገልግሎቱ ፍላጎታቸውን የሚያረካ ዘመናዊ ባንክ መሆኑን የበለጠ እንዲገነዘቡ ያደርጋል የሚል እምነትም አላቸው፡፡ የደንበኞችን ትኩረት በመሳብ የባንኩን ገጽታ በወጥነት ለማስተዋወቅ የሚደረገውን ጥረት ውጤታማነት ከፍ በመድረጉ ረገድም አዲሱ ዓርማ ይጠቅማል ተብሏል፡፡

ባንኩ የሚጠቀምበትን የአዲሱን ዓርማ ቀለም መረጣ ላይ ብዙ ስለመደከሙ የባንኩ መግለጫ ያመለክታል፡፡ ኮርፖሬት ቀለም፣ የአንድ ተቋም ብራንድ በሰዎች አዕምሮ ውስጥ እንዲሰርጽና እንዲታወስ ለማድረግ የብራንዱ መገለጫ በመሆኑ ከሚያገለግሉ የተለያዩ ነገሮች ውስጥ አንዱና ትልቅ ተፅዕኖ መፍጠር የሚችል እንደሆነ መጥቀስ በዚሁ ግንዛቤ የቀለም መረጣው ተከናውኗል፡፡ የቀለም ምርጫው የአንድን ተቋም መንፈስ ወይም መልዕክት ከቀለም በተሻለ መንገድ የሚገልጽ ነገር ባለመኖሩ አዲሱ ዓርማ በሚቀረፅበት ወቅትም ለቀለም ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ተገቢውን ወካይ ቀለም ሊመረጥ እንደተቻለ ተገልጿል፡፡ ይህም በቀለም መረጣ ላይ የዓርማ ዋነኛ ቀለም ብርቱካናማ እንዲሆን ተወስኗል፡፡ ብርቱካናማው ቀለም ተፈጥሯዊ ክስተት ከሆነው ጎህ ሲቀድ በሰማይ አድማስ ላይ ከሚታየው የጠዋት ፀሐይ ደማቅ ብርሃን የተቀዳ ሲሆን፣ የሚያመለክተውም በተስፋና በመልካም ምኞች የተሞላ ብሩህ ጊዜን እንደሆነ የቀለም ምርጫውን በተመለከተ በተሰጠው ማብራሪያ ላይ ተገልጿል፡፡

‹‹በንግዱ ዓለም፣ ብርቱካናማ ቀለም ታላቅነትን፣ አዳዲስ ነገሮችን የመፍጠር ተነሳሽነትን፣ የካበተ ዕውቀት፣ ልምድ፣ ሀብትና ጥራትን ይወክላል፤›› የባንኩ መግለጫ አዲሱን ዓርማ በተለያየ መንገድ ማስተዋወቅ መጀመሩን አስታውቋል፡፡

አዲሱ ዓርማ የባንኩን 20ኛ ዓመት በሚከበርበትና የከተማችን አዲስ ፈርጥ ያሉትን የባንኩን ሕንፃ ለማስመረቅ በዝግጅት ላይ ባለበት ወቅት መተዋወቁ ባንኩ ወደ አዲስ ምዕራፍ መሸጋገሩን እንደሚያሳይ የገለጹት አቶ ተፈሪ፣ እ.ኤ.አ. በ2025 ስለአሥሩ የአፍሪካ ባንኮች አንዱ ለመሆን የተነደፈን ዕቅድ ከግብ ለማድረስ አጋዥ ይሆናልም ብለውታል፡፡

ወጋገን ባንክ ከ20 ዓመታት በፊት የተቋቋመ ሲሆን፣ ከ3,000 በላይ ባለአክሲዮኖችን ይዞ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ የግል ባንክ ከመሆኑም በተጨማሪ ካፒታሉን ከ2.1 ቢሊዮን ብር በላይ ለማድረስ የተቻለው የፋይናንስ ተቋም ነው፡፡

 

 

Standard (Image)

የቤልጂየሙ ኦንቴክስ ኩባንያ በኢትዮጵያ የካንቤቢ ዳይፐር ማምረት ጀመረ

$
0
0

 

ሁለት ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ሽያጭ ያለው የካንቤቢ ዳይፐር አምራቹ ኦንቴክስ ኩባንያ በኢትዮጵያ ሥራ ጀመረ፡፡ ከሳሃራ በታች የአፍሪካ አገሮች የመጀመሪያው በሆነው ፋብሪካው፣ በደቂቃ 700 ዳይፐሮች የሚያመርት ማሽኑን የተከለው በሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ነው፡፡ በአሥር ወራት ጊዜ ውስጥም ሁለተኛውን ማምረቻ በመተከል ምርቱን እንደሚያስፋፋ ታውቋል፡፡

የምርቱን 40 በመቶ ለአገር ውስጥ ገበያ፣ 60 በመቶውን ደግሞ ወደ ውጭ ለመላክ የሚያስችለውን የምርት ሥርዓት ዘርግቷል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኩባንያው እያመረተ የሚገኘው ከጠቅላላ የማምረት አቅሙ 60 በመቶው ሲሆን፣ በቅርቡም ሙሉ አቅሙን ተጠቅሞ ማምረት እንደሚጀምር በኢትዮጵያ የኩባንያው ዋና ኃላፊ አቶ ዳንኤል ገብረ ጊዮርጊስ ገልጸዋል፡፡ ወደ ውጭ የሚልከውን የምርት መጠንም ወደ 80 በመቶ ከፍ እንደሚያደርገው፣ ከምሥራቅና ደቡባዊ የአፍሪካ አገሮች የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) አባላት ቅድሚያ እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡

የአዋቂዎችና የልጆች ዳይፐር እንዲሁም የሴቶች የወር አበባ ንጽህና መጠበቂያ (ሞዴስ) ማምረት የሚችለው ፋብሪካው፣ በአሁኑ ወቅት ግን እያመረተ የሚገኘው የሕፃናት ዳይፐር ብቻ ነው፡፡ ወደፊት የገበያውን ሁኔታ እያየ ሌሎችም የሚታወቅባቸውን ምርቶች በኢትዮጵያ እንደሚያመርት፣ አንድ ዳይፐር ለማምረት 14 ዓይነት ጥሬ ዕቃዎች እንደሚያስፈልጉት፣ እነዚህ በሙሉ ግን አገር ውስጥ ስለማይገኙ ከካናዳ፣ ከአሜሪካና ከኮሪያ በማስመጣት እንደሚጠቀም አቶ ዳንኤል አብራርተዋል፡፡

አንደኛው የምርት መስመር ብቻ በዓመት 250 ሚሊዮን ዳይፐር የማምረት አቅም እንዳለው የተናገሩት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የቦርድ ሰብሳቢ   አርከበ ዕቁባይ (ዶ/ር)፣ ኩባንያው እ.ኤ.አ. በ2020 ብቻ 400 ሚሊዮን ዩሮ የሚገመት ምርት ወደ ውጭ እንደሚልክ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ ዳይፐር ለማምረት በግብዓትነት የሚውለውን የፐልፕ ግብዓት በአገር ውስጥ ማምረት በመጀመር ከውጭ የሚገባውን የጥሬ ዕቃ ፍጆታ ለመቀነስ እንደታሰበም ተናግረዋል፡፡

በ27 አገሮች ውስጥ ባሉት ፋብሪካዎቹ ከ11000 በላይ ሠራተኞችን የሚያስተዳድረው ኦንቴክስ ኩባንያ፣ በ110 አገሮች ውስጥ ከሚያሰራጫቸው ብራንዶቹ መካከል ቢቢቲፕስ፣ ባዮቤቢ፣ ፖምፖም፣ ቢግፍራል፣ ካንፔድ፣ አይዲ ኤንድ ሴሬኒቲ እንዲሁም በኢትዮጵያ መመረት የጀመረውን ካንቤቢ ዳይፐርን ጨምሮ በርካታ ምርቶችን እያመረተ የሚገኝ ኩባንያ ነው፡፡

ከሰሃራ በታች ከሚገኙ የአፍሪካ አገሮች ውስጥ በኢትዮጵያ የተከለው ፋብሪካ የመጀመሪያው እንደሆነ በማብራራት፣ ለሌሎች የአፍሪካ አገሮች እዚህ ከተመረተው እንደሚላክላቸው የጠቀሱት አርከበ፣ ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2025 ከአፍሪካ ትልቋ የማኑፋክቸሪንግ እምብርት ለመሆን የያዘችውን ውጥን ለማሳካት፣ እንዲህ ያሉ ግዙፍ የውጭ ኩባንያዎች በብዛት መግባታቸው ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ወደ ኢንዱስትሪ ፓርኮች እንዲገቡ በመንግሥት ጥሪ የተደረገላቸውና ፈቃደኛ የሆኑ የአገር ውስጥ ኩባንያዎችም ተመዝግበው ልዩ ድጋፍ የሚያገኙበት መንገድ እንደተመቻቸ ተናግረዋል፡፡

ለጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ምርት በተገነባው ሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ እስካሁን 18 ኩባንያዎች እንደገቡ ሲታወቅ፣ ከእነዚህ መካከል ስድስቱ ምርቶቻቸውን ወደ ውጭ መላክ ከጀመሩ አምስት ወራት ማስቆጠራቸውን፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ፍጹም አረጋ ገልጸዋል፡፡

የስምንት ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ሽያጭ ያለው የአሜሪካው ፒቪኤች ፓርኩን ከተቀላቀሉ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች መካከል ነው፡፡ የህንዱ ሬይመንድና የሸሚዝ ጨርቆች በማምረት የሚታወቀው ዉሽ ይጠቀሳሉ፡፡ እንደ አቶ ፍጹም ገለጻ፣ እስካሁን ድረስ አገሪቱ ከጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ ከ100 ሚሊዮን ዶላር በላይ አግኝታ አታውቅም፡፡ ይሁንና በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ በሐዋሳ ኢንዱስትሪ ከሚገኙ አምራቾች ብቻ አንድ ቢሊዮን ዶላር ከጨርቃ ጨርቅ የወጪ ንግድ እንደሚገኝ ይጠበቃል፡፡

ከዚህም ባሻገር በአገሪቱ የጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪ ታሪክ የፈጠረው የሥራ ቅጥር ከ53,000 በልጦ አያውቅም፡፡ ይሁንና በቅርቡ ሥራ የጀመረው የሐዋሳ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ብቻውን ለ60,000 ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ይጠበቃል፡፡ እስካሁንም ለ10,000 ዜጎች የሥራ ዕድል አስገኝቷል፡፡

ኦንቴክስ በበኩሉ ከ30 ለሚበልጡ ኢትዮጵያውያን የሥራ ዕድል ፈጥሯል፡፡ በ14 አገሮች ፋብሪካዎቹን አቋቁሞ የሚሠራው ኩባንያው ምርቶቹ በ110 ከተሞች ተደራሽ ናቸው፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስም ትራኮን ትሬዲንግ የድርጅቱ ወኪል በመሆን ምርቱን በአገር ውስጥ ሲያከፋፍል መቆየቱን፣ ኩባንያው ሥራ መጀመሩን ማክሰኞ ሐምሌ 4 ቀን 2009 ዓ.ም. ይፋ ባደረገበት ወቅት አስታውቋል፡፡ ኩባንያው በረጅም ርቀት ሩጫ የምትታወቀውን አትሌት መሠረት ደፋርን የብራንድ አምባሳደር በማድረግ ሰይሟል፡፡

Standard (Image)

አዲሱ የምርት ገበያ አዋጅ የሚፈቅዳቸው አዳዲስ አሠራሮች

$
0
0

 

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ማቋቋሚያ አዋጅ ሰሞኑን ለሁለተኛ ጊዜ እንዲሻሻል መደረጉ ይታወቃል፡፡ የማቋቋሚያ አዋጁ እንደገና እንዲሻሻል የተፈገለው የአገሪቱን የቡና ዘርፍ ብቻም ሳይሆን ወጪ ንግዱን ችግሮች ለማሻሻል ከተጀመረው እንቅስቃሴ ጋር  በማያያዝ ለውጥ እንዲመጣ በማሰብ ነው፡፡

የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ማቋቋሚያ አዋጅ የወጣው በ2000 ዓ.ም. ነበር፡፡ የመጀመሪያው የማሻሻያ አዋጅ ደግሞ በ2007 ዓ.ም. ሥራ ላይ የዋለ ሲሆን፣ ይህ ማሻሻያ ዋናው ዓላማ አንድ ተጨማሪ አንቀጽ ለማከል ተፈልጎ እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡ ባለፈው ሳምንት ለሁለተኛ ጊዜ ተሻሽሎ የፀደቀው አዋጅ ግን በርካታ መሠረታዊ ማሻሻያዎች ተካትተውበታል፡፡

በምርት ገበያው ለተደረገው ማሻሻያ የተሰጠው ምክንያት፣ ተቋሙ የተቋቋመበትን ዓላማ ለማሳካትና ተደራሽነቱን የበለጠ በማስፋት የግብይት ተዋናዮችን ፍላጎት ብሎም አነስተኛ አምራቾችም በምርት ገበያው ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል አሠራር መዘርጋት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡

በቀደመው አዋጅ ውስጥ ከተካተቱ አንቀጾች አሥራ ሁለት ያህል ለውጦች መደረጋቸውን ያመላክታል፡፡ በቀድሞው አዋጅ ውስጥ የነበሩ ከስምንት በላይ ንዑስ አንቀጾች ሙሉ በሙሉ ተሰርዘው በአዲስ ተተክተዋል፡፡ አዳዲስ ንዑሳን አንቀጾችም ተካተዋል፡፡ እንዲህ ያሉ ለውጦችን በመያዝ በፀደቀው አዋጅ መሠረት፣ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከሐምሌ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ አገልግሎት መስጠት እንደጀመረ የምርት ገበያ ባለሥልጣንና የቡና እና ሻይ ልማትና ግብይት ባለሥልጣን በጋራ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡

በተሻሻለው አዋጅ ውስጥ ከተጨመሩት አንቀጾች ውስጥ ቡና በመኪና ላይ  ሳለ ሽያጭ ማካሔድ እንደሚፈቀድ የተጠቀሰው ንዑስ አንቀጽ ይገኝበታል፡፡ ይህም የግብይት  ምርት የጫኑ ተሽከርካሪዎች፣ ጭነቱ በተሽከርካሪው ላይ እንዳለ ተሸጦ ወደ ገዥ እስከሚተላለፍበት ወይም በምርት ማከማቻ መጋዘን እስከሚራገፍበት ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ የሚቆሙበት የተከለለና ደኅንነቱ የተጠበቀ ቦታ እንዲፈጠር ማድረጉ ነው፡፡  በተሻሻለው አዋጅ ‹‹ጥብቅ ማቆያ ሥፍራ›› በማለት የተገለጸ ሲሆን፣ በመኪና ላይ የሚደረገውን ግብይት ለመደገፍ የተካተተ ንዑስ አንቀጽ ነው፡፡

የማሻሻያ አዋጁ ከሰረዛቸው አንቀጾች መካከል አንዱ ተቆጣጣሪ ባለሥልጣን የነበረውን የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለሥልጣንን የሚመለከተው ይገኝበታል፡፡  የዚህ መሥሪያ ቤት ሚና አዲሱ አዋጅ ለንግድ ሚኒስቴር በመሰጠቱ፣ የምርት ገበያው አዲሱ ተቆጣጣሪ ሆኗል፡፡

ስትራቴጂያዊ በሆኑ የአገሪቱ አካባቢዎች ዘመናዊና በቴክኖሎጂ የተደገፉ የምርት ማከማቻ መጋዘኖችና ጥብቅ የማቆያ ሥፍራዎችን መገንባትና ማስተዳደር ለምርት የተሰጠ ኃላፊነት ሆኗል፡፡ በምርት ገበያው ግብይት የሚደረግባቸው ምርቶች የሚጓጓዙበትን ሁኔታ በተመለከተ እንደ አስፈላጊነቱ አግባብነት ካለው የመንግሥት አካል በሚሰጠው ውክልና መሠረት አስገዳጅ መስፈርት ማውጣት፤ ተፈጻሚነቱን የማረጋገጥና ተገቢውን ዕርምጃ የመውሰድ ሥልጣን የሰጠ አንቀጽ በማሻሻያ አዋጁ ተጨምሯል፡፡

በማሻሻያ አዋጁ እንደ መሠረታዊ ለውጥ የሚታየው ሌላው ነጥብ ደግሞ የምርት ገበያውን ካፒታል መጠን የቀየረ መሆኑ ነው፡፡ በቀድሞ አዋጅ የምርት ገበያው የተፈቀደ ካፒታል 250 ሚሊዮን ብር ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 90 ሚሊዮን ብር የሚሆነው ስለመከፈሉ የሚደነግግ ነበር፡፡ በማሻሻያ አዋጁ ግን ይህንን የካፒታል መጠን ሙሉ በሙሉ በመሰረዝ የምርት ገበያው የተፈቀደ ካፒታል 1.25 ቢሊዮን ብር መሆኑን ይገልጻል፡፡ ከዚህ ውስጥ 725 ሚሊዮን ብር  በዓይነትና በጥሬ ገንዘብ እንደተከፈለ በማሳወቅ ማሻሻያ ተደርጓል፡፡

የምርት ገበያው የአባልነት መቀመጫን በተመለከተ ተደንግጎ የነበረውን በማስቀረት “በምርት ገበያው የአባልነት መቀመጫ ሳይኖራቸው ያለአገናኝ በምርት ገበያው የግብይት መድረክ በራሳቸው መገበያየት የሚችሉ ምርት ሻጮች ወይም ገዥዎች የሚስተናገዱበት ዝርዝር ሁኔታ በምርት ገበያው ደንብ ይወሰናል፤” የሚል አንቀጽ እንዲካተትበት ተደርጓል፡፡ ይህም ማሻሻያ መቀመጫ ባላቸው አገበያዮች አስገዳጅ የነበረውን የማገበያየት ሥራ የሚያስቀር ነው፡፡ በቀድሞው አዋጅ ውስጥ የዳይሬክተሮች ቦርድ አሥራ አንድ አባላት የሚኖሩት ሲሆን፣ ሰብሳቢውን ጨምሮ ስድስቱ በሚኒስትሩ፣ እንዲሁም አምስቱ በአባላት እንደሚሾሙ ይገልጻል፡፡ የማሻሻያው አዋጅ ግን ይህ ሙሉ ለሙሉ ተሰርዞ የዳይሬክተሮች ቦርድ አሥራ አንድ አባላት የሚኖሩት ሲሆን፣ ሰብሳቢውን ጨምሮ ስድስቱ በሚኒስቴሩ (በንግድ ሚኒስቴር) ይሰየማሉ፤ አምስቱ በምርት ገበያው ደንብ መሠረት ከአባላት ወይም ከአባል ማኅበራት ይመረጣሉ በሚል ተሻሽሏል፡፡

ስለምርቱ ጥራት ወይም ደረጃ ከምርት ገበያው የምርት የምስክር ወረቀት ሳያገኝ እንዲሁም ስለምርቱ መጠን፣ መነሻ ቦታ ሁኔታና የማከማቻ መጋዘኑ ወይም ጥብቅ ማቆያው የሚገኝበትን ቦታ የሚገልጽ የመጋዘን ማከማቻ ደረሰኝ ሳይኖረው ምርቱን በምርት ገበያው ለግብይት ማቅረብ የተከለከለ ስለመሆኑ የሚገልጽ አዲስ አንቀጽ አለው፡፡ ይህም ምርት ገበያው ጥራትን ከመመዘን አኳያው አዲስ ኃላፊነት የሰጠው እንደሆነ አመላክቷል፡፡

በምርት ገበያው ግብይት የሚደግባቸው ርክክባቸው ወደፊት የሚፈጸምና ወደፊት የሚፈጸሙ ውሎችን በተመለከተ ዝርዝሩ ባለሥልጣኑ በሚወጣው መመርያና በምርት ገበያው የውስጥ ደንብ እንደሚወሰን ተገልጿል፡፡ ማሻሻያ አዋጁ ይህም በሚኒስቴሩ ወይም አግባብነት ባለው የመንግሥት አካል መጽደቁ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ የምርት ገበያው ከግብርና ምርቶች ውጭ ያሉ ውሎችን በማጥናት ሊያገበያይ የሚችልበትን ሥልጣን የሚሰጥ አዲስ ንዑስ አቀንጽ ገብቷል፡፡

ከአዲሱ የቡና ግብይት ማሻሻያ ጋር በተያያዘ፣ የምርት ገበያውን የማቋቋሚያ አዋጅ ለማሻሻል እንደምትክ ከሚቀርቡት ውስጥ ቡናን በአካባቢ መጠሪያ ወይም ዱካ መሸጥ መፈቀዱም የሚጠቀስለት ነው፡፡

በዚህም መሠረት የምርት ገበያው የምርቱን ባለቤት ማንነትና የምርቱን ዱካ ያረጋገጠ የግብይት ሥርዓት ሊዘረጋ እንደሚችል በማሻሻያ አዋጁ ተመልክቷል፡፡ ባለቤትነትንና የምርት ዱካን ባስጠበቀ ሁኔታ በሚደረግ ግብይት መካተት ያለባቸውን ምርቶች ዝርዝር ንግድ ሚኒስቴር በየጊዜው እየከለሰ ሊወስን እንደሚችል ሥልጣን የሚሰጥ አንቀጽ ነው፡፡ በዚህ ሥርዓት ግብይት የሚፈጸምባቸው ምርቶች የመጋዘን ውስጥ የምርት አቀማመጥ፤ አስተዳደርና ርክክብም የምርቱንና የባለቤቱን ወይም አቅራቢውን ማንነት የሚያረጋግጡ መሆን እንደሚኖርበት ተደንግጓል፡፡ በዚህ ሥርዓት ግብይት የሚደረግበትን ምርት እንደጫኑ በምርት ገበያው ጥብቅ ማቆያ ሥፍራ ግብይት የሚካሄድባቸውን ተሽከርካሪዎችና ጭነቶች አቀባበል፣ ናሙና አወሳሰድ፣ ደረጃ አወሳሰን፣ የክብደት ምዘና፣ ግብይት፣ ርክክብና የአደጋ ቁጥጥር አሠራሮችን የተመለከቱ ዝርዝር የአሠራር ሥርዓት በምርት ገበያው ደንብ እንደሚወሰንም የማሻሻያ አዋጁ ያመለክታል፡፡

ከዚህ አዋጅ ጋር ተያይዞ ምርት ገበያው ባለፈው ረቡዕ ሐምሌ 5 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ፣ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ የቡናን የግብይት ሥርዓት ውጤታማና ቀልጣፋ ለማድረግ የሚያስችሉ ዘርፈ ብዙ የማሻሻያ ሥራዎች በመሠራታቸው በዚሁ መሠረት አገልግሎት ጀምሯል፡፡ ለቡና ግብይቱ የምርት ባለቤትነትንና መገኛን ገላጭ የሆነ የመኪና ላይ አዲስ የግብይት ሥርዓት አዘጋጅቶ ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝም የምርት ገበያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ኤርሚያስ እሸቱ ተናግረዋል፡፡

ለእነዚህ አገልግሎት ተጠቃሚዎች ልዩ ሥልጠና እየተሰጣቸው ነው፡፡ የግብይት ሥርዓቱ የሚካሄደው የምርቱንና የምርቱን ባለቤት ማንነት ባስጠበቀ (ገላጭ) መልኩ ሲሆን፣ ምርቱ ወደ መጋዘን ውስጥ ሳይገባ በተከለለ ጥብቅ ማቆያ (Bonded Yard) ውስጥ በመኪና ላይ እንዳለ መሸጥ የሚያስችል ጭምር ነው፡፡ ከመኪና ሽያጭ ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያ በቡና እና ሻይ ባለሥልጣን ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሻፊ ኡመር እንዲህ ላለው አገልግሎቶች የሚሆኑ መመርያዎች ተሰናድተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ያለአገናኝ አባል በቀጥታ መገበያየት ለሚፈልጉ ግለሰቦች፣ የኅብረት ሥራ ማኅበራት፣ የንግድ ድርጅቶችና ሌሎችም አስፈላጊውን መመዘኛዎች እንዲያሟሉ በማድረግ በቀጥታ እንዲሳተፉ የሚያስችል ተደራሽነትን ያረጋገጠ የግብይት መድረክ እንደተዘጋጀም ተገልጿል፡፡ በዚህም መሠረት ያለአገናኝ መገበያየት ለሚፈልጉ ሥልጠና እየተሰጠና ብቃታቸው በፈተና እየተረጋገጠ ወደ ግብይት መድረኩ የሚገቡበት ዝግጅት እየተደረገ ስለመሆኑ አቶ ኤርሚያስ ተናግረዋል፡፡  

ሥርዓቱንም ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችሉ መጠነ ሰፊ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች የተከናወኑ ሲሆን፣ ባለቤትነትን ገላጭ የሆነ የመኪና ላይ ግብይት ለማካሄድ እንዲረዳ ስለ አዲሱ የቡና ግብይት አፈጻጸም ለሚመለከታቸው የግብይት ተዋንያን በአሠራር ሥርዓቱ ላይ ግልጽነትን ሊያረጋግጡ የሚችሉ ሥልጠናዎች እየተሰጡ ስለመሆኑ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተነግሯል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የቡና ምርት ቅበላ በሚካሄድባቸው በሁሉም ቅርንጫፍ መጋዘኖች ለሚሠሩ ሠራተኞች፣ የአዲሱን የቡና ግብይት ሥርዓት አስመልክቶ ሥልጠና እየተሰጠ ነው ተብሏል፡፡

የቡና ግብይት አገልግሎት አሰጣጥ ቀልጣፋና ወጪ ቆጣቢ እንዲሆን ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት ለማከናወን እንዲቻል ከዚህ በፊት ከኢትዮጵያ ምርት ገበያ ተለይቶ ራሱን ችሎ ተቋቁሞ የነበረው የኢትዮጵያ የግብርና ምርቶች የመጋዘን አገልግሎት ድርጅት ተመልሶ ከኢትዮጵያ ምርት ገበያ ጋር እንዲዋሃድ የአደረጃጀት ማሻሻያዎች ስለመደረጋቸውም አቶ ኤርሚያስ ሳያስታውሱ አላለፉም፡፡

አዲሱ የግብይት ሥርዓት የቡናን ግብይት ውጤታማነት ከማስጠበቅ አልፎ በቡና ልማትና ግብይት ዘርፍ የሚታየውን የተንዛዛ እሴት የማይጨምር የግብይት ሰንሰለትን በማሳጠርና ሥር የሰደዱ ችግሮችን በመቅረፍ የቡና የወጪ ንግድን ለማሳደግ የሚኖረው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑን የሥራ ኃላፊዎቹ ገልጸዋል፡፡

አዲሱ አሠራር ሕገወጥ ተግባራትን ለመገደብ የሚያስችል መሆኑን የለገጹት የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር አሌሮ ኦፒው፣ አዲሱን አሠራር በሚፃረር መልኩ የሚሳተፉ ላይ የሚወሰደውን ዕርምጃ በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ አዲሱ አዋጅ አሠራራችንን እንድናቀላጥፍ ያደርጋል ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ለኢትዮጵያ ወጪ ንግድ መሠረታዊ ለውጥ ያመጣል ብለዋል፡፡

የቡናው ዘርፍ ለአገራችን የውጭ ምንዛሪ በማስገኘት የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ መሆኑ የሚታወቅ ስለመሆኑ የገለጹት አቶ ኤርሚያስ፣ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የወጪ ንግድ ግኝቱ እየቀነሰ የግብይት ሥርዓቱም ችግር እያጋጠመው በመጣው ባለፉት ጥቂት ወራት ወደውጭ የተላከው የቡና መጠን ከፍተኛ ሊሆን መቻሉን በመጥቀስ አዲሱ አሠራር ከወዲሁ ውጤት የታየበት እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ የተራዘመ የግብይት ሥርዓት ደረጃዎች መኖራቸው፤ እሴት የማይጨምር ረዥም የቡና ግብይት ሰንሰለት መኖር፤ ቡናችን በዓለም ገበያ ላይ ሊኖረው የሚገባው ተወዳዳሪነት እንዲያሽቆለቁል አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡

አሁን ግን ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል አቅም የሚፈጥር አሠራር ስለመዘርጋቱ የተናገሩት አቶ ሻፊ፣ አገሪቱ በቡና ግብይት የተንዛዛ ሰንሰለት ታወጣ የነበረውን ከፍተኛ ወጪ ይቀንሳል፣ የውጭ ምንዛሪዋም ይጨምራል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ የቡና ግብይት ሰንሰለት መራዘም የቡና የወጪ ንግዱ ወጪ 40 በመቶ አድርሶታል ያሉት አቶ ሻፊ፣ አሁን ሰንሰለቱ ስለሚያጥር ወጪው ይቀንሳል ብለዋል፡፡ ይህም ተወዳዳሪ ዋጋ ያለው ቡና ለማቅረብ ያስችላል ተብሏል፡፡

አዲሱ የቡና ግብይት ሥርዓት በየጊዜው እየዳበረ የሚሄድና ጊዜው የሚፈቅደውን የአሠራር ሥርዓት ተከትሎ የሚቀጥል ነው፡፡ በመሆኑም ሁሉም ባለድርሻ አካላት በባለቤትነት መንፈስ ማሻሻያውን ተግባራዊ እንዲያደርጉ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ አሳስቧል፡፡

 

 

 

Standard (Image)

አቢሲኒያ ባንክ ከ14 ቢሊዮን ብር በላይ በማበደር ዓመቱን አገባደደ የተበላሸ የብድር

$
0
0

አቢሲኒያ ባንክ የ2009 ዓ.ም. በጀት ዓመት የሰጠው የብድር መጠን በ73.3 በመቶ በማሳደግ 14.1 ቢሊዮን ብር ማድረሱን ገለጸ፡፡ የተቀማጭ ገንዘብ መጠኑ ደግሞ ከ 20.7 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱን ተገለጸ፡፡

ባንኩ የ2009 ዓ.ም. በጀት ዓመት አፈጻጸሙን አስመልክቶ ለሪፖርተር በላከው መረጃ በቀዳሚው ዓመት መጨረሻ ላይ 8.14 ደርሶበት የነበረውን የብድር መጠን በአራተኛ ደረጃ በማሳደግ በባንኩ ታሪክ ከፍኛ ሊባል የሚችለውን ውጤት አስመዝግቧል፡፡

በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ግን የብድር መጠኑን በከፍተኛ ደረጃ ከማሳየቱም በላይ ባንኩ የተቀማጭ ገንዘብ መጠኑን ለማሳደግ ባካሄደው እንቅስቃሴ በቀዳሚው ዓመት መጨረሻ ላይ አሰባስቦት ከነበረው ተቀማጭ ገንዘብ 52 በመቶ በመጨመር በ2009 ዓ.ም በጀት ዓመት 20.7 ቢሊዮን ደርሷል፡፡ አምና በተመሳሳይ ወቅት የተቀማጭ ገንዘብ መጠኑ 13.6 ቢሊዮን ብር ነበር፡፡

ለተቀማጭ ገንዘብ መጠኑ ዕድገት አስተዋጽኦ ካበረከቱት ዕርምጃዎች አንዱ በበጀት አውታሩ 27 አዳዲስ ቅርንጫፎች መክፈቱ ነው፡፡ አዳዲሶቹ ቅርንጫፎች መክፈት በበጀት አውታሩ መጨረሻ ላይ ባንኩ አገልግሎት የሚሰጥባቸውን ቁጥር በ26 በመቶ በማሳደግ 233 አድርሶለታል፡፡  

እንደባንኩ መረጃ ለተቀማጭ ገንዘብ መጠኑን ዕድገት የባንኩን አስቀማጭ ደንበኞች ቁጥር ከቀዳሚው ዓመት በ28 በመቶ ማደግ በመቻሉ ነው፡፡ እንደ መረጃው በ2009 መጨረሻ ላይ 585,735 የነበረው ደንበኞች በተጠናቀቀው በጀት 750 ሺሕ መድረሱ ለአብነት ተጠቅሷል፡፡

ባንኩ በዚህን ያህል ደረጃ የብድር መጠኑ ቢያድግም በበጀት ዓመቱ ያስመዘገበው የተበላሸ ብድር መጠን () 1.41 በመቶ ብቻ ነው፡፡

በቀደመው ዓመት ደግሞ ዝቅተኛ የተበላሸ ብድር መጠን ካላቸው ባንኮች ውስጥ አንዱ እንደነበር የተጠቀሰ ሲሆን በወቅቱ የተበላ ብድር መጠኑ 1.9 በመቶ ነበር፡፡ በዚህ ዓመት ግን ይህንንም ወደ 1.4 በመቶ መውረዱ እንዲሁም ዝቅተኛ የተበላሸ ብድር መጠን ካላቸው ባንኮች ተርታ ተሠልፏል፡፡

በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ድንጋጌ ባንኮች የተበላሸ ብድር መጠየቃቸው ከ5 በመቶ መብጥ የለበትም፡፡ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተገኘው ወቅታዊ መረጃ እንደሚያሳየው ደግሞ የ2009 በጀት ዓመት የባንኮች አማካይ የተበላሸ የብድር መጠን 3 በመቶ ነው፡፡

የ2009 በጀት ዓመት የትርፍ መጠኑን በተመለከተ የተለካው መረጃ ደግሞ ባንኩ ከታክስና ፕሮቬዥን ማይቀነስ 801 ሚሊዮን ብር አግኝቻለሁ ብሏል፡፡ ፕሮቪዥን ሲቀነስ ከታክስ በፊት ከ730 ሚሊዮን ብር በላይ ትርፍ ሊያመዘግብ እንደሚችል ይገመታል፡፡

አቢሲኒያ ባንክ በበጀት ዓመቱ መጀመርያ ላይ የባንኩን ካፒታል ወደ 4 ቢሊዮን ብር ለማድረስ የወጠነ ሲሆን በዘርፉ መሠረት የተከፈለ ካፒታሉን እየሠራ ነው፡፡ ይህንን ውሳኔ ዓመት ባለፈበት ወቅት የባንኩ የተከፈለ ካፒታል 1.27 ቢሊዮን ብር ሲሆን ለ2009 ዓ.ምም መጨረሻ ላይ ደግሞ በ41 በመቶ በማድረግ 1.8 ቢሊዮን ብር ለማድረስ መቻሉን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ባንኩ በአሁኑ ወቅት 5,005 ሠራተኞች ይዞ እየተንቀሳቀሰ ነው ይህም 20.8 በመቶ ሚሊዮን ነው፡፡ 

Standard (Image)

የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን የ6.3 ቢሊዮን ብር በጀት ፀደቀለት

$
0
0
  • በ2009 በጀት ዓመት ከ5.4 ቢሊዮን ብር በላይ ተመድቦለት ነበር

የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን በ2010 በጀት ዓመት 101 ፕሮጀክቶችን ለመተግበር መነሳቱንና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርም የ6.38 ቢሊዮን ብር በጀት እንዳፀደቀለት አስታወቀ፡፡

ባለሥልጣኑ በ2010 በጀት ዓመት ለማከናወን ካቀዳቸው 101 ፕሮጀክቶች ውስጥ 30ዎቹ ካለፈው በጀት ዓመት የዞሩ ናቸው፡፡ እንደ ባለሥልጣኑ መረጃ ከሆነ፣ በበጀት ዓመቱ 32 አዳዲስ የመንገድ ግንባታዎችን የሚያከናውን ሲሆን፣ ከ20/80 እና ከ40/60 የኮንዶሚኒየም ግንባታዎች ጋር የተያያዙ 18 የመንገድ ሥራዎችንም እንደሚገነባ አስታውቋል፡፡ የተጓተቱ የስምንት መንገዶች ግንባታም በዚሁ በጀት ዓመት ከሚከናወኑ ሥራዎች ውስጥ ተካትተዋል፡፡

በያዝነው በጀት ዓመት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለባለሥልጣኑ 5.1 ቢሊዮን ብር የሚለቅለት ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 4.83 ቢሊዮን ብር ለካፒታል በጀት፣ 264.29 ሚሊዮን ብር ደግሞ ለመደበኛ በጀት የሚውል ነው፡፡

ቀሪው ለባለሥልጣኑ የተፈቀደው በጀት የሚሸፈነው ከመንገድ ፈንድና ከቻይና ኤግዚም ባንክ በተገኘ የብድር ገንዘብ ነው፡፡ እንደ ባለሥልጣኑ ከሆነ፣ ከቻይና ኤግዚም ባንክ የተፈቀደውና በባለሥልጣኑ በጀት ውስጥ የተካተተው ገንዘብ 1.21 ቢሊዮን ብር ሲሆን፣ የመንገድ ፈንድ ጽሕፈት ቤት የሚበጅትለት ደግሞ 67.38 ሚሊዮን ብር በመሆኑ፣ በድምሩ 6.38 ቢሊዮን ብር በጀት ለዚህ ዓመት ሥራዎቹ ማከናወኛ ሊመደብለት ችሏል፡፡

በ2010 በጀት ዓመት ይጀመራሉ ተብለው ከተያዙት አዳዲስ የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክቶች ውስጥ ከፑሽኪን አደባባይ-ጎፋ ማዞሪያ፣ ቃሊቲ ቀለበት መንገድ አደባባይ-ቱሉ ዲምቱ አደባባይ፣ ቃሊቲ ቀለበት መንገድ አደባባይ-ቡልቡላ ቂሊንጦ አደባባይ 2ኛው ቀለበት መንገድ፣ ከአያት ኮንዶሚኒየም-ቦሌ በሻሌ፣ ከሽሮ ሜዳ-ቁስቋም፣ ከአበበ ቢቂላ ስታዲየም መግቢያ-አዲሱ ሚካኤል-ሰሜን ሆቴል የሚከናወኑት ግንባታዎች ይጠቀሳሉ፡፡

ከመብራት ኃይል ኮንዶሚኒየም-ቦሌ ሆምስ፣ ከሃይኒከን-ወርቁ ሰፈር-ቀለበት መንገድ፣ ከሃያሁለት-ዋና መንገድ-አዲሱ ብሔራዊ ስታዲየም፣ አየር ጤና-አደባባይ-ወለቴ-ዓለምገና አደባባይ፣ ከአውቶቡስ ተራ-ፓስተር፣ ከመሳለሚያ-ኮካ አደባባይ፣ ቦሌ አያት 1፣ 2፣ 3 እና 4 ኮንዶሚኒየም በዚሁ ዕቅድ ውስጥ እንደተካተቱ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከሃያሁለት ማዞሪያ-እንግሊዝ ኤምባሲ ‹‹በራስ ደስታ ሆስፒታል-ቀጨኔ መድኃኔዓለም አስፓልት ፕሮጀክት፣ ሽሮ ሜዳ-ቁስቋም ፕሮጀክት ዲዛይናቸው ተጠናቆ በ2010 በጀት ዓመት ግንባታቸው ከሚጀመሩት መንገዶች መካከል ይገኛሉ፡፡

ከመንገድ ግንባታ ሥራው ባሻገር፣ በ2009 በጀት ዓመት በብዛት ሲያካሒድ የነበረውን የመንገድ ጥገና ሥራም በአዲሱ በጀት ዓመትም እንደሚቀጥልበት ባለሥልጣኑ አስታውቋል፡፡ ተከታታይና ወቅታዊነቱን የጠበቀ የመንገድ ጥገና ሥራ ለማከናወን ከከተማው አስተዳደር 150 ሚሊዮን ብር የተመደበለት ሲሆን፣ ከመንገድ ፈንድ ጽሕፈት ቤት 67.3 ሚሊዮን ብር እንደሚያገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ለመንገድ ጥገና ሥራው ከከተማ አስተዳደሩና ከመንገድ ፈንድ ጽሕፈት ቤት የተገኘው በጠቅላላው ከ273 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን ገንዘብ ሥራ ላይ ይውላል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የጠጠር መንገድ ግንባታን ጨምሮ በባለሥልጣኑ አቅም በተለያዩ የአዲስ አበባ አካባቢዎች ለሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶችና ለኢንዱስትሪ መንደሮች የአገናኝ መንገዶች ግንባታ ማካሔጃ የ110 ሚሊዮን ብር በጀት እንደተያዘም ባለሥልጣኑ ጠቅሷል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን በ2009 በጀት ዓመት ከአስተዳደሩ፣ ከመንገድ ፈንድና ከብድር ከተገኘ ገንዘብ ውስጥ የ5.4 ቢሊዮን ብር በጀት ተለቆለት ሲንቀሳቀስ ነበር፡፡ ከዚህ ውስጥ 5.2 ቢሊዮን ብር ለካፒታል በጀት፣ 166 ሚሊዮን ብር ለመደበኛ እና 61 ሚሊዮን ብር ደግሞ ለጥገና በመመደብ ዓመቱን አሳልፏል፡፡ በ2009 በጀት ዓመት ከፀደቀለት ከዚህ በጀት ውጪ፣ ለመንገድ ጥገና ሥራዎች የ280 ሚሊዮን ብር ተጨማሪ ገንዘብ ተፈቅዶለት እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ ይህንንም ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ሥራ ላይ እንዳዋለው አስታውቋል፡፡  

Standard (Image)

አኅጉራዊው የቱሪዝም ፍሰት ለአገሮች ኢኮኖሚ የኋላ ደጀንነቱን እያሳየ ነው

$
0
0
  • ከዓለም አቀፍ አሥር ጎብኚዎች አራቱ አፍሪካውያን ናቸው
  • አዲስ አበባ ከሆቴል ፎረም የ5.8 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝታለች

ከጥቂት ቀናት በፊት ይፋ የተደረገውና በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የንግድና የልማት ጉባዔ (UNCTAD) የተሰናዳው ሪፖርት፣ የአፍሪካ ቱሪስቶች ለአኅጉሪቱ የቱሪዝም ዘርፍ እያበረከቱ የሚገኙትን አስተዋጽኦ ተንኗል፡፡ አፍሪካያውን ቱሪስቶች በሚጎበኟቸው አገሮች የኢኮኖሚ ደጀን በመሆን ለሥራ ዕድልና ለውጭ ምንዛሪ ገቢ ማደግ ሚናቸው እየጎላ እንደመጣም ሪፖርቱ አትቷል፡፡

ባለፈው ሳምንት በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ በመገኘት ሪፖርቱን ያቀረቡት (በተመድ) የንግድና ልማት ጉባዔ የአፍሪካ ክፍል ዋና ኃላፊ ጁኒየር ዴቪስ (ዶ/ር) ሪፖርቱን ይፋ ሲያደርጉ እንዳስታወቁት ከሆነ፣ እያደገ የመጣው የአፍሪካ ቱሪዝም ኢንዱስትሪ ባለፉት 20 ዓመታት ውስጥ ከ21 ሚሊዮን በላይ ለሚቆጠሩ ዜጎች የሥራ ዕድል አስገኝቷል፡፡ ይህም ማለት ከእያንዳንዱ 14 የሥራ ዕድል ውስጥ አንዱ በቱሪዝም መስክ የተፈጠረ እንደሆነ ያመላክታል ብለዋል፡፡ በመጪዎቹ አሥር ዓመታት ውስጥም 12 ሚሊዮን ተጨማሪ የሥራ ዕድሎች ከዚሁ ከቱሪዝም ዘርፍ እንደሚመነጩ የተመድ ሪፖርት ይተነብያል፡፡

ይኼ እንዲሆን ምንክንያት ከሆኑት መካከል፣ ዜጎች በአፍሪካ አገሮች ውስጥ ከአንዱ ወደ ሌላው የሚያደርጉት ጉብኝት አንዱ የሚጠቀስ ነጥብ ነው፡፡ ተመድ ‹‹Tourism for Transformative and Inclusive Growth›› በተሰኘው ሪፖርቱ ውስጥ በጥናት አጣቅሶ እንዳሰፈረው፣ የአፍሪካ አገሮችን ከጎበኙ አሥር ዓለም አቀፍ ጎብኚዎች ውስጥ አራቱ አፍሪካውያን ሆነዋል፡፡

በአፍሪካ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው የቱሪዝም ኢንዱስትሪ በዓለም አቀፍ ጎብኚዎች በኩል የስድስት በመቶ እንዲሁም በቱሪዝም ገቢ ረገድ የዘጠኝ በመቶ ዓመታዊ ዕድገት እንዲታይበት ያስቻሉ ከተባሉት ምክንያቶች መካከል አንዱ፣ አፍሪካውያን በአፍሪካ አገሮች መካከል የሚያደርጉት ጉብኝትና ዝውውር ነው፡፡ ምንም እንኳ አፍሪካውያን በአኅጉራቸው የሚያደርጉት እንቅስቃሴና ጉብኝት አስዋጽኦው እየጎላ መምጣቱ ቢነገርለትም፣ በአንፃሩ ከሌሎች አኳያ ሲታይ ግን ዝቅተኛ ነው፡፡ ለአብነት ጁኒየር ዴቪስ የሚጠቅሱት በአውሮፓ አገሮች መካከል አውሮፓውያኑ ይጎላሉ፡፡ ከአውሮፓ ዜጎች አምስቱ አራቱ እዚያው አውሮፓ ውስጥ በመዘዋወርና በመጎብኘት የአኅጉሩን የቱሪዝም እንቅስቃሴ አጠናክረዋል ያሉት ዴቪስ፣ በአፍሪካ ይህ አነስተኛም ቢሆን እያደገ መምጣቱን ግን ጠቅሰዋል፡፡

ከዚህም ባሻገር በአፍሪካ በተመዘገበው የ52 በመቶ የአገልግሎት ወጪ ንግድ ውስጥ ከግማሽ በላዩ የተመዘገበው ከቱሪዝም ዘርፍ መሆኑም ሌላኛው አወንታዊ ጎኑ ነው፡፡ ምንም እንኳ ሪፖርቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ የበርካታ አገሮችን የቅርብ ጊዜ መረጃ ማካተት እንዳልተቻለ ዴቪስ ቢያብራሩም፣ በአፍሪካ ከቱሪዝም ዘርፍ ብቻ የ47 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ሊመዘገብ ችሏል፡፡

ምንም እንኳ የዚህን ዓመት የተጠቃለለ የቱሪዝም ዘርፍ አፈጻጸም መረጃ ከባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሪፖርተር ለማግኘት ሞክሮ፣ ገና እየተጠናቀረ እንደሚገኝ ቢገለጽለትም ከዘርፉ በተጠናቀቀው የ2009 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ውስጥ፣ ከ685 ሺሕ በላይ የውጭ ጎብኝዎች ከ2.6 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሪ ገቢ መገኘቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ይሁንና ለ2009 በጀት ዓመት የተያዘው አጠቃላይ የገቢ መጠን ከ3.7 ቢሊዮን ዶላር በላይ እንደሚሆን መታቀዱም ይታወሳል፡፡ ይሁንና እንዲህ ያለውን ዓይነት ወቅታዊ መረጃ የተመድ ተቋማት ማግኘት እንዳልቻሉ እየጠቀሱ ነው፡፡ ዴቪስ እንደሚገልጹት፣ ኢትዮጵያንና ሌሎችም አገሮች ሪፖርቱ በሚጠናቀርበት ወቅት የተጠየቋቸውን የዓምና እና የካቻምና የዘርፉን መረጃዎች ሊያቀርቡ ባለመቻላቸው ምክንያት የሪፖርቱ ዳራ እ.ኤ.አ. እስከ 2014 የነበረውን የአፍሪካን የቱሪዝም እንቅስቃሴ በማሳየት ላይ ብቻ እንዲገደብ ምክንያት ሆኗል ብለዋል፡፡

     የመረጃው አለመካተት ደግሞ በአፍሪካ የታዩ ወቅታዊ ክስተቶች በዘርፉ ላይ ያሳደሩትን ተፅዕኖ በሚገባ ለማሳየትና ለመተንተን አለማስቻሉ አንዱ ጉድለት ሆኗል፡፡ ለአብነትም በኢትዮጵያ የተከሰተው ሕዝባዊ አመጽ፣ በቱሪዝም ዘርፉ ላይ የነበረውን አሉታዊ ጫና በዝርዝር ማሳየት ባይቻልም፣ በርካታ አገሮች የጉዞ ክልከላዎችንና ማስጠንቀቂያዎችን ሲያወጡ መታየታቸው ዘርፉ ላይ ተፅዕኖ እንደሚኖረው የሪፖርቱ አቅራቢ ገልጸዋል፡፡

ይህም ቢባል ግን በአፍሪካ የተከሰቱ ፖለቲካዊ ግጭቶችና ጦርነቶች፣ የበሽታ ወረርሽኞችና ሌሎችም ክስተቶች በጅምላ አፍሪካን የጎዱበት ክስተት መስተናገዱን ዴቪስ ሲጠቅሱ ዋቢ ያደረጉት የኢቦላ ወረርሽኝን ነበር፡፡ በምዕራብ አፍሪካ የተከሰተው ይህ በሽታ፣ በዋናነት የጎዳው ሦስት አገሮችን ቢሆንም ከደቡብ እስከ ምሥራቅ አፍሪካ የተዛመተ የጎንዮሽ ተፅዕኖ አሳድሮ አልፏል፡፡ በሽታው ባልታየባቸው አገሮች ውስጥ ሳይቀር ቱሪስት አመንጪ አገሮች የጉዞ ዕቀባ በመጣል የቱሪዝም ዘርፉን ጉዳት ላይ ሊጥል የሚችል ዕርምጃ ሲወስዱ ታይተዋል፡፡

በኬንያ የተደረጉ የአሸባሪዎች አደጋ ወይም በናይጄሪያ በአሸባሪው ቦኮሐራም ወይም በሶማሊያ የተደረጉ የአልሻባብ ጥቃቶች መላ አፍሪካን የሚመለከቱ በማስመሰል የሚወሰዱ የጉዞ ማሳሰቢያዎችና ማስጠንቀቂያዎች የአፍሪካ ቱሪዝም ዘርፍ የሚፈታተኑ ተደርገው ቢታሰቡም፣ ቱሪስቶች ግን በዚህ ሁሉ ሳይሸበሩ እየመጡ እንደሚገኙ ዴቪስ አጣቅሰዋል፡፡ ይህም ቢባል ግን ቱሪስቶች እንደልብ ወደ አፍሪካ እንዳይመጡ አስተዋጽኦ እያደረጉ እንደሚገኙ ከሚነገርላቸው ውጫዊ ምክንያቶች (በቀጥታ ከዘርፉ ጋር ተያያዥ ያልሆኑ ጉዳዮች) መካከል፣ የአካባቢ ብክለት፣ የመሬት ባለቤትነት መብት በአግባቡ አለመከበር፣ የመሬት ተጠቃሚነት፣ የቆሻሻ አወጋገድ ሥርዓት አለመዳበር፣ እንዲሁም ለዘመናት የቆዩት የበሽታና የግጭት ክስተቶች ይገኙበታል፡፡ እንዲህ ያሉትን ጨምሮ ሌሎችም የዘርፉ ድክመቶች ተደራርበው የአኅጉሪቱ የቱሪዝም ዘርፍ ከዝቅተኛ ደረጃ በመነሳት ላይ የሚገኝ ታዳጊ ዘርፍ እንዲሆን አስገድደውታል፡፡

በመሆኑም እንደ ዛምቢያና ሩዋንዳ ያሉ የባህር በር የሌላቸው አገሮች ከሚያስተናግዷቸው የውጭ ጎብኚዎች ውስጥ ከ70 እስከ 80 በመቶ የሚደርሱት ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች ከሚመጡ ዜጎች እንዲሆኑ ማስቻሉን ዴቪስ ጠቅሰዋል፡፡ እንደ ሩዋንዳ ያሉት አገሮች ከኮንፈረንስ ቱሪዝም በተለይ ተጠቃሚ በመሆን የሚጠቀሱ ሲሆኑ፣ የአፍሪካውያን የገቢ መጠን እየጨመረ መምጣቱም በእርስ በርስ የቱሪዝም እንቅስቃሴው ውስጥ ትልቁን ድርሻ ለማበርከት የተጫወተው ሚና እንደሚጎላ ተብራርቷል፡፡ እንደ ሞሮኮ፣ ቱኒዝያ፣ ደቡብ አፍሪካና ሞሪሺየስ ያሉ አገሮች በቱሪዝም ዘርፍ ውስ ጥራት ያላቸውን የመሠረተ ልማት አውታሮች በመገንባት ረገድ በአፍሪካ ጉልህ ኢንቨስትመንት በማድረግ ላይ የሚገኙ አገሮች ተብለዋል፡፡

በአንፃሩ ከአፍሪካ አገሮች ውስጥ እንደ ሲሺዬልስ፣ ካቦ ቨርዴ እንዲሁም ሞሪሺየስ ከአፍሪካ አገሮች ዋና ዋና የቱሪዝም ዘርፍ ተጠቃሚ አገሮች ግንባር ቀደምቶቹ ሆነዋል፡፡ ሲሺዬልስ ከኢኮኖሚዋ 61.5 በመቶውን ድርሻ የያዘው ቱሪዝም ነው፡፡ ካቦ ቨርዴና ሞሪሺየስም በ43.4 በመቶና በ26.7 በመቶ የኢኮኖሚ ድርሻ ተከታዮቹን ደረጃዎች በመያዝ በአፍሪካ ተቀዳሚ የዘርፉ ተጠቃሚ አገሮች ሆነዋል፡፡ በአንፃሩ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ በርካታ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርፆችን በዓለም ያስመዘገቡ፣ ነገር ግን እንደሚገባቸው ዘርፉን ያልተጠቀሙበትና ያላስተዋወቁ አገሮች ለኢኮኖሚያቸው የሚያበረክተውን ድርሻ አነሳ እንዳደረገው ከሪፖርቱ መረዳት ይቻላል፡፡    

በሌላ በኩል በአፍሪካ እየተዘወተረ የመጣው የሆቴሎች ኢንቨስትመንትን የተመለከተው ስብሰባም አስተዋጽኦ እያደረገ እንደሚገኝ ተጠቀሷል፡፡ በአፍሪካ የሆቴል ኢንቨስትመንትን የተመለከቱ መደበኛ ጉባዔዎችን የሚያሰናዳው ቤንች ኤቨንትስ የተባለው የእንግሊዙ ኩባንያ ባወጣው ሪፖርት መሠረትም፣ ጉባዔውን ያስተናገዱ አገሮች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከ16.8 ሚሊዮን ዶላር ያላነሰ ገቢ ማግኘት እንደቻሉ አትቷል፡፡

ቤንች ኤቨንትስ ግራንት ቶርንቶን በተባለ አጥኚ ተቋም አማካይት ባስጠናው የዳሰሳ ጥናት መሠረት፣ አዲስ አበባ እ.ኤ.አ. በ2014 እና በ2015 በተከታታይ ባስተናገደችው የአፍሪካ ሆቴል ኢንቨስትመንት ፎረም አማካይነት ብቻ የ2.4 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ስታገኝ፣ ከሌሎች ፈርጀ ብዙ ጠቀሜታዎች አኳያ ያገኘችው ገቢ ከ3.4 ሚሊዮን ዶላር በላይ እንደሆነ ተመልክቷል፡፡ አዲስ አበባ ጨምሮ ካዛብላንካ፣ ናይሮቢ (ሁለት ጊዜ ጉባዔውን አስተናግዳለች)፣ አዲስ አበባ (ሁለት ጊዜ ጉባዔውን አስተናግዳለች)፣ ሎሜና ኪጋሊ ከተሞችም በስብሰባው አማካይነት በተፈጠሩ ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ምንጮች የየራሳቸውን ገቢ ማግኘት የቻሉ ከተሞች ናቸው፡፡ 

Standard (Image)

ከ880 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ በማስገኘት ቡና የወጪ ንግዱን በበላይነት መምራቱን ቀጥሏል

$
0
0

ከስድስት ዓመታት ቆይታ በኋላ ከፍተኛው እንደሆነ የተነገረለትን የ881 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ገቢ ያስገኘው ቡና፣ ወደ ውጭ ከሚላኩ ምርቶች ከፍተኛውን ድርሻ በመያዝ መሪነቱን ቀጥሏል፡፡

ሪፖርተር ከኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ልማትና ግብይት ባለሥልጣን ባገኘው መረጃ መሠረት፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ወደ ውጭ ከተላከው ከ225 ሺሕ ቶን በላይ ቡና፣ 881.6 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቷል፡፡ በመጠንም ሆነ በገቢ ረገድ የ2009 በጀት አፈጻጸም ከዓምናውም ሆነ ከስድስት ዓመት በፊት ከተመዘገበው ይልቅ ከፍተኛው ሊባል እንደሚችል የሚያመላክት ውጤት ታይቶበታል፡፡

ዓምና የተመዘገው የቡና የወጪ ንግድ አፈጻጸም በገቢ ረገድ 722 ሚሊዮን ዶላር እንደነበርና ወደ ውጭ የተላከው ቡና መጠንም 198 ሺሕ ቶን እንደነበር ቡናና ሻይ ባለሥልጣን አስታውሷል፡፡ በመሆኑም ከዘንድሮው አፈጻጸም አኳያ በውጭ ምንዛሪ ገቢ ረገድ የ159.6 ሚሊዮን ዶላር እንዲሁም በመጠን ረገድም የ27 ሺሕ ቶን ጭማሪ ተመዝግቦበታል፡፡ በባለሥልጣኑ መረጃ መሠረት በመጠንም በገንዘብም ይገኛል ተብሎ ከታቀደው ውስጥ የ93 በመቶ ውጤት ተመዝገቧል፡፡

በ2009 ዓ.ም. ወደ ውጭ ይላካል ተብሎ የሚጠበቀው የቡና መጠን 241 ሺሕ ቶን ሲሆን፣ ይገኛል የተባለው የውጭ ምንዛሪ ገቢም 941 ሚሊዮን ዶላር ገንዘብ ነበር፡፡ ይሁንና 225.3 ሺሕ ቶን በመላክ፣ በገቢ ረገድም 881 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማስገኘት ቡና እንደወትሮው ከወጪ ንግድ ምርቶች ከምንጊዜውም ይልቅ ቀዳሚውን ድርሻ በመያዝ እንዲጓዝ የቻለበት ዓመት ሆኖለታል፡፡

ከስድስት ዓመት በፊት በነበረው አኃዝ መሠረት፣ ሪፖርተርን ጨምሮ በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ መገናኛ ብዙኃን የዘገቡት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የተገኘበት የቡና መጠን ከዘንድሮው ጋር ተቀራራቢ ነበር፡፡ በገቢ ረገድም ከአሁኑ ብዙም የራቀ አልነበረም፡፡ እ.ኤ.አ. በ2010/11 ወደ ውጭ የተላከው የቡና መጠን 200 ሺሕ ነበር፡፡ ከዚህ ቡና የተገኘው የውጭ ምንዛሪ ገቢም 841.6 ሚሊዮን ዶላር እንደነበር መዘገቡ ይታወሳል፡፡ ይህ አኃዝ ከዚህ በፊት ከቡና ያልተገኘ በመሆኑ ከፍተኛው አፈጻጸም እንደነበር መጠቀሱም አይዘነጋም፡፡

በወቅቱ ለቡናው ከፍተኛ ውጤት ተጠቃሽ ምክንያቶች ሆነው ሲቀርቡ ከነበሩት መካከል የብራዚልና የኮሎምቢያ የቡና አቅርቦት መቀነሱ፣ የዓለም የሸቀጥ ዋጋ መጨመሩና የግብርና ምርቶች ዋጋም ማሻቀብ መጀመሩ ዋና ዋናዎቹ ምክንያቶች ነበሩ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በወቅቱ ገና ወደ ሥራ የገባውና አዲስ የነበረው የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ድርሻም ተወስቷል፡፡ በግብይቱ መድረክ ግልጽነትን ለማስፈን በመቻሉ የቡና ንግድ እንቅስቃሴ እንዲቀላጠፍ ማስቻሉም ሲነገርለት ነበር፡፡ ይህም ሆኖ በመጀመሪያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ሰነድ ውስጥ በተጠቀሰው መሠረት ወደ ውጭ እንደሚላክ ይታሰብ የነበረው የቡና መጠን 700 ሺሕ ቶን እንደነበር ይታወሳል፡፡

ይሁንና ከስምንት ዓመታት ቆይታ በኋላ የቡና ግብይት ላይ ከማሳ እስከ ወጪ ንግድ መዳረሻ ድረስ ባሉት የምርትና የግብይት ሰንሰለቶች ውስጥ በርካታ እንቅፋቶች በማጋጠማቸው መንግሥት የአሠራር ለውጥ እንዲያደረግ አስገድደውታል፡፡ በመሆኑም የምርት ገበያውን የመቋቋሚያ አዋጅ ለሁለተኛ ጊዜ በማሻሻል እንዲሁም የግብይትና የምርት ቁጥጥር ሥርዓትን የሚደነግገውንም ሕግ በማስተካከል አዳዲስ ሥርዓቶችን ለመተግበር ተገዷል፡፡ ለአብነትም ነጋዴዎች ምርት ከጫኑበት መኪና ላይ ሳለ በቀጥታ ወደ ላኪዎች እንዲደርስ የሚያደርጉበት አሠራር ተፈጥሯል፡፡ በዚህ መሠረት ከዚህ ቀደም በምርት ገበያው የነበረው በመደበኛ አባልነት ወይም በወንበር ባላቸው አባላትና በግብይት ፈጻሚ አባላት መካከል የነበረውን የግብይት ልዩነት የሚቀይር አካሄድ መተግበር ተጀምሯል፡፡ እንዲህ ያሉት ዕርምጃዎች የቡናን የወጪ ንግድ አፈጻጸም ለማሻሻል ብቻም ሳይሆን ለውጭ ገበያ መቅረብ የሚገባው ምርት በወቅቱ ለማቅረብ እንዲቻል የተንዛዙ አሠራሮችን የሚቀንስ እንደሆነም መንግሥት አስታውቋል፡፡

 

Standard (Image)

ንብ ባንክ በ680 ሚሊዮን ብር የጨረታ ዋጋ የገዛውን ሕንፃ ተረከበ

$
0
0

በፍርድ ቤት ትዕዛዝ እንዲሸጥ የተወሰነውን ባለሰባት ወለል ሕንፃ የጨረታ ሒደቱን በ680 ሚሊዮን ብር በማሸነፍ የገዛው ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ፣ የሚጠበቅበትን ገንዘብ ለመንግሥት ገቢ በማድረግ ሕንፃውን እንደተረከበ አስታወቀ፡፡

ከባንኩ የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው፣ በጨረታ ያሸነፈበትን ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ገቢ በማድረግ ሕንፃውን ለመረከብ የበቃው ማክሰኞ፣ ሐምሌ 11 ቀን 2009 ዓ.ም. ነበር፡፡

ንብ ባንክ በጨረታ የገዛው ሕንፃ ከስምንት ዓመታት በፊት ለግንባታ በሰጠው ብድር የተገነባ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፣ በዚህ ሕንፃ ግንባታ ከባንኩ ከ55 ሚሊዮን ብር በላይ የተበደሩትና በአራጣ አበዳሪነት ተከሰው የተፈረደባቸው አቶ ከበደ ተሠራ፣ ንብረታቸው እንዲወረስ በፍርድ ቤት መወሰኑ ይታወቃል፡፡ በዚህ መሠረት ባንኩ ያበደረውን ገንዘብ ለማስመለስ ከገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ጋር ለዓመታት የዘለቀ የይገባኛል ክርክር ሲያካሒድ ቆይቷል፡፡ በመጨረሻም ሕንፃው በሐራጅ እንዲሸጥ ሲወሰን፣ ባንኩ ከሌሎች ተጫራቾች ጋር ተወዳዳሮ በከፍተኛ ገንዘብ ሊገዛው ችሏል፡፡

በአሁኑ ወቅት ለዋና መሥሪያ ቤትነት እያስገነባው የሚገኘው ከ30 ወለል በላይ የሆነው ሕንፃ እስኪጠናቀቅ ድረስ፣ አራት ኪሎ አካባቢ የሚገኘውን ይህንን ሕንፃ በጊዜያዊነት ለዋና መሥሪያ ቤትነት ሊጠቀምበት አቅዷል፡፡ በመሆኑም በጨረታ የገዛው ሕንፃ የማጠናቀቂያ ግንባታ በቅርቡ ይጀመራል ተብሏል፡፡

 የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ሕጋዊ ባልሆነ የገንዘብ እንቅስቃሴ አማካይነት የተገኘ ንብረት በመሆኑ ንብ ባንክ ሕንፃውን መሸጥ እንደማይችል በማመልከቱ፣ ባለሥልጣኑና ባንኩ በዚህ ጭብጥ ላይ ከስድስት ዓመታት በላይ የፈጀ የፍርድ ቤት ክርክር ሲያካሔዱ ቆይተዋል፡፡

ንብ ባንክ ለሕንፃው ግንባታ እንዲውል ያበደረው 55 ሚሊዮን ብር፣ በአሁኑ ወቅት እስከነወለዱ ከ120 ሚሊዮን ብር በላይ ደርሷል፡፡ እንደ ባንኩ መረጃ ሕንፃውን ከገዛ በኋላ ባንኩ፣ የሰጠውን ብድር ከነወለዱ በመጠየቅ እንደሚቀበል ይጠበቃል፡፡

አራት ኪሎ አካባቢ፣ ከቱሪስት ሆቴል አጠገብ በሚገኝ ቦታ ከዘጠኝ ዓመት በፊት ግንባታው ተጀምሮ በማጠናቀቂያው ምዕራፍ ላይ የሚገኘው ባለ ስምንት ወለል ሕንፃ፣ መከታ ሪል ስቴት ሲያስገነባው የነበረ ነው፡፡ ይሁንና መከታ ሪል ስቴት ለሕንፃው ግንባታ የተበደረውን ገንዘብ በወቅቱ መመለስ ባለመቻሉ፣ ባንኩ በሕጉ መሠረት ሕንፃውን በሐራጅ ለመሸጥ ማስታወቂያ አውጥቶ ወደ ዕርምጃ ለመግባት መንቀሳቀስ ሲጀምር፣ የሪል ስቴት ኩባንያው ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ በማለቱ፣ ሕንፃውን ሽጦ ገንዘቡን ለማስመለስ ሳይችል ይቀራል፡፡

የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ያቀረበው አቤቱታም ንብረቱ ወይ ሕንፃው በአራጣ የተያዘ፣ ሕጋዊ ባልሆነ የገንዘብ ልውውጥ የተገኘና ይወረስ የሚል ጥያቄ የቀረበበት በመሆኑ ንብ ባንክ ሊሸጠው አይችልም በማለቱ ነው፡፡ ይህ አቤቱታ የቀረበው በመጋቢት ወር 2003 ዓ.ም. ሲሆን፣ በገቢዎችና በጉምሩክ ባለሥልጣንና በባንኩ መካከል ለዓመታት ለዘለቀው ክርክርም መነሻ ሆኖ መቆየቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

በባለሥልጣኑ አቤቱታ መሠረት፣ ባንኩ ንብረቱን ለመሸጥ ያደረገው እንቅስቃሴ በጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ ይታገዳል፡፡ የዕግድ ትዕዛዝ ሲወጣም የጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔን በመቃወም ባንኩ በበኩሉ ዕግዱን በመቃወም ንብረቱን ለመሸጥ መብት እንዳለው በመከራከር በመጨረሻም በተካሔደው ጨረታ መሠረት ሕንፃውን በ680 ሚሊዮን ብር በመግዛት የገዛ ንብረቱ ለማድረግ በቅቷል፡፡

 

Standard (Image)

ከስድስት ቢሊዮን ዶላር በላይ ይጠቅበት የነበረው የወጪ ንግድ ግማሹን አሳክቷል

$
0
0

-በመጪው ዓመት ስምንት ቢሊዮን ዶላር ይጠበቃል

በተሸኘው የ2009 በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ ይጠበቅ የነበረው ገቢ ከ6.7 ቢሊዮን ዶላር በላይ ነበር፡፡ ይሁንና ከሦስት ቢሊዮን ዶላር ብዙም ፈቅ ያላለ የውጭ ምንዛሪ ገቢ ከዘርፉ መገኘቱን ከፋይናንስና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር የተገኙ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

ምንም እንኳ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተሻሻ ቢመጣም የወጪ ንግዱ አፈጻጸም ከሚጠበቀው በታች ሲያሽቆለቁል ቆይቷል፡፡ ለአብነት እንኳ በ2009 በጀት ዓመት ሰባት ወራት ውስጥ የታየው አፈጻጸም ከፍተኛው ቅናሽ የተመዘገገበት እንደነበር የንግድ ሚኒስቴር ሪፖርት አሳይቷል፡፡ በ2009 ዓ.ም. ሰባት ወራት ውስጥ 2.488 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ለማግኘት ታቅዶ በአፈፃፀም የተመዘገበው 1.423 ቢሊዮን ዶላር ወይም 57 በመቶ ብቻ  ነበር፡፡

በዚሁ አካሔድ የቀጠለው የአገሪቱ አጠቃላይ የወጪ ንግድ ሁኔታ በዓመቱ ማጠቃለያም ከታቀደው በግማሽ ያነሰ አፈጻጸም በማሳየት አዲሱን በጀት ዓመት ጀምሯል፡፡ ለውጭ ገበያ ከሚቀርቡ ሸቀጦች ውስጥ ምንም እንኳ ቡና የተሻለ አፈጻጸም ቢያሳይም እስከ ሦስተኛው ሩብ ዓመት አጋማሽ ድረስ የነበረው የወጪ ንግድ እንቅስቃሴ የተንቀራፈፈና ከሚጠበቀው ይልቅ አነስተኛ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ይሁንና እስከ ሰኔ መጨረሻ ድረስ በነበረው አካሔድ ግን የቡና የወጪ ንግድ ከሚጠበቀው የ940 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ 881 ሚሊዮን ዶላር በማስገኘት ከዕቅዱ የ93 በመቶውን፣ ከሌላውም ጊዜ ይበልጥ ውጤት በማስገኘት ዓመቱን ደምድሟል፡፡

የቅባት እህሎች የኤክስፖርት አፈፃጸም ከዕቅድ አንፃርም ሆነ ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃጸር ዝቅተኛ የሆነበት ምክንያት የወቅቱ የሰሊጥ ምርት አቅርቦትና ሽኝት በመቀነሱ ምክንያት ላኪዎች በቂ ምርት አግኝተው በመግዛት የገቡትን ኮንትራት በተገቢው መንገድ ሊወጡ ባለመቻላቸው እንደሆነ ንግድ ሚኒስቴር ያወጣው ሪፖርት አመላክቶ ነበር፡፡

ከቁም ከብትና ከሥጋ ለዕቅድ አፈፃፀሙ ዝቅተኛ መሆን እንደምክንያት በዋናነት የምንወስዳቸው በዘርፉ ውስጥ ልምዱ ያላቸው ላኪዎች በብድር አቅርቦት ምክንያት ወደ ገበያ ማቅረብ አለመቻላቸው፣ ሕገ ወጥ ንግዱን መግታት አለመቻሉ  ይጠቀሳል፡፡ የሥጋ ምርትም ከዕቅዱ አኳያ ማሳካት ያልቻለ ሌላው ንዑስ ዘርፍ ሲሆን፣ ዋና ዋና ችግሮች ተብለው ሲጠቀሱለት ከቆዩት ውስጥ በዕቅድ ታሳቢ የተደረጉት ኤክስፖርት ቄራዎችና ላኪዎች በሙሉ አቅማቸው አለመሥራቸው እና የእርድ እንስሳት አቅርቦት እጥረት ዋና ዋና ከሚባሉት ውስጥ ሲጠቀሱ የቆዩ ችግሮች ናቸው፡፡

ለአበባ የወጪ ንግድ እንቅስቃሴ መዳከምም ምክንያቶች አልታጡም፡፡ ከጥቅምት አጋማሽ ጀምሮ የአየር ጠባይ ለውጥ ምክንያት ሆኖት ቆጦ ነበር፡፡ በወቅቱ ቅዝቃዜው ከዜሮ በታች ሦስት ዲግሪ ሴልሺየስ ከመውረዱ ምርቱ ቶሎ ማገገም አለመቻሉ እና የተወሰኑ አምራች ድርጅቶች ዝርያ በመቀየር ላይ በመሆናቸው ወደ ማምረት ሒደቱ መግባት አለመቻላቸውም ተዘግቧልል፡፡ ለአትክልትና ፍራፍሬም ተመሳሳዩ የአየር ጠባይ ለውጥ ምክንያት ሆኖ የኤክስፖርት አፈጻጸሙ እንዲቀንስ ሰበብ ሆኖታል፡፡

ለቆዳና ጨርቃጨርቅም እንዲሁ የኩባንያ የውስጥ አስተዳደራዊ ችግሮች፣ የጥሬ ዕጦት፣ የሥራ ማስኬጃ ካፒታል እጥረት፣ የገዥዎች ፍላጎት መቀነስ ከሚጠቀሱ ዋና ዋና ችግሮች መካከል ንግድ ሚኒስቴር ሲያቀርባቸው የሰነበቱ የወጪ ንግዱ ችግሮች ናቸው፡፡ ምንም እንኳ የተጠቃለለውን የ2009 በጀት ዓመት ሪፖርት ከንግድ ሚኒስቴር ለማግኘት የተደረገው ጥረት ባይሳካም፣ ከዓምናው የወጪ ንግድ አፈጻጸም ይልቅ ጥቂት ለውጥ እንደታየ ይታመናል፡፡

በዚህ አኳኋን የአገሪቱ የወጪ ንግድ አፈጻጸም ከሚጠበቀውም ከቀድምት ዓመታትም እየቀነሰ የመጣባቸው ውስጣዊና ውጫዊ ምክንያቶች ተዘርዝረው ቢቀርቡም፣ መንግሥት በዚህ ዓመት ከወጪ ንግድ የሚጠብቀው ገቢ ስምንት ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትሩ አብርሃም ተከስተ (ዶ/ር) በዚህ ሳምንት አስታውቀዋል፡፡ ይህም በአምስቱ ዓመት የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ሰነድ ውስጥ በተቀመጠው መሠረት ሲሆን፣ በዕቅድ ዘመኑ መጨረሻም ከ14 ቢሊዮን ዶላር ያላነሰ የወጪ ንግድ ገቢ እንደሚጠበቅ በሰነዱ ተመልክቷል፡፡

የሸቀጦች ወጪ ንግድ ትንበያ ከ2008 እስከ 2012 (ገቢ በሚሊዮን ዶላር)

ዝርዝር

መነሻ ዓመት

ትንበያ

የ2007 አፈጻጸም

2007

2008

2009

2010

2011

2012

ጠቅላላ የወጪ ንግድ ገቢ

3,019.3

4,884.6

6,780.3

8,747.8

11,035.6

13,909.1

የግብርና ምርቶች ወጪ ንግድ

2,255.9

3,277.4

4,213.0

5,239.2

6,338.4

7,663.9

መደበኛ የግብርና ምርቶች

1,978.9

2,907

3,738

4,556

5,441

6,481

ቡና

780.5

1,022.4

1,339.4

1,607.2

1,870.8

2,173.9

የቅባት እህሎች

510.1

904.5

1,134.2

1,413.3

1,710.0

2,048.6

ጥራጥሬዎች

219.9

318.8

398.5

498.1

622.6

778.3

አትክልትና ፍራፍሬ

47.6

69.0

86.2

107.8

129.4

155.2

የቁም ከብት

148.5

267.3

337.9

425.7

534.7

673.8

ጫት

272.4

324.7

441.6

504.3

572.9

650.8

አበባ

203.1

260.0

339.0

440.3

571.1

742.4

ሌሎች የግብርና ምርቶች

73.9

110.7

136.2

242.4

326.8

440.8

የኢንዱስትሪ ምርቶች ወጪ ንግድ

419.9

992.7

1,852.6

2,332.2

3,118.6

4,199.2

ማኑፋክቸሪንግ

377.1

864.6

1,313.6

1,801.3

2,534.5

3,556.8

ቆዳና የቆዳ ውጤቶች

131.6

206.6

272.7

368.1

505.0

706.5

ስጋና የስጋ ውጤቶች

92.8

112.3

146.0

192.7

263.4

374.1

የጨርቃጨርቅ ውጤቶች

98.9

184.0

270.5

397.9

556.7

778.8

ስኳርና ሞላሰስ

0.0

138.0

265.0

327.0

435.8

586.2

ምግብና መጠጥ

21.5

25.7

44.3

88.6

154.3

268.0

ኬሚካል

18.9

27.5

49.8

62.9

81.1

101.3

ፋርማሲቲካልስ

2.7

29.6

54.8

69.0

89.2

111.4

የብረታብረትና ኢንጅነሪንግ ውጤቶች

10.5

92.1

121.1

181.5

302.9

448.0

የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክስ ውጤቶች

0.2

48.9

89.4

113.6

146.0

182.4

ኤሌክትሪክ ሀይል

42.8

128.0

539.0

530.9

584.0

642.4

የማዕድን ወጪ ንግድ

345.73

500.35

780.75

1,049.91

1,470.39

2,011.01

ምንጭ፡- ብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን፣ የሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን የተጠቃለለ ሰነድ 

Standard (Image)

የጭነት ተሽከርካሪዎች አምራቹ ኩባንያ የ440 ሚሊዮን ብር የወጪ ንግድ ገቢ ለማግኘት አቅዷል

$
0
0

 

  • ከ160 በላይ እዚሁ የተገጣጠሙ ተሽከርካሪዎችን ለገበያ አቅርቧል

ፍራከን ኢቲ አውቶሞቲቭ ኢንጂነሪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ እስካሁን ካመረታቸውና ከገጣጠማቸው 162 ተሽከርካሪዎች ባሻገር፣ የዚህን ዓመት ዕቅዱን ጨምሮ በመጪዎቹ ሦስት ዓመታት ውስጥ ከ3700 በላይ ተሽከርካሪዎችን በአገር ውስጥ በማምረት፣ ከዚህ ውስጥም ከ10 እስከ 29 በመቶዎቹን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ማቀዱን ይፋ አድርጓል፡፡ ከሁለት ዓመት በኋላ ከወጪ ንግድ የሚያገኘው ገቢ በዓመት ወደ 440 ሚሊዮን ብር ከፍ እንደሚልም የኩባንያው ኃላፊዎች አስታውቀዋል፡፡ 

ከዛሬ ሦስት ዓመት በፊት ማለትም እ.ኤ.አ. በ2014 የተቋቋመ ኩባንያ ነው፡፡ በአውቶሞቲቭ የኢንዱስትሪው መስክ ለመሰማራት በ20 ሚሊዮን ብር ካፒታል የተመሠረተው ይህ ኩባንያ፣ በአብላጫው የተለያዩ ከባድ ተሽከርካሪዎችን በመገጣጠም ሥራ ላይ የተሰማራ ነው፡፡

ከመገጣጠም ሥራው ባሻገር፣ የተለያዩ የተሽከርካሪ አካላትን በተለያዩ ዲዛይኖች በመሥራትም ይታወቃል፡፡ ከአዲስ አበባ 32 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሱሉልታ ከተማ በተገነባው የኩባንያው ፋብሪካ ውስጥ የሚጣጠሙት ተሽከርካሪዎች፣ ከአገር ውስጥ ገበያ ባሻገር ለውጭ ገበያ ለማቅረብ በማሰብ ጭምር እንደተገነባ የኩባንያው ዋና ሥራ አስኪያጅ ፍራንሲስኮ ቫይሎን ይገልጻሉ፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ ተሽከርካሪዎችን የሚገጣጥሙ ኩባንያዎች ብዙ ሲነገርላቸው ቆይተዋል፡፡ ፍራንከን ግን ከዚህ በተለየ መንገድ ሲጓዝ ቆይቶ ስለመኖሩ እንኳ በይፋ የታወቀው በቅርቡ ነበር፡፡ ቅዳሜ፣ ሐምሌ 8 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሄደ ሥነ ሥርዓት፣ ስለሥራ እንቅስቃሴው፣ በትራንስፖርትና በሌሎች ተያያዥ ቢዝነሶች ለመምከር ባሰናዳው መድረክ ወቅት ህልውናውን በይፋ አሳውቋል፡፡ ደንበኞቹን ጭምር ባሳተፈበት በዚህ መድረክ፣ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ለመነጋገርና እግረ መንገዱንም ምርቶቹን ለማስተዋወቅ በማሰብ በተዘጋገጀው ፕሮግራም ወቅት ስለኩባንያው ለመገንዘብ ተችሏል፡፡

ፍራንከን ኩባንያ ድምፁን አጥፍቶ በሥራው ላይ በማተኮር መቆየቱ ብቻም ሳይሆን፣ በፍራንከን የተገጣጠሙትን ተሽከርካሪዎችም ለተለያዩ የአፍሪካ አገሮች ገበያ ማቅረቡም ሌላኛው አስገራሚ ነገር ነበር፡፡

ለሽያጭ ከቀረቡት ተሽከርካሪዎችና ሌሎች ምርቶች ውስጥ ባለፉት ሦስት ዓመታት ወደ ሦስት የአፍሪካ አገሮች ተልከው ከተሸጡ ተሽከርካሪዎች የውጭ ምንዛሪ ገቢ ተገኝቷል፡፡ እንዲህ ባለው ቢዝነዝ ቀዳሚ ሊያሰኘው የሚችለውን የተሽከርካሪዎች የወጪ ንግድ ለማበረታት ድርጅቱ የተለያዩ ስትራቴጂዎች እንደቀረፀ ያስታወቀ ሲሆን፣ ለውጭ ገበያ ያቀረባቸው ምርቶች ገጣጥሞ የሸጠው በአብዛኛው ከኢትዮጵያ ውጭ ባሉት ኩባንያዎቹ አማካይነት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የተመረቱት ተሽከርካሪዎች ግን በአብዛኛው ለአገር ውስጥ ገበያ ስለመዋላቸውን የኩባንያው ኃላፊዎች ይገልጻሉ፡፡

ተሽከርካሪዎችን በኢትዮጵያ ፋብሪካው ገጣጥሞ ወደ ውጭ ለመላክ ቢሞክርም፣  አንዳንድ አሠራሮች ጋሬጣ እንደሆኑበት፣ በዚህም በኢትዮጵያ የተገጣጠመ መሆኑን የሚጠይቅ ምልክትና ስም በግድ በሌሎች አገሮች አምራቾች በኩል ለመሸጥ እንዲያስገድደውም ይጠቅሳሉ፡፡

በዕለቱ የምክክር መድረክ በዘርፉ የበለጠ የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት ከተፈለገ ማነቆ ሆነው ያስቸገሩ አሠራሮች ሊቀረፉ ይገባቸዋል ተብሏል፡፡ በዚሁ አግባብ ከተጠቀሱት ውስጥ የቫውቸር አሠራር አንዱ ነው፡፡ በአገሪቱ ውስጥ የሚሠራበት የቫውቸር ሥርዓት ከ1,300 በላይ ኩባንያዎችን በሥሩ ለሚያስተዳድረው ይህ ተቋም በተለይም የተሽከርካሪ ዕቃዎችን ለማስገባት የሚያስቸገር በመሆኑ፣ ይህንን አሠራር በሚመች መንገድ መቀየር አንዱ መፍትሔ እንደሆነ ኃላፊዎቹ ይጠቅሳሉ፡፡

ሌላው ችግር ሆኖ የቀረበው የባንኮች አሠራር ሲሆን፣ በሦስተኛ ደረጃ እንደማነቆ የሚቆጠረው የውጭ ምንዛሪ እጥረት ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ክፍተቶች ከተሻሻሉ፣ አሁን ላይ ያሉት የመገጣጠም ችግሮች ተቀርፈው የኢትዮጵያ ማምረቻውን ማዕከል በማድረግ ምርቱን በቀጥታ ወደ ውጭ መላክ የሚጀምርበት ውጥን ሊሳካ እንደሚችልም ኩባንያው አስታውቋል፡፡

ይህም ሆኖ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ የሚመረቱትን ተሽከርካሪዎች ወደ ውጭ ለመላክ ዝግጅት ላይ ነን ያሉን አቶ ፍራንሲስኮ፣ በቅርቡ አምስት የጭነት ተሽከርካሪዎችን ወደ ኡጋንዳ ለመላክ ዝግጅት እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ ከምክክሩ በኋላም ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ምርቱን ለውጭ ገበያ እንዳያቀርብ ማነቆ ሆነውብኛል ያላቸውን ችግሮችን ለመፈታት ቃል በመግባት አሠራሮች ተስተካክለው ምርቱን ከኢትዮጵያ መላክ እንጀምራለን የሚል ተስፋ ፈንጥቋል፡፡

የፍራንከን ምርት ወደ አገራቸው ካስገቡ የኮንጎ ደንበኞች መካከል አንዱ በአዲስ አበባ ቆይታቸው ወቅት እንደገለጹት፣ እስካሁን ከፍራከን ኩባንያ ሰባት ተሽከርካሪዎችን ገዝተዋል፡፡ የተሽከርካሪዎችን ጥራትና ብቃት በማየትም ተጨማሪ ተሽከርካሪዎችን ለመግዛት እንደተዘጋጁ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በአፍሪካ ከፍተኛ የወርቅ ክምችት ከሚገኝባቸው አገሮች አንዷ በሆነችው ኮንጎ፣ የጭነት ማመላለስ ሥራ ለመሥራት ተስማሚ ሆነው የተገኙትን የፍራኮንን ተሽከርካሪዎች በብዛት ለመግዛት ተጨማሪ የአራት ዓመት ኮንትራት የተፈራረመ ኩባንያ፣ ከሽያጭ በኋላ ከኩባንያው የሚያገኘውን የአገልግሎት አቅርቦትም እንደሚያገኝ አረጋግጦ ተመልሷል፡፡

በዕለቱ ‹‹የምንሠራውን እወቁልን›› በሚል የተዘጋጀ መሆኑን በመግለጽ ቀዝቀዝ ብሎ የተጀመረው ምክክር የኩባንያውን የሥራ ሒደት፣ ተግባርና ራዕይ የተመለከቱ አስተያየቶች ከየአቅጣጫው ሲሰነዘሩ ታይቷል፡፡ የኩባንያው የእስካሁኑ ጉዞ የሁሉንም ስሜት የገዛና በዕለቱ ከተገኙ የተለያዩ ተቋማት ተወካዮችም ለኩባንያው ድጋፍ እንደሚሰጡ ቃል እስኪገቡ ድረስ የሚያነሳሳ መድረክ ነበር፡፡ በተለይ ባንኮች ተሽከርካሪዎችን ገጥሞ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የሚያደርገውን ጥረት በገንዘብ አቅርቦት ረገድ ድጋፍ እንደሚሰጡ ተናግረዋል፡፡

ኩባንያው በዋናነት አነስተኛ፣ መካከለኛና ትላልቅ ተሽከርካሪዎችን የራሱን የአሠራር ስልት ተጠቅሞ የሚያመርት ሲሆን፣ ከእነዚህ ተሽከርካሪዎች ባሻገርም የማጓጓዣ ካርጎ አልትራክስ ለማምረት አቅዷል፡፡ እንደ ሲሚንቶ ያሉ ምርቶችን የሚያጓጉዙ ከባድ ተሽከርካሪዎችን በመሠራት ካስረከባቸው መካከል አንዱ ዳንጎቴ ሲሚንቶ ፋብሪካ መሆኑም ታውቋል፡፡

እንደ አቶ ፍራንሲስኮ ገለጻ፣ በጭነት ተሽከርካሪ መስክ በዘርፉ ያለውን የጊዜውን ቴክኖሎጂ በሙሉ በመጠቀም የሚገጣጥሙ በርካታ ባለሙያዎችን ያፈራ ኩባንያ ለመሆን በመብቃቱ ብቻም ሳይሆን፣ ለውጭ ገበያ ተስማሚነትን ብቻም ሳይሆን የጥራት ደረጃን በመጠበቅ ጭምር ለማምረት የቻለ ኩባንያ ኢትዮጵያ ውስጥ ተፈጥሯል ብለዋል፡፡ ‹‹የምንሠራው ሥራ ውጤታማ መሆኑን የሚያረጋግጥልን ምርቶቻችንን ተረክበው እየተቀጠሙ ያሉ የተለያዩ የአፍሪካ አገሮች አሁንም ተጨማሪ ምርቶችን እንድናቀርብላቸው ትዕዛዝ መስጠታቸው ነው፤›› ብለዋል፡፡

ነገር ግን ለዚህ ሥራ ፋይናንስ መሠረታዊ በመሆኑ ከተለያዩ ባንኮች ጋር የፋይናንስ አቅርቦት እያገኘ መሆኑን የገለጹት አቶ ፍራንሲስኮ፣ ‹‹በምንፈልገው ደረጃ የፋይናንስ አቅርቦት እያገኘን አይደለም፤›› በማለት ብዙ እንደሚቀር ጠቅሰዋል፡፡

በዕለቱ ከተለያዩ ባንኮች የተወከሉ ባለሙያዎችም በመገኘታቸው፣ የኩባንያው ሥራ አስኪያጅ አሠራራቸው ምን እንደሚመስል ባስረዱበት ወቅት፣ ኩባንያውን ለመደገፍ ቃል ገብተዋል፡፡ ባንኮች አሠራራቸውን ያስተካክሉ የሚል ጠንካራ አስተያየት የተደመጠበት ይህ መድረክ፣ በተለይ ውጤታማ ለሆኑ ኩባንያዎች ተገቢውን የፋይናንስ አቅርቦት እንዲያገኙና በቅልጥፍና እንዲስተናገዱ ማድረግ የግድ ይላል ብለዋል፡፡

በመድረኩ ላይ ስለፍራከን የተናገሩት የኦሮሚያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ተወካይ፣ የባንኮችን አሠራር ከተቹት ውስጥ አንዱ ነበሩ፡፡

በዕለቱ የተገኙት የዳሸን፣ የዘመንና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተወካዮችም የኩባንያውን እንቅስቃሴ በማወደስ አብሮ ለመሥራት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የዘመን ባንክ ተወካይ በበኩላቸው፣ ባንኩ የብድር አሠራሩን ለማዘመን የተለያዩ የብድር አሠጣጥ ዘዴዎች በመተግበር እየሠራ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል፡፡ ዓብይ ችግሮች በመሆን ከተጠቀሱት ውስጥ አንዱ የሆነው ኩባንያቸው አገር በቀል ኩባንያ እንደመሆኑ መጠን ለምርታቸው የሚሆን ጥሬ ዕቃ ከቀረጥ ነፃ ለማስገባት መቸገሩ ነው፡፡

ኩባንያው ለሚገጣጥማቸው ተሽከርካሪዎች ግብዓቶችን ከውጭ ያስገባ እንጂ፣ የተሽከርካሪዎቹን ዲዛይን በኩባንያው ባለሙያዎች እዚሁ እያዘጋጀ የሚጠቀም ነው፡፡ ይህም የሚገጣጠሙት ተሽከርካሪዎች ለኢትዮጵያም ለሌሎች የአፍሪካ አገሮች መልካ ምድራዊ ሁኔታዎችና የመንገዶች ጠባይ ያላቸው ተስማሚነት ታሳቢ ተደርጎ እንደሆነ ተብራርቷል፡፡

ባለፉት አራት ዓመታት የኩባንያው ጉዞ የአይቪኮ ቴክኖሎጂን ከቻይና ቴክሎጂዎች ጋር በማጣመር የጭነት ተሽከርከሪዎችን በራሱ የንግድ ስያሜ በማምረት በአገር ውስጥና ከኢትየጵያ ውጭም ለኡጋንዳ፣ ለታንዛኒያና ለኮንጎ ገበያ ለማቅረብ ችሏል፡፡

ከኢትዮጵያ ምርቱን ለመላክ ከሌሎች መንግሥት አካላት በተለይ ከብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ደጋፊ የሚሻ ስለመሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ የብረታ ብረት ኢንዲስትሪዎች ልማት ኢንስቲትዩቱ ተወካዮችም ኩባንያው የገጠሙትን ችግሮች ለመፍታት አስፈላጊውን ድጋፍ ለማደረግ እንችላለን የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

እንደ አቶ ፍራንሲስኮ ገለጻ ከሆነ፣ አሁን የተለያዩ አገር ቴክኖሎጂዎችንና ግብዓቶችን በመጠቀም የምንሠራው ሥራ ብዙ ዜጎች ቴክኖሎጂውን በመቅሰም ውጤታማ እንዲሆኑ እያስቻለ በመሆኑ፣ ዘርፉን በመደገፍ ለውጥ ማምጣት ያስፈልጋል፡፡

 

Standard (Image)

የእንስሳትን የወጪ ንግድ የሚያግዝ የመለያና የእንስሳት ዱካ መከታተያ ፕሮጀክት ይፋ ተደረገ

$
0
0

በአሜሪካ መንግሥት የ32 ሚሊዮን ብር ድጋፍ የቁም እንስሳት የልየታ፣ የዱካ መከታተያ አገር አቀፍ ፕሮጀክት በትግራይና በኦሮሚያ ክልል በሙከራ ደረጃ መተግበር የጀመረው ፕሮጀክት በአምስት ዓመት ጊዜ ውስጥ አገር አቀፍ እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

በእንስሳትና ዓሣ ሀብት ሚኒስቴር ማክሰኞ፣ ሐምሌ 18 ቀን 2009 ዓ.ም. ይፋ የተደረገው ይህ ፕሮጀክት፣ ላለፉት ሁለት ዓመታት ተኩል ዝግጅት ሲደረግበት መቆየቱን፣ በሚኒስቴሩ የእንስሳት ልየታ፣ ክትትልና ጤንነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሃድጉ ማንደፍሮ (ዶ/ር) አስታውቀዋል፡፡

የቁም እንስሳትን ለመለየት እንዲያስችል በጂኦግራፊክ ኢንፎርሜሽን ሲስተም የሚታገዝና በጆሯቸው ላይ የሚንጠለጠል መለያ ከፈረንሣይ በማስመጣት ጥቅም ላይ ማዋል መጀመሩን ለሪፖርተር የጠቀሱት ኃላፊው፣ እስካሁን ከ250 ሺሕ በላይ የቁም እንስሳት በዚህ ቴክኖሎጂ መሠረት ተለይተው ክትትል እየተደረገባቸው እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

ከመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ግብይት መፈጸሚያ ጣቢያዎች ጀምሮ፣ በእንስሳት ማቆያዎች፣ በሕክምና መስጫዎች፣ በኤክስፖርት ቄራዎችና በሌሎችም የአቅርቦት ሰንሰለቶች ውስጥ እንስሳቱ በሚያልፉባቸው ሒደቶች ውስጥ ከየት ተነስተው የት እንደደረሱ ዱካቸውን የሚከታተለው ይህ ሥርዓት፣ ኢትዮጵያ ወደ ውጭ የምትልካቸው እንስሳት የጤንነት ደረጃዎች ስለማሟላታቸው፣ የሚላከው የሥጋ ምርትም ተገቢውን የጥራትና የጤንነት መሥፈርቶች ስለማሟላቱ ለማረጋገጥ እንደሚረዳ ተጠቅሷል፡፡

በኢትዮጵያ የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ኤጀንሲ (ዩኤስኤኣይዲ) ተወካይ ስቴፈን ሞሪን ስለፕሮጀክቱ አስፈላጊነት በአብራሩበት ወቅት በዓለም በሥጋ አምራችነት የሚታወቁ እንደ ብራዚል ያሉ አገሮች ከሥጋ የወጪ ንግዳቸው ላይ ያጋጠማቸውን ከፍተኛ የማጭበርበር ተግባር ያጋለጠው እንዲህ ያለው የምርት መለያና መከታተያ ሥርዓት እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊትም በአውሮፓ የፈረስና የአህያ ሥጋ የበሬ ሥጋ በማስመሰል ሲልኩ የነበሩ አገሮች ላይ ከፍተኛ ኪሳራ ያደረሰ ቀውስ መከሰቱን አስታውሰዋል፡፡

እንዲህ ያሉ ችግሮችን ከምንጫቸው ተከታትሎ ለመቆጣጠርና የጤና ችግሮች ሲከሰቱም የትኛው አካባቢ የሚገኙ እንስሳት ለበሽታ ተጋላጭ እንደሆኑ በ24 ሰዓት ውስጥ ለማረጋገጥ ያስችላል የተባለው ይህ ሥርዓት፣ ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ሲያጋጥማት የቆየውን የኤክስፖርት ክልከላ ችግሮች እንደሚቀርፍ ታምኖበታል፡፡ አቶ ሃድጉ እንዳስታወቁት፣ ኢትዮጵያ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገሮች የምትልከው የሥጋ ምርት በተደጋጋሚ ውድቅ ሲደረግ ቆይቷል፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ተገቢውን የጤና መሥፈርት አላሟሉም ተብለው ውድቅ ሲደረጉ በነበሩት ምርቶች ሳቢያ፣ በቅርቡ ሪፖርት በተደረገ መረጃ ብቻ እንኳ እስከ 35 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ኪሳራ እንዳጋጠማት አቶ ሃድጉ ጠቅሰዋል፡፡

የአገሪቱን የቁም እንስሳትም ሆነ የሥጋ ምርት የወጪ ንግድ ያዘምናል የተባለው ይህ ፕሮጀክት፣ በቦረና የእንስሳት ኮሪዶር እንዲሁም በአበርገሌ የግብይት አካባቢዎች በሙከራ ደረጃ እየተተገበረ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡ ይህ ሥርዓት እንዲጀመር ምክንያት ከሆኑት መካከል የቁም እንስሳትም ሆነ የሥጋ ውጤቶችን የሚገዙ አገሮች ስለሚላክላቸው እንስሳትና የሥጋ ምርት መረጃ እንዲሰጣቸው ጥያቄ እያቀረቡ መሆናቸውም አንዱ ሆኖ ቀርቧል፡፡ ተጠባባቂዋ የዩኤስኤኣይዲ የኢትዮጵያ ሚሽን ዳይሬክተር ዲያና ሳልሴዶ እንዳስታወቁት፣ የአሜሪካ መንግሥት 1.4 ሚሊዮን ዶላር ኢንቨስት ያደረገበት ይህ ፕሮጀክት፣ ወደፊት ውጤታማቱ ታይቶ በመላ አገሪቱ ሊስፋፋ የሚችልበት ውጤት ይጠበቃል፡፡ ለፕሮጀክቱ የሚውሉትን የሶፍትዌር ፕሮግራሞችን ጨምሮ ልዩ ልዩ የቴክኒክና የሥልጠና ድጋፎች ከአሜሪካ መንግሥት ባሻገር የአውሮፓ አገሮች፣ የዓለም የእርሻና የምግብ ድርጅት (ኤፍኤኦ) እና ሌሎችም ተሳትፎ ማድረጋቸውን የእንስሳትና የዓሣ ሀብት ሚኒስቴር ጠቅሷል፡፡  

ኢትዮጵያ በእንስሳት ሀብት ብዛት ከዓለም አገሮች በዘጠነኛ ደረጃ እንደምትቀመጥ ሚኒስቴሩ ይፋ ቢያደርግም፣ በእንስሳት ሀብቷ ብዙም ያልተጠቀመች መሆኗ ይታያል፡፡ በየጊዜው ደጋግሞ የሚመጣው ድርቅና የእንስሳት በሽታ አርብቶ አደሮችን ክፉኛ እየተፈታተናቸው እንደሚገኝ ዓለም አቀፍ የረድኤት ድርጅቶች ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡

 

Standard (Image)

የንግድ ባንክ ሠራተኞች ለቤት ግዥ ክፍያ የተጠየቁትን ዋስትና ባንኩ ቢያነሳም መድን ድርጅት ገንዘባቸውን ሊመልስ እንዳልቻለ ገለጹ

$
0
0

- መድን ድርጅት በበኩሉ ከውል ውጭ ጥያቄ እንደቀረበበት በመግለጽ ከባንኩ ጋር ውይይት ላይ ነኝ ብሏል

- በዓመት ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ ለሞርጌጅ ዋስትና ይከፈላል ተብሏል

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለሠራተኞቹ ማበረታቻ ይሆን ዘንድ በረጅም ጊዜ የሚከፈል የቤት መግዣ ብድር ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ በዚህ አግባብ ተጠቃሚ የነበሩ ከ3,000 በላይ ሠራተኞች ለብድሩ ዋስትና ይሆን ዘንድ የገቡትን የመድን ዋስትና ግን ከስድስት ወራት በፊት መነሳቱን፣ ለሠራተኞቹ የተሰጠው ብድርም ሳይከፈል ይቀራል የሚል ሥጋት እንደሌለ በማስታወቅ የኢትዮጵያ መድን ድርጅት ዋስትናውን እንዲያነሳ ጠይቆ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡

ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ የንግድ ባንክ ሠራተኞች ለሪፖርተር በገለጹት መሠረት፣ ባንኩ ለሠራተኞች የቤት መግዣ የሰጣቸውን ብድር በገቡት ስምምነት መሠረት በወቅቱ መክፈል ቢሳናቸው፣ ይህንን ኪሳራ ለመሸፈን የሚያስችል መድን ገብቶላቸው በዚያ መሠረት ለኢትዮጵያ መድን ድርጅት ክፍያ ሲፈጽሙ ቆይተዋል፡፡

ይሁንና ባንኩ ‹‹ሞርጌጅ ፔይመንት ፕሮቴክሽን ኢንሹራንስ›› ወይም በአጭሩ ሞርጌጅ ኢንሹራንስ እየተባለ የሚጠራውን ይህንን ዋስትና ከመንፈቅ ወዲህ ማንሳቱን፣ ለዋስትናው መነሳት ምክንያቱም ለሠራተኞቹ የቤት ግዥ ክፍያ የተገባው ዋስትና ሥጋቱ ዝቅተኛ መሆኑን በማሰብ እንደሆነ ከሠራተኞቹ ለመረዳት ተችሏል፡፡ በዚህ መሠረት ባንኩ ዋስትና አያስፈልገውም ቢልም፣ ‹‹መድን ድርጅት ግን እምቢተኛነቱን በማሳየት ጥያቄያቸውን ለማስተናገድ ፈቃደኛነቱን እንዳላሳየ፤›› ገልጸዋል፡፡

ሠራተኞቹ እንደሚገልጹት፣ የሞርጌጅ ኢንሹራንሱ የብድር ጥያቄያቸው በባንኩ እንደተስተናገደ፣ ቀድሞውኑ ሙሉ በሙሉ ይከፈላል፡፡ በመሆኑም ንግድ ባንክ ዋስትና አያስፈልገውም በማለቱ እስካሁን የተከፈለው በታሳቢነት ተቀናሽ ተደርጎ ለወደፊቱ ጥቅም ላይ እንዲውል ይጠበቅ የነበረው ቀሪ ገንዘብ እንዲመለስላቸው ጥያቄ በማቅረብ ላይ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡ በሠራተኞቹ መረጃ መሠረት ከ3,000 በላይ ለሚሆኑ ሠራተኞች በዓመት የሚከፈለው የሞርጌጅ ዋስትና ቢያንስ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚደርስ ይገመታል፡፡

ስለ ጉዳዩ ማብራሪያ የሰጡት የኢትዮጵያ መድን ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ነፃነት ለማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ጥያቄ እየተነሳበት የሚገኘው የሞርጌጅ ኢንሹራንስ ዘርፍ፣ ተበዳሪው የተበደረውን ገንዘብ ሳይከፍል በሞት ቢለይ ለብድሩ ማካካሻ በቀረው የዕዳ መጠን ላይ መድን ድርጅት ካሳ ለመክፈል ተዋውሏል፡፡ የሞርጌጅ ኢንሹራንስ በሁለት አበይት ምክንያቶች ይቋረጣል ያሉት አቶ ነፃነት፣ አንደኛው ምክንያት ተበዳሪው ብድሩን አጠናቆ ሲከፍል በሁለተኛ ደረጃም ተበዳሪው ሲሞት የተገባው የመድን ውል እንደሚቋረጥ ገልጸዋል፡፡

እነዚህ ቅደመ ሁኔታዎች ከባንኩ ጋር በተደረጉ የውል ስምምነቶች በግልጽ መቀመጣቸውን በመግለጽ፣ ሠራተኞቹ በባንኩ ክፍያ የተፈጸመበትን የሞርጌጅ ኢንሹራንስ የመድን ገንዘብ ለምን ማስመለስ እንዳልቻለ እንዲጠይቁ መክረዋል፡፡ ባንኩና መድን ድርጅት በተዋዋሉት መሠረት ከላይ በአቶ ነፃነት ከተጠቀሱት ሁለት ቅድመ ሁኔታዎች አንዱ ቢሟላ መድን ድርጅት ለዋስትና የተከፈለውን ገንዘብ ለመመለስ ፈቃደኛ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

‹‹ገንዘቡ እንዲመለስላችሁ የምትፈልጉ ከሆነ እያንዳንዱ ተበዳሪ ዕዳውን ከፍሏል ብላችሁ ጻፉልን ብንላቸውም ይህንን ማድረግ ተጠያቂነት ያመጣብናል፤›› በማለታቸው ገንዘቡን ከዋስትና ስምምነቱ ውጪ ለመመለስ የሚችልበት ዕድል በባንኩ ሊፈጠርለት እንዳልቻለ አቶ ነፃነት አስረድተዋል፡፡ ባንኩ የሕዝብ ገንዘብ የሚያስተዳድር ተቋም በመሆኑ ጭምር ውሉን መሰረዝ እንደማይችል የጠቀሱት አቶ ነፃነት፣ መድን ድርጅት ብቻ ሁለት ቢሊዮን ብር በባንኩ የተቀመጠ ገንዘብ ያለው በመሆኑ በተዘዋዋሪ ይህንን ገንዘብ ስለሚያበድር ጥንቃቄ የተሞላበት አካሔድ መከተል እንደሚገባውም ያሳስባሉ፡፡

ንግድ ባንክ ለሠራተኞች በሰጠው የሞርጌጅ ብድር መሠረት አንድ ተበዳሪ ዕዳውን ሳይከፍል ቢሞት፣ አማራጩ ንብረቱ ሳይነካ ዕዳውን ይሰርዝለታል ማለት ነው፡፡ ይህ አሠራር የሕዝብን ገንዘብ አበድሮ መልሶ የሚቀበልበት ዕድል ሳይኖረው እንደመሠረዝ የሚቆጠር በመሆኑ፣ ከዚህ ይልቅ ግን የሞርጌጅ ኢንሹራንስ ክፍያው በዝቷል ከተባለም ሌሎች አማራጮች መከተል እንደሚቻል ጠቅሰዋል፡፡

ምንም እንኳ ከአሁን በኋላ የሞርጌጅ ኢንሹራንስ እንደማይገባ ባንኩ ቢያስታውቅም፣ እስካሁን የነበረውን መሰረዝ እንደማይችል፣ ይህም በሁለቱ መካከል በተገባው አስገዳጅ ውል መሠረት እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡ ሠራተኞቹ ለሞርጌጅ ኢንሹራንስ የተከፈለባቸው ገንዘብ እንዲመለስላቸው ያቀረቡትን ጥያቄ በሚመለከት አማራጮችን ለማየት የሚያስችሉ ውይይቶች ሲደረጉ መቆየታቸውና ወደፊትም ተጨማሪ ውይይቶች እንደሚካሔዱ አቶ ነፃነት ገልጸዋል፡፡

ንግድ ባንክ የመድን ድርጅትን ምልከታ ያላካተተ ጥናት በማድረግ በየዓመቱ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ የሞርጌጅ ወጭ እያወጣ እንደሚገኝ በመገንዘቡ ይህንን የመድን አገልግሎት ለማቋረጥ እንደተነሳ ይነገራል፡፡ በየዓመቱ በሞት የሚለየው ሰው የሚያስወጣው ወጪ ከአምስት እስከ አሥር ሚሊዮን ብር የሚገመት ገንዘብ እንደሆነም በጥናት መረዳቱን አቶ ነፃነት ይናገራሉ፡፡ ይሁንና ግን ለሞርጌጅ ኢንሹራንስ የሚከፈለው አረቦን ለአንድ ጊዜ ተከፍሎ ከ20 ዓመታት በላይ የሚቆይ እንደሆነ፣ መድን ድርጅትም በዚህ ጊዜ ውስጥ ለሚከሰቱ ሥጋቶች ዋስትና በመስጠት የሚሠራበት አካሔድ ወደፊት የሚኖሩ ተለዋዋጭ ሁኔታዎች ሲታከሉበት፣ በአሁኑ ወቅት የሚከፈለው የዋስትና ገንዘብ እንደሚገመተው የተጋነነ አይደለም ይላሉ፡፡ ባንኩ መድን ድርጅትን ቢያማክር ኖሮ ሌሎች የመድን አማራጮችንም መጠቀም ይቻል እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ይሁንና ግን ካለፈው የካቲት ወር ጀምሮ የሞርጌጅ ኢንሹራንስ ውሉን ማቋረጡን የሚገልጽ ደብዳቤ ለመድን ድርጅት መጻፉን አቶ ነፃነት አስታውሰዋል፡፡

የንግድ ባንክን አቋም በዚህ ዘገባ ለማካተት ሙከራ ቢደረግም ሊሳካ አልቻለም፡፡ የሞርጌጅ ኢንሹራንስ ውሉ እንዲቋረጥ ዋናው ምክንያት የሆነው የኮንስትራሽንና ቢዝነስ ባንክን ከመጠቅለሉ ጋር እንደሚገናኝ ይነገራል፡፡ የቀድሞው የኮንስትራክሽንና ቢዝነስ ባንክ ሠራተኞች እንዲህ ያለው የቤት ግዥ ብድር ክፍያ የተመለከተ ዋስትና ከንግድ ባንክ ጋር ከመቀላቀላቸው በፊት ገብተው ስለማያውቁ፣ ዋስትናውን እንደማይቀበሉት በማስታወቃቸው ባንኩ አሠራሩን ወጥ ለማድረግ በማሰብም ጭምር የመድን ሽፋኑን እንዳቋረጠ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ንግድ ባንክ የሞርጌጅ ኢንሹራንሱን ያነሳው አንድም ለሠራተኞቹ እንደ ጥቅማጠቅም እንዲታይለት ለማድረግ በማሰብ፣ በሌላ ጎኑ ደግሞ ከኮንስትራክሽንና ቢዝነስ ባንክ የተረከባቸው ከ3,000 በላይ ሠራተኞች ከዚህ ቀደም በነበሩበት ባንክ የዚህ ዓይነት የመድን ሽፋን እንዲገቡ የማይገደዱ በመሆናቸው፣ አንድ ወጥ አሠራር ለመዘርጋት በማሰብ ዋስትናው እንዲቀር እንዳደረገም ይነገራል፡፡

መድን ድርጅት ለባንኩ ካቀረባቸው አማራጮች መካከል ነባሩን የሞርጌጅ ኢንሹራንስ ሙሉ ለሙሉ ከሚቀር፣ ሠራተኞቹ ጥቂት በመሆናቸው በድርድር የሚከፈለው የአረቦን መጠን ቅናሽ እንዲደረግበት ቢጠይቅ ሊስተካከል የሚችልባቸው አማራጮች እንደነበሩ አቶ ነፃነት አስታውሰዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ለሠራተኞቹ ወደ ሕይወት መድን መቀየር የሚችልበት አሠራር እንዲፈጠር ማድረግ የሚቻልበት አማራጭ በመስጠቱ፣ ባንኩ በመድን ድርጅት የቀረቡለትን አማራጮች በመመልከት ለውይይት እየተዘጋጀ እንደሚገኝ አቶ ነፃነት ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

 

Standard (Image)
Viewing all 720 articles
Browse latest View live