Quantcast
Channel: አስተያየት
Viewing all 720 articles
Browse latest View live

መስፍን ኢንጂነሪንግ የሕንድ ትራክተሮችን መገጣጠም ጀመረ

$
0
0

ከተለያዩ የአውሮፓ ተሽከርካሪ አምራቾች ጋር ስምምነት በመፍጠር  አውቶሞብሎችንና የጭነት ተሽከርካሪዎችን መገጣጠም የጀመረው መስፍን ኢንዱስትሪያል ኢንጂነሪንግ፣ ሶናሊካ የተባለውን የሕንድ ትራክተሮች አምራች ምርቶችን በኢትዮጵያ መገጣጠም ጀመረ፡፡

መስፍን ኢንጂነሪግ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ ከዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ጋር ስምምነት በመፈጸም እየገጣጠማቸው ከሚገኙ የቤት አውቶሞብሎችና የጭነት ተሽከርካሪዎች ባሻገር የእርሻ መሣሪያዎችን ለመገጣጠም ከሕንዱ ኩባንያ ጋር በገባው ውል መሠረት፣ በኢትዮጵያ የተገጣጠሙትን የመጀመሪያዎቹን ትራክተሮች ቅዳሜ፣ ሐምሌ 15 ቀን 2009 ዓ.ም. ይፋ አድርጓል፡፡

ከመቀሌ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ውቅሮ ከተማ የተገነባው የትራክተር መገጣጠሚያ፣ በአሁኑ ወቅት ለገበያ ያቀረባቸው ትራክተሮች፣ ከ60 እስከ 110 የፈረስ ጉልበት ያላቸው ሕንድ ሠራሽ፣ የሶናሊካ ኩባንያ ብራንዶች ናቸው፡፡  ትራክተሮቹ ይፋ በተደረጉበት ፕሮግራም ወቅት እንደተመለከተው፣ የውቅሮው ፋብሪካ በወር 240 ትራክተሮችን የመገጣጠም አቅም አለው፡፡

ከመስፍን ኢንጅነሪንግ በተገኘው መረጃ መሠረት፣ ከትራክተሮቹ በተጨማሪ ሌሎች የእርሻ መሣሪያዎችንም ለመገጣጠም ዝግጅት መጠናቀቁን፣ ሌሎችም ለእርሻ ሥራ የሚውሉ መሣሪያዎች ማለትም መከስከሻ፣ ማረሻ፣ መዝጊያና የመሳሰሉት ማሽኖች ይገኙባቸዋል፡፡

ሶናሊካ ኩባንያ በሕንድ ከሚገኙ አምራቾች ሦስተኛው ግዙፍ ትራክተር አምራች ነው፡፡ ከ20 የፈረስ ጉልበት ጀምሮ በተለያየ ደረጃ እስከ 120 የፈረስ ጉልበት ያላቸው፣ በፍጥነታቸው፣ በማሳ ዝግጅትና በችግኝ ተከላ፣ በአጨዳና በሌሎችም የእርሻ ሥራዎች መስክ አገልግሎት የሚሰጡ ልዩ ልዩ የትራክተር ሞዴሎችን በማምረት ምርቶቹን በ80 አገሮች ውስጥ ማሰራጨት የቻለ ግዙፍ ኩባንያ ነው፡፡ እ.ኤ.አ. በ1969 የተመሠረተው ሶናሊካ ኩባንያ እስካሁን ከ300 ሺሕ በላይ ትራክተሮችን በማምረት ለዓለም ገበያ ማቅረቡም ይነገርለታል፡፡  

መስፍን ኢንጅነሪንግ ከዚህ ቀደም ከቻይናው ጂሊ የተሽከርካሪ አምራች ጋር ባደረገው ስምምነት መሠረት፣ የጂሊ ሞዴል የቤት አውቶሞቢሎችን በመገጣጠም ይታወቃል፡፡ ባለፈው ዓመትም ከታዋቂው የፈረንሣይ አውቶሞቢል አምራች ፔዦ ኩባንያ ጋር ባደረገው ስምምነት፣ የተለያዩ የቤት አውቶሞቢሎችን በመገጣጠም ለገበያ እያቀረበ ይገኛል፡፡ የጭነትና የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎችን በማምረት ከሚታወቀው የጀርመኑ ኤምኤኤን (MAN) ኩባንያ ጋር በደረሰው ስምምት መሠረትም፣ የኩባንያውን ምርቶች መገጣጠም ጀምሯል፡፡

በትግራይ መልሶ ማቋቋም የኢንዶውመንት ፈንድ (ትዕምት) ሥር ከሚተዳደሩ ኩባንያዎች መካከል አንዱ የሆነውና የመስፍን ኢንዱስትሪያል እህት ኩባንያ የሆነው ትራንስ ኢትዮጵያ በበኩሉ፣ የስካንያ የጭነት ተሽከርካሪዎችና አውቶብሶች የጅቡቲና የኢትዮጵያ ወኪል ሆኖ ለመሥራት ከስዊድኑ ኩባንያ ጋር ስምምነት መፈጸሙ ይታወቃል፡፡ 

Standard (Image)

የሰንሻይኑ ሰን ሲስተርስ ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ በማውጣት የኢንዱስትሪ ንፅሕና መስጫ ማዕከል መሠረተ

$
0
0

ሰን ሲስተርስ ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ በሰንሻይን ኢንቨስትመንት ግሩፕ ሥር ከሚተዳደሩ ኩባንያዎችና የማኅበራዊ አገልግሎት ከሚሰጠው ድርጅት መካከል አንዱ ነው፡፡ በልብስ ንጽሕና አገልግሎት፣ በውበት መጠበቂያ ምርቶች ሽያጭ እንዲሁም በሪል ስቴት ሥራዎች ውስጥ የሚንቀሳቀሰው  ሰን ሲስተርስ ትሬዲንግ፣ ዛሬ የሚገኝበት ደረጃ ላይ ከመድረሱ በፊት፣ ሰንሻይን የልብስ ንጽሕና መስጫና ሰንሻይን የውበት ሳሎን በሚሉ መጠሪያዎች የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶችን በመክፈት ወደ ሥራ የገባው ከሩብ ክፍለ ዘመን በፊት ነበር፡፡ በእነዚህ ቢዝነሶች ወደ ሥራ ሲገባ በወቅቱ ይዞት የተነሳው ካፒታል ሁለት ሚሊዮን ብር ነበር፡፡ አሁን በአዲስ አደረጃጀት ሰን ሲስተርስ ትሬዲንግ የሚል ስያሜ በመያዝ በሰንሻይን ኢንቨስትመንት ግሩፕ ሥር እንዲንቀሳቀስ ሲደረግ የካፒታል መጠኑን ወደ 105 ሚሊዮን ብር አሳድጎ አገልግሎቶቹን በማስፋፋት ላይ ይገኛል፡፡

በተለይ ሰን ሲስተርስ ኩባንያ ከሚያካሒዳቸው ቢዝነሶች አንዱ በሆነው የልብስ ንጽሕና አገልግሎት መስጫ ዘርፍን በተለየ ለማሳደግ በአሁኑ ወቅት አገልግሎት የሚሰጥባቸውን ቅርንጫፎች ቁጥር ወደ 18 ከፍ አድርጓል፡፡ በሰንሻይን ኢንቨስትመንት ግሩፕ ምክትል ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ፈትለወርቅ ኢላላ የሚመራው ሰን ሲስተርስ ትሬዲንግ፣ የልብስ ንጽሕና አገልግሎቱን የሚሰጠው ቅርንጫፍ በማስፋፋት ብቻ ሳይሆን አሠራሩንም ከተለመደው የልብስ ንጽሕና ወይም የእጥበት ሥርዓት ወደ  ኢንዱስትሪ ደረጃ ለማሳደግ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡

የአልባሳት እጥበትና ንፅሕናውን ሥራ በኢንዱስትሪ ደረጃ ለማሳደግ በነበረው ውጥን መሠረት አገልግሎቱን ሰንሻይን ኢንዲስትሪያል ላውንደሪ በሚል መጠሪያ አዲስ የኢንዱስትሪ አልባሳት ንፅሕና መስጫ በመገንባት ለአገልግሎት አብቅቷል፡፡

ሰንሻይን ኢንዱስትሪያል ላውንደሪን ወደ ሥራ ለማስገባት ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ጠይቋል፡፡ ይህ የኢንዱስትሪ ንፅሕና አገልግሎት መስጫ ማዕከል፣ ጃክሮስ ኢንዱስትሪ መንደር አካባቢ በ4000 ካሬ ሜትር ላይ የተገነባ ነው፡፡ እሑድ ሐምሌ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ማዕከሉ በይፋ ሥራ መጀመሩን ለማስታወቅ በተሰናዳው ፕሮግራም እንደተገለጸው፣ በኢንዱስትሪ ደረጃ የተቋቋመ ቀዳሚው ኢንዱስትሪያል የልብስ ንጽሕና መስጫ ማዕከል ነው፡፡ በሰን ሲስተርስ ትሬዲንግ የሰንሻይን ኢንዲስትሪያል ላውንደሪ የቴክኒክ ክፍል ኃላፊ አቶ ሲሳይ ተሾመ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አገልግሎቱን ከተለመዱት የልብስ ንጽሕና መስጫዎች ለየት የሚያደርገው በኢንዱስትሪ ደረጃ መቋቋሙና ለአገልግሎቱ ተብለው የተተከሉት ማሽኖች ብሎም የተያያዥ መሣሪያዎች አቅምና ይዘት ነው፡፡

በማዕከሉ በጠቅላላው ከ65 በላይ የተለያዩ ማሽኖች ተተክለዋል፡፡ ከማጠቢያ ማሽኖቹ ውስጥ በሰዓት 300 ኪሎ ግራም አልባሳትን የማጠብ አቅም ያላቸው አሥር የውኃ እጥበት ማሽኖች ይገኙባቸዋል፡፡ እንደ አቶ ሲሳይ ገለጻ፣ 300 ኪሎ ግራም የሚመዝኑ አልባሳት በሸሚዝ ቢመነዘሩ፣ ማሽኖቹ በሰዓት 1200 ሸሚዞችን የማጠብ አቅም ይኖራቸዋል እንደማለት ነው፡፡

ሙሉ ለሙሉ ለአልባሳት እጥበት የሚያገለግሉት ጣልያን ሠራሽ ሦስት የደረቅ እጥበት ማካሔጃ ማሽኖችም በሰዓት 240 ኮትና ሱሪ የማጠብ አቅም አላቸው፡፡ በአጠቃላይ በውኃና በደረቅ እጥበት የሚያገለግሉት ማሽኖች በድምሩ  420 ኪሎ ግራም ልብሶችን በሰዓት ማጠብ የሚችሉ ሲሆን፣ ይህም በስምንት ሰዓት ውስጥ ከ3360 ኪሎ ግራም በላይ የሚመዝኑ አልባሳትን የማጠብ አቅም ያለው ማዕከል እንደተገነባ ይመሰክራል፡፡ በዚህ ደረጃ የልብስ ንጽሕና ለመስጠት ታስቦ የተቋቋመ ትልቅ ማዕከል  እንደሌለ ያስታወሱት የምርት ክፍል ኃላፊው፣ በኢንዱስትሪ ደረጃ በሰፊው አገልግሎቱን በማቅረብ በፍጥነትና በጥራት ለማቅረብ የተቋቋመ ማዕከል እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡

በደረቅና በውኃ እጥበት አገልግሎት እንዲሰጡ ከተተከሉት ማሽኖች በተጨማሪ ለባለቀለም አልባሳት የሚያገለግሉ ማሽኖችም ሥራ ጀምረዋል፡፡ በሰዓት 400 ኪሎ ግራም አልባሳትን ማድረቅ የሚችሉ አሥር የማድረቂያ ማሽኖች የተተከሉበት ይህ ማዕከል፣ በኤሌክትሪክ ኃይልና በእንፋሎት ብቻ እየታገዙ የሚተኩሱ ዘመናዊ ማሽኖችም ተገጥመውለታል፡፡ በተለይ ጥቁር ቀለም ያላቸውን አልባሳት ሲተኮሱ እንዳይበላሹና ጉዳት እንዳይደርስባቸው የሚረዳ የእንፋሎት መተኮሻ ማሽኖችንም አካቷል፡፡

የአልባሳት እጥበትን በጥንቃቄና በጥራት ለማካሄድ የሸሚዝ፣ የኮትና ሌሎች አልባሳትን በተለየ ደረጃ የሚተኩሱ ማሽኖች የማዕከሉ መገለጫዎች ናቸው፡፡ የኮሌታ፣ የእጅጌ፣ የጀርባ ክፍሎችን የሚተኩስ የተለየ የማሽን ክፍልም የሥራው አካል ነው፡፡

የእጥበት አገልግሎቱን በኢንዱስትሪ ደረጃ ለማቅረብ ሲታሰብ፣ የሰንሻይን ኢንዱስትሪያል ላውንደሪ ያለማቋረጥ አገልግሎት እንዲሰጥ በማስቻልና የእጥበት ሥራውን ያለ ችግር ለማከናወን ወሳኝ የሆኑ እንደ ውኃና የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎትን ለማሟላት የሚያስችሉ ግብዓቶችን ከወዲሁ አሟልቷል፡፡ የጉድጓድ ውኃና 1050 ኪሎቮልት ኃይል የመሸከም አቅም ያላቸው ጄኔሬተሮች ተተክለውለታል፡፡

የጉድጓድ መስመሩ በሰከንድ ሁለት ሊትር ውኃ ለእጥበት ክፍሉ የማቅረብ አቅም ያለው ነው፡፡ ከመደበኛ መስመር የሚሰራጨው ውኃ ላይ የአቅርቦት እጥረት ቢያጋጥም፣ ኢንዱስትሪያል ላውንደሪ በቀጥታ ከጉድጓድ ውኃው የሚጠቀምበት መስመር ዘርግቷል፡፡ የኢንዱስትሪ ማጠቢያው ማሽኖች ሙሉ ለሙሉ ሲሠሩ በሰዓት 4800 ሊትር ውኃ የሚፈልጉ በመሆኑ፣ ለዚህ ታስቦ የተገነባ ነው፡፡ በመሆኑም 100 ሺሕ ሊትር የሚይዝ የውኃ ማከማቻ ታንከር ከምድር በታች በማዕከሉ ይዞታ ሥር ተገንብቷል፡፡

እንደ ኩባንያው ኃላፊዎች ገለጻ፣ የአልባሳት እጥበት ሥራውን በኢንዱስትሪ ደረጃ እንዲገነባ የተደረገው ለሰንሻይን የልብስ ንፅሕና መስጫ ቅርንጫፎች አገልግሎት ለመስጠት ተፈልጎ ብቻ አይደለም፡፡ በአሁኑ ወቅት እያደገ ያለውን የአገልግሎት ፍላጎት መሠረት በማድረግ፣ አግልግሎቱን የሚፈልጉ ተቋማትን በማሰብና በዚህ ዘርፍ ያለውን ገበያ ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው፡፡

ሆቴሎች ካላቸው አቅም አንፃር ደንበኞቻቸውን የሚገለገሉባቸው እንደ አንሶላ፣ ብርድ ልብስ፣ የፊትና የአፍ ማበሻዎች፣ የጠረጴዛ አልባሳት፣ የመጋረጃና የመሳሰሉትን ጨርቃ ጨርቆች በፍጥነት አጥቦና ተኩሶ ለማቅረብ፣ የዚህ ማዕከል ሥራ መጀመር ጠቀሜታውን ያጎላዋል ተብሏል፡፡ ከዚህ አንፃር በአሁኑ ጊዜ እንደ ማሪዎት ያሉ ሆቴሎች ከሠራተኞች የደንብ አልባሳት ጀምሮ እስከ መኝታ ክፍሎች የሚያገለግሉ የሙሉ አልባሳት እጥበት ሥራ በዚህ ማዕከል እንደሚከናወን ተገልጿል፡፡ እንደ አፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ያሉ ድርጅቶች የሠራተኞቻቸውን የደንብ አልባሳት በማሳጠብ ረገድ የማዕከሉ ተጠቃሚ መሆናቸውን የሚገለጹት አቶ ሲሳይ፣ ወደ ሌሎችም ተቋማት  በማስፋፋት በአሁን ወቅት  በስምንት ሰዓት የተወሰነውን አገልግሎት ወደ 24 ሰዓት  የማሳደግ ዕቅድ ተይዟል፡፡

አብዛኛውን ጊዜ ሆቴሎች በራሳቸው የእጥበት አገልግሎት ቢሰጡም፣ በፍጥነትና በጥራት ብዛት ያላቸውን አልባሳት ለማጠብ ዕድል እንደሚሰጣቸው ተጠቅሷል፡፡ የኢንዱስትሪ ንሕፅና መስጫው በተለይ ሆቴሎች ለሚፈልጉት የእጥበት ዓይነት የሚስማሙ በመሆናቸው፣ ለዚሁ እንዲረዱ ተብለው የተተከሉ ዘመናዊ መሣሪያዎችም ለሥራ ዝግጁ ሆነዋል፡፡

ለዚህ እንደ ምሳሌ የጠቀሱት ለአንሶላ መተኮሻ ብቻ የሚውሉ ማሽኖች መኖራቸው ነው፡፡ የአንሶላ መተኮሻ ካውያዎቹ 1.8 ሜትር እስከ ሦስት ሜትር ስፋት ያላቸውን አንሶላዎችን መተኮስ የሚችሉ ሲሆን፣ ማሽኖቹ አንዱን አንሶላ በ30 ሰከንድ ውስጥ ተኩሰው ያወጣሉ፡፡ የኢንዱስትሪ አልባሳት ንፅሕና መስጫ ማዕከሉ መከፈት፣ በየቅርንጫፎቹ ሲሰጥ የቆየውን የእጥበት አገልግሎት በአንድ ማዕከል ለማካሔድ ያስቻለው ሲሆን፣ ይህንን ቢዝነስ ለማሳደግም ተጨማሪ የማስፋፊያ ሥራዎች እንደሚሠራ አስታውቋል፡፡ በእጥበት ማዕከሉ በአሁኑ ወቅት ከ250 በላይ ሠራተኞች መቀጠራቸው ታውቋል፡፡   

Standard (Image)

የሳሳካዋ ግሎባል ከፍተኛ ኃላፊ ኢትዮጵያ የሜካናይዜሽን እርሻን ለመጀመር መጣደፍ እንደሌለባት መከሩ

$
0
0

 

-የአግሮ ፓርክ ፕሮጀክቶች በረጅም ጊዜ ውስጥ ውጤት እንደሚያመጡ ገልጸዋል

በ1977 የተከሰተው አስከፊው ረሃብ ወደ አፍሪካ በመምጣት ድጋፍ ለማድረግ መነሻ እንደሆናቸው የሚነገርላቸው ጃፓናዊው የበጎ አድራጎት ሰብዕና ባለቤት ሚስተር ዮሂ ሳሳካዋ የመሠረቱትን ሳሳካዋ ግሎባል 2000 አፍሪካ ወይም ሳሳካዋ አፍሪካ አሶሲዬሽን በመባል የሚጠራውንና በኢትዮጵያ ትልቅ ዕውቅና የሚሰጠውን ተቋም ከጥንስሱ ጀምሮ ላለፉት 31 ዓመታት በተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎች ሲመሩት ቆይተዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት የሳሳካዋ አፍሪካ አሶሲዬሽን የበጎ አድራጎት ድርጅት ከፍተኛ ሥራ አስፈጻሚ የሆኑትና ከአንድ ወር በኋላ ኃላፊነታቸውን የሚያስረክቡት ሚስተር ማሳዓኪ ሚያሞቶ፣ ከሪፖርተር ጋር ባለፈው ሐምሌ 19 ቀን 2009 ዓ.ም. ባደረጉት ቆይታ፣ በበርካታ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ትንታኔ ሰጥተዋል፡፡ ከእነዚህ ጉዳዮች መካከልም በኢትዮጵያ የሜካናይዜሽን እርሻን ለማስፋፋት የሚደረጉ ሙከራዎችን በተመለከተ የሰጡት ማብራሪያ ይጠቀሳል፡፡ በተለይም በአነስተኛ የእርሻ መሬት ይዞታ የሚተዳደሩ ገበሬዎችን በሜካናይዜሽን ስልት እንዲያመርቱ ለማድረግ የሚያስችሉ መሟላት የሚገባቸው በርካታ ጉዳዮች በመኖራቸው፣ ለሜካናይዜሽን እርሻ መቻኮል እንደማይገባ ይመክራሉ፡፡

ከስድስት ዓመታት በፊት፣ በአዲስ አበባ የአረጓዴው አብዮት አባት እየተባሉ የሚጠሩትንና በእርሻ ሥራ መስክ የዓለም የኖቤል አቻ የሆነውን ሽልማት ያሸነፉት ኖርማን ቦርሎግ (ዶ/ር) በተዘከሩበት ጉባዔ ወቅት፣ የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተር ተገኝተው ነበር፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ጨምሮ በርካታ የአፍሪካ ባለሥልጣናት በታደሙበት ጉባዔ ወቅት፣ ጂሚ ካርተር ለአፍሪካ መሪዎች የተናገሩት ማሳሰቢያ አይዘነጋም፡፡ በወቅቱ በርካታ የውጭ ኩባንያዎች በአፍሪካ እጅግ ሰፋፊ የእርሻ መሬቶችን በመግዛት ወይም በመከራየት ላይ የነበሩበት ወቅት ነበር፡፡ እንዲህ ያለው አካሔድ አነስተኛ ገበሬዎችን ይጎዳል በማለት ያጣጣሉት ጂሚ ካርተር፣ ለውጭ ኩባንያዎችና ባለሀብቶች የሚሰጡ ሰፋፊ መሬቶች ለአገሬው ቢሰጡ ይበልጥ ጠቃሜታ እንደሚኖራቸው መክረው ነበር፡፡ መንግሥታቱ የአፍሪካ አነስተኛ ገበሬዎችን በማስተባበር የሚያስፈልጓቸውን የእርሻ መሣሪያዎችና ግብዓቶች ቢያቀርቡላቸው ውጤቱ የተለየ እንደሚሆንና የአፍሪካ ሕዝቦችንም በምግብ ራሳቸውን እንዲችሉ ሊያግዝ እንደሚችል ገልጸው ነበር፡፡   

ስለዚሁ ጉዳይ ከሪፖርተር የተጠየቁት ሚያሞቶ፣ የፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተር ሐሳብ የአሜሪካን ተሞክሮ መነሻ ያደረ አሜሪካዊ አስተሳሰብ ነው ብለውታል፡፡ በአፍሪካ መሬት የሚተዳደርበት ሥሪት፣ የመሬት ባለቤትነትና ተጠቃሚነት ሥርዓት እንዲሁም አነስተኛ ገበሬዎች በየቦታው ተበታትነው የሚገኙ በመሆናቸው ሳቢያ ይህን ሁሉ አስተካክሎና አቀናጅቶ ሜካናይዝድ እርሻን ማስኬድ ከባድ እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡ እነዚህ መሠረታዊ ነጥቦች በአግባቡ ምላሽ ሳያገኙ ወደ ሜናይዜሽን ማቅናቱ፣ እንደ ትራክተር ኮምባይነርና የመሳሰሉት ሌሎችም የእርሻ መሣሪያዎች ያለ ጥቅም እንዲበላሹ ሊያደርጉ የሚችሉ አጋጣሚዎች ሊፈጠሩ ስለሚችሉ ሜካናይዜሽን ትልቅ ትኩረት እንደሚሻ አሳስበዋል፡፡ መንግሥት በአነስተኛ ገበሬዎች የሚለማ የሜካናይዜሽን እርሻ ለማስፋፋት ፖሊሲ ማዘጋጀቱ ይታወቃል፡፡

ከዚህም ባሻገር መንግሥት የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎችን በብዛት ለማቋቋም የሚረዱ የአግሮፕሮሰሲንግ ፓርኮችን መገንባት ጀምሯል፡፡ ይህም ቢሆን ችኮላ እንደማያስፈልገውም ሚያሞቶ ይመክራሉ፡፡ በተጨማሪም እነዚህ ፕሮጀክቶች ወደፊት የሚኖራቸው ጠቀሜታ ዘርፈ ብዙ በመሆኑ መንግሥት ፓርኮቹን መገንባቱ ተገቢ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በሳሳካዋ ከሚደገፉ አገሮች ሞዴል መሆኗን የጠቀሱት ሚስተር ሚያሞቶ፣ ከዚህ ቀደም በ15 የአፍሪካ አገሮች ውስጥ ሲያደርግ የነበረውን እንቅስቃሴ ቀስ በቀስ በመቀነስ በአራት አገሮች ተወስኗል፡፡ ኢትዮጵያን ጨምሮ በኡጋንዳ፣ በማሊ እንዲሁም በናይጄሪያ በሚያካሄደው እንቅስቃሴ አምስት ዋና ዋና ዘርፎችን በመለየት እንደሚንቀሳቀስ ሚያማቶ ጠቅሰዋል፡፡

የሰብል ምርት ምርታማነት ማሻሻያ፣ የድኅረ ምርት እንዲሁም የአግሮፕሮሰሲንግ ሥራዎች ማሻሻያ፣ የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት የገበያ ተደራሽነትን በማስፋፋት አነስተኛ ገበሬዎችን ተጠቃሚ ማድረግ፣ የሰው ሀብት ልማት እንዲሁም የፕሮጀክቶች ክትትል ምዘናና ሌሎችም ሥራዎች ለመጪዎቹ አምስት ዓመታት እየተተገበሩ የሚቀጥሉ አንኳር ሥራዎች ሆነዋል፡፡ ለሦስት አሥርታት ሳሳካዋ ግሎባል ከ250 ሚሊዮን ዶላር በላይ የፋይናንስ ድጋፍ ከሚያርግለት የጃፓኑ ኒፖን ፋውንዴሽን እያገኘ፣ በየአገሮቹ ለሚተገብራቸው ፕሮጀክቶች ማስፈጻሚያነት ሲጠቀምበት ቆይቷል፡፡

ዋናው ተልዕኮው ለአገሮች ፋይናንስ ፈሰስ ከማድረግ ይልቅ የምርምርና ሥርፀት ሥራዎች፣ የሥልጠናና የአቅም ግንባታ መስኮች ላይ በማተኮር የሚሰጠው ድጋፍ ትልቁን ድርሻ እንደሚይዝ ተቋሙ ይናገራል፡፡ በዚህም በርካታ የአነስተኛ ገበሬዎች ላይ ያተኮሩ፣ የእርሻ፣ የቅድመ ምርትና ድኅረ ምርት አስተዳደርና መሰል መስኮች ላይ ለግብርና ባለሙያዎች ሥልጠና በመስጠት፣ ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር አብሮ ለመሥራት የሚችልበትን ሥርዓት ዘግርቷል፡፡

ምንም እንኳ ተቋሙ በአፍሪካ ለ31 ዓመታት ቢቆይም ወደ ኢትዮጵያ የመጣው ግን ከደርግ መንግሥት መውደቅን ተከትሎ እንደሆነ ይነገራል፡፡ ይኸውም በአገሪቱ በተከሰተው የ1977ቱ ረሃብ ወቅት ድጋፍ ለማድረግ በማሰብ ቢመጣም ከደርግ ጋር ባለመጣጣሙ እንደወጣም ይገለጻል፡፡ 

ሚስተር ሳሳካዋ ከበጎ ተግባሮቻቸው ባሻገር ታዋቂ የንግድ ሰው ናቸው፡፡ ኒፖን ፋውንዴሽን ሊቀመንበር በመሆን በግብርና ዘርፍ ለአፍሪካ አገሮች ከሚያደርጓቸው ድጋፎች ባሻገር በሥጋ ደዌ በሽታ ለተጠቁ ወገኖች በመድረስም ስማቸው ጎልቶ ይጠቀሳል፡፡ የጃፓን የሥጋ ደዌ አምባሳደር እንዲሁም፣ በዓለም ጤና ድርጅት የሥጋ ደዌን የማጥፋት ዘመቻ የክብር አምባሳደር በመሆንም ያገለግላሉ፡፡ በልዩ ልዩ የሰብዓዊ ተግባሮቻቸው በ46 አገሮች፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅቶችና በሌሎችም ዓለም አቀፍ ተቋማት የክብር ሜዳይና ልዩ ልዩ ሽልማቶች ተበርክተውላቸዋል፡፡

 

Standard (Image)

በ1.4 ቢሊዮን ብር ወጪ እየተገነቡ የሚገኙ የአውቶቡስ ማቆሚያ ዴፖዎች ከወራት በኋላ እንደሚጠናቀቁ ተገለጸ

$
0
0

 

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ1.4 ቢሊዮን ብር ወጪ ግንባታቸው እየተካሔዱ የሚገኙ የከተማ አውቶቡሶችን የሚስተናገዱባቸው ሁለት ዴፖዎች በተያዘው በጀት ዓመት ማገባደጃ እንደሚጠናቀቁ ተገለጸ፡፡

የከተማ አውቶቡሶችን ደኅንነት ለመጠበቅና ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን ለማቅረብ እንዲቻል ተብለው እየተገነቡ የሚገኙት ዴፖዎች በቃሊቲ እንዲሁም በሸጎሌ አካባቢ የሚገኙ ናቸው፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥር የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት የእግረኛና የሕዝብ ትራንስፖርት ኃላፊ አቶ ይኼይስ ግርማሥላሴ ለሪፖርተር እንዳስታወቁት፣ እሳቸው የሚመሯቸው የቃሊቲና የሸጎሌ ከተማ አውቶቡስ ዴፖዎችን ጨምሮ አምስት ዴፖዎች በከተማ አስተዳደሩ ወጪ ተገንብተው ለአገልግሎት ይበቃሉ፡፡

የሸጎሌ የአውቶቡስ ዴፓ ግንባታ ሥራ 32 በመቶ መከናወኑን የቃሊቲውም 15 በመቶ ግንባታ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ አቶ ይኼይስ ጠቅሰዋል፡፡ ዴፖቹ ተገንብተው ሲጠናቀቁ በአንድ ጊዜ 500 አውቶቡሶችን የማስተናገድ አቅም ይኖራቸዋል፡፡ የሸጎሌ አውቶቡስ ዴፖ በ52 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ የሚሸፍን ግንባታ እየተካሔደበት እንደሚገኝ ሲገለጽ፣ በአንድ ጊዜ ከ250 እስከ 300 አውቶቡሶች የማስተናገድ አቅም እንደሚኖረውም ተጠቅሷል፡፡ የቃሊቲው ዴፖም በተመሳሳይ በአንድ ጊዜ ከ250 እስከ 300 የሚደርሱ አውቶቡሶችን ለማስተናገድ የሚችልበት አቅም ኖሮት እየተገነባ የሚገኝ ሲሆን፣ በ53 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ እንደሚያርፍ የአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት አስታውቋል፡፡

ከሁለቱ ዴፖዎች ባሻገር በመካኒሳና በገርጂ አካባቢ ተጨማሪ ዴፖዎችን ለመገንባት ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝና የገርጂ አውቶቡስ ዴፖ በዲዛይን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ አቶ ይኼይስ ገልጸዋል፡፡ በጠቅላላው በሁለት ዓመት ውስጥ አምስት ዴፖዎች ተገንብተው ወደ ሥራ እንደሚገቡ ይጠበቃል ተብሏል፡፡

ከዴፖ ግንባታ ባሻገር የተሳፋሪዎችን እንግልት ለመቀነስ ያስቻላሉ የተባሉ የተቀናጁ የትራንስፖርት አገልግሎት መስጫ ማዕከላት ግንባታዎችም ይካሄዳሉ ተብሏል፡፡ በመርካቶ አካባቢ የዚህ ማዕከል ግንባታ መጀመሩን ጽሕፈት ቤቱ አስታውቋል፡፡ በመገናኛም የትራንስፖርት መሳፈሪያ ማዕከል ግንባታ ለማካሄድ የዲዛይን ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

ዴፖዎቹ በመገንባታቸው ምክንያት አውቶቡሶች ነዳጅ በመቅዳት፣ በመኪና እጥበት እንዲሁም በጥገና ምክንያት ሲያባክኑ የነበረውን ጊዜ በማስተካከል ቀልጣፋ የስምሪት ሥርዓት እንዲፈጠር እንደሚያግዙ ተጠቅሷል፡፡

ዴፖዎቹ ከመንግሥት ባሻገር በግል የብዙኃን ትራንስፖርት አገልግሎት ለሚሰጡ ድርጅቶችም አገልግሎት የሚሰጡበት አሠራር እንደሚመቻች ተነግሯል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከሚያከናውናቸው የትራንስፖርት አገልግሎት መሠረተ ልማት አውታሮች ግንባታ ጎን ለጎን፣ የከተማዋን ትራንስፖርት ዘርፍ ዘመናዊና የተቀላጠፈ ለማድረግ፣ እንደ ፈጣን የአውቶቡስ ትራንስፖርት ያሉትን ሥራ ለማስጀመር የፈረንሳይ መንግሥት የፋይናንስ ድጋፍ ማድረጉ ይታወቃል፡፡ ከዚህም ባሻገር የዓለም ባንክ የአዲስ አበባን የትራንስፖርት አግልግሎት አሰጣጥ፣ ትራፊክ ፍሰትና ስምሪት የሚያሻሽል ፕሮጀክት እንዲተገበር የ300 ሚሊዮን ዶላር ብድር መስጠቱም አይዘነጋም፡፡ ይህም ሆኖ በአዲስ አበባ ከዕለት ወደ ዕለት እየተባባሰ የመጣው የትራፊክ መጨናነቅ ለበርካቶች ችግር እየሆነ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ባለሥልጣንም ሆነ የፌደራል ትራንስፖርት ባለሥልጣን ለትራፊክ መጨናነቁ መንስዔ ከሚያደርጓቸው መካከል ከመንገድ ዳር የሚዘወተሩ የመኪና ማቆም ተግባራት ይጠቀሳሉ፡፡ ይህንንም ለመቀነስ ዘመናዊ የመኪና ማቆሚያ ተርሚናሎች ወይም ስማርት ፓርኪንግ የሚባሉ ቴክኖሎጂዎች ግንባታ መካሄድ ተጀምሯል፡፡ በዚሁ መሠረት በመገናኛ አካባቢ የተገነባው የመኪና ማቆሚያ አገልግሎት መስጠት ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡  

Standard (Image)

የግማሽ ቢሊዮን ብር የማስፋፊያ ግንባታ ያቀደው ናሽናል ሲሚንቶ ለድሬዳዋ ሕዝብ አክሲዮን እንደሚሸጥ አስታወቀ

$
0
0

ናሽናል ሲሚንቶ አክሲዮን ማኅበር፣ የድሬዳዋ ከተማ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግና የፋብሪካውን የባለቤት ድርሻ ለመጋራት የሚያስችለው የአክሲዮን ሽያጭ እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡ አዲስ የማስፋፊያ ግንባታ እንደሚጀምር ገለጸ፡፡

ናሽናል ሲሚንቶን ጨምሮ ሌሎች ኩባንያዎችን የሚያስተዳድረው የኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ ኩባንያ መሥራችና ሊቀመንበር አቶ ብዙአየሁ ታደለ በኩባንያው ዓመታዊ በዓል ላይ እንዳስታወቁት፣ የናሽናል ሲሚንቶ አክሲዮን ባለቤትነት ድርሻን መሠረት ለማስፋት በማሰብ ለአካባቢው ማኅበረሰብ ለመሸጥ ያቀደውን አክሲዮን በቅርቡ ተግባራዊ ያደርጋል፡፡

ኩባንያቸው የድሬዳዋና የአካባቢዋ ነዋሪዎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማቀድ በቅርቡ የሚያካሂደው የአክሲዮን ሽያጭ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች እንዲሁም ለባለሀብቶችም እንደሚሸጥ ሐሙስ፣ ሐምሌ 20 ቀን 2009 ዓ.ም. በድሬዳዋ በተካሄደው ሥነ ሥርዓት ወቅት አቶ ብዙአየሁ አስታውቀዋል፡፡ ሆኖም ኩባንያው ምን ያህል አክሲዮኖችን ለድሬዳዋና ለአካባቢዋ ማኅበረሰብ እንደሚሸጥ ይፋ ያላደረገ ሲሆን፣ ኩባንያው ከነበረበት ችግር ወጥቶ ወደ አትራፊነት መሸጋገሩን ይፋ ባደረገበት ማግሥት የናሽናል ሲሚንቶን የባለቤትነት መሠረት ለማስፋት ተብሎ የተወሰነው የአክሲዮን ሽያጭ፣ የፋብሪካው ሠራተኞችንም እንደሚያሳትፍ ከአቶ ብዙአየሁ ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ወደ አትራፊነቱ የመጣው ናሽናል ሲሚንቶ፣ ለአካባቢው ማኅበረሰብ አክሲዮን ለመሸጥ ማቀዱ የፋብሪካው የባለቤትነት ስሜት በሕዝቡ ዘንድ እንዲንሠራፋ ከማድረጉም በላይ፣ ሕዝቡ የትርፉ ተቋዳሽ እንዲሆን ታስቦበት የተደረገ እንደሆነም በክብረ በዓሉ ወቅት ተገልጿል፡፡

ፋብሪካው በ2009 ዓ.ም. ወደ 200 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ትርፍ እንዳገኘ የሚገልጹት የኩባንያው ኃላፊዎች፣ በ2010 ዓ.ም. ደግሞ 450 ሚሊዮን ብር ትርፍ ለማግኘት እንዳቀደም አስታውቀዋል፡፡ ከዚህ የአክሲዮን ሽያጭ ጎን ለጎን የፋብሪካውን የማምረት አቅም ለማሳደግ የማስፋፊያ ግንባታ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ እንደሚጀምር ታውቋል፡፡ የማስፋፊያ ሥራውን በተመለከተ የኩንያው መረጃ እንደሚያመላክተውም፣ የማስፋፊያ ግንባታው ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ይጠይቃል ተብሎ ይገመታል፡፡

የፋብሪካውን የማምረት አቅም ዕውን ለማድረግ የረዥም ጊዜ ራዕያችን ነበር ያሉት አቶ ብዙአየሁም፣ የፋብሪካውን የማምረት አቅም ለማሳደግ በተደረገው ጥናት በቀን 3,500 ቶን የማምረት አቅም ወደ 5,000 ቶን ለማሸጋገር ያስችላል ብለዋል፡፡ በዚህ ወር ተጀምሮ በአጭር ጊዜ ይጠናቀቃል ተብሎ የሚጠበቀው የማስፋፊያ ግንባታ ሲጠናቀቅ፣ በአገሪቱ ከሚገኙ ትልልቅ የሰሚንቶ ፋብሪካ አንዱ ሊያደርገው እንደሚችል ተጠቅሷል፡፡ የፋብሪካው ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ዘመንፈስ ገብረ ሚካኤል በበኩላቸው የማስፋፊያ ግንባታው አዳዲስ የሲሚንቶ ምርቶችን ለማውጣት የሚያስችል ዕድል ይፈጥርለታል፡፡

በ2009 ዓ.ም. 826,500 ቶን ክሊንከር ለማምረት አቅዶ 835,855 ቶን ክሊንከር እንዳመረተ የሚገልጸው የኩባንያው መረጃ፣ በዛው ዓመት 923,339 ቶን ሲሚንቶ መሸጡንም ያስረዳል፡፡

በተለይ በአገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል በመካሄድ ላይ የሚገኘውን የኢንዱስትሪና የመሠረተ ልማት አውታሮች ግንባታ ከመደገፍ በተጨማሪ ምርቱን ወደ ጎረቤት አገሮች በስፋት ለመላክ ያስችላል ተብሏል፡፡

ፋብሪካው በእስካሁኑ ጉዞው በየዓመቱ ምርቱን ለውጭ ገበያ ሲያቀርብ እንደቆየ የተገለጸ ሲሆን፣ በ2008 ዓ.ም. አምስት ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ያስገኘ ምርቱን ለሶማሊያና ለጂቡቲ አቅርቧል፡፡ በ2009 ዓ.ም. ደግሞ ወደ ሁለቱም አገሮች ከተላከው ሲሚንቶ 8.8 ሚሊዮን ዶላር መገኘቱን አቶ ዘመንፈስ ገብረ እግዚአብሔር ገልጸዋል፡፡

በክብረ በዓሉ ላይ የተገኙት የድሬዳዋ ከንቲባ አቶ ኢብራሂም ኡስማን ፋራህ እንደገለጹት፣ ፋብሪካው ለድሬዳዋ ከተማ አበርክቷል ያሉትን ዕገዛና ድጋፍ አትተው አሁንም ያቀዷቸውን ዕቅዶች ለማሳካት አስተዳደሩ እንደሚደግፋቸው አረጋግጠዋል፡፡

የፋብሪካው ዋና ሥራ አስፈጻሚ የምርት ግብዓቶች በሚገኙበት አካባቢ እየተካሄደ ያለው ሕገወጥ የቤቶች ግንባታ እንዲቆምላቸው ላቀረቡት ጥያቄ፣ የከተማው አስተዳደር መፍትሔ እንደሚሰጠው ከንቲባው ቃል ገብተዋል፡፡

ቀድሞ ድሬዳዋ ሲሚንቶ ፋብሪካ እየተባለ ይጠራ የነበረውን ፋብሪካ ከመንግሥት የልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ በመግዛት የጠቀለለው በ1997 ዓ.ም. ነበር፡፡ ፋብሪካውን ለማስፋትና ለማጠናከር እስካሁን ከሦስት ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉ ተጠቅሷል፡፡ ጠቅላላ ሀብቱም 4.3 ቢሊዮን ብር እንደደረሰ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከ1,300 በላይ ሠራተኞችን የሚያስተዳድረው ናሽናል ሲሚንቶ ፋብሪካ፣ የካይዘን ሥርዓትን በመተግበር ዓመታዊ የምርት መጠኑን በማሳደግ ላይ እንደሚገኝም አስታውቋል፡፡

ኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ በሥሩ የሚያስተዳድራቸው ኩባንያዎች ከ6,330 በላይ ሠራተኞችን የያዙ ሲሆን፣ በዓመት 370 ሚሊዮን ብር ለሠራተኞች ደመወዝ ወጪ የሚያደርጉ ኩባንያዎችን ያሰባሰበ የንግድ ተቋም እንደሆነም ኃላፊዎቹ ይናገራሉ፡፡ የናሽናል ሲሚንቶ ፋብሪካ ባለቤት አቶ ብዙአየሁ በቅርቡ በፎርብስ መጽሔት ሚሊየነሮች ተርታ ስማቸው ከሠፈሩ አምስት ኢትዮጵያውያን መካከል አንዱ ናቸው፡፡ 

Standard (Image)

ሊተነበይ ያልቻለው የአዲስ አበባ ሪል ስቴቶች ዕጣ ፈንታ

$
0
0

 

በ1995 ዓ.ም. አርከበ ዕቁባይ (ዶ/ር) የአዲስ አበባከተማን ቁልፍ ከአቶ አሊ አብዶ ሲረከቡ በከተማው የነበሩ ቤቶች ቁጥር 387,000 ብቻ ነበር፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ1996 ዓ.ም. ባደረገው የጂአይኤስ ዳሰሳ ጥናት፣ በከተማው ውስጥ ከነበሩ ቤቶች መካከል 238,000 (61.5 በመቶ) መኖሪያ ቤቶች ሲሆኑ፣ የተቀሩት የተለያዩ አገልግሎቶች ይሰጡ ነበር፡፡

በዚህ ወቅት በአዲስ አበባ ከተማ የ500 ሺሕ ቤቶች እጥረት እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ይህንን የከፋና ሲከማች የቆየውን የመኖሪያ ቤት እጥረት ከመሠረቱ ለመፍታት የቀድሞው የአዲስ አበባ ከተማ ጊዜያዊ አስተዳደር ከንቲባ አርከበ ሁለት ጉዳዮች ላይ ትኩረት አደረጉ፡፡

የመጀመሪያው ዝቅተኛና መካከለኛ ገቢ ላለው የኅብረተሰብ ክፍል በየዓመቱ 50 ሺሕ ኮንዶሚኒየም ቤቶች በ1.5 ቢሊዮን ብር ወጪ መገንባት፣ ሁለተኛው ደግሞ ከፍተኛና መካከለኛ ገቢ ላለው የኅብረተሰብ ክፍል የሚሆኑ የሪል ስቴት ቤቶችን በግሉ ዘርፍ እንዲገነባ ዕድሉን ማመቻቸት ነው፡፡

በዚህ መሠረት በተለይ በ1996 ዓ.ም. በተካሄደው የጂአይኤስ ዳሰሳ ጥናት በከተማው ከሚገኙ ቤቶች 80 በመቶ ያህሉ ያረጁ፣ ለመኖሪያ ምቹ ያልሆኑና አሮጌ መንደሮችን በማፍረስ በመሀል ከተማ አዲስ ግንባታ ማካሄድ ነው፡፡ ለዚህም መንግሥት ነባር ነዋሪዎችን አንስቶ ጊዜያዊ መጠለያ ውስጥ በማቆየት፣ ቤቶቹን ከገነባ በኋላ መልሶ ለማስፈር ዕቅድ አውጥቶ ነበር፡፡

በዚህም የማይናቅ መንገድ ከተሄደ በኋላ በታሪካዊው ምርጫ የ1997 ዓ.ም. ከተማውን ለማስተዳደር ምርጫውን ያሸነፈው ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ በተለያዩ ምክንያቶች ሥልጣኑን መረከብ አልቻለም፡፡ መረከብ ባለመቻሉም በአቶ ብርሃነ ደሬሳ የሚመራው የአዲስ አበባ ከተማ ባለአደራ አስተዳደር ሥልጣኑን ተረክቧል፡፡

የአቶ ብርሃነ ካቢኔ ባለአደራ አስተዳደር እንደመሆኑ የተጀመረው የመኖሪያ ቤት ልማት በተጀመረበት መንገድ ማስቀጠል ሳይቻል ቀርቷል፡፡ ራሱንም ‹‹ፋየር ብርጌድ›› በማለት ሲጠራ ቆይቷል፡፡

በወቅቱ የተጀመረውን የኮንዶሚኒየም ቤቶች ለማግኘት ከ453 ሺሕ በላይ ነዋሪዎች የተመዘገቡ ቢሆንም፣ ከ13 ዓመታት በኋላም ከእነዚህ ነዋሪዎች መካከል አብዛኛዎቹ ቤታቸውን ማግኘት አልቻሉም፡፡ አሁንም ቢሆን የተወሰኑ ነዋሪዎች በመጠለያ ውስጥ እንደሚገኙ ልብ ይሏል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ድሪባ ኩማ የበጀት ዓመቱን ሪፖርት ለምክር ቤት ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት፣ የከተማው የቤት ልማት ሥራ በእስካሁኑ ጉዞ 175 ሺሕ የሚሆኑ ቤቶችን ለተጠቃሚ አስተላልፏል፡፡ 40/60 ፕሮግራምን ጨምሮ 132 ሺሕ ቤቶች ደግሞ ግንባታቸው እየተካሄደ ነው፡፡

ከ13 ዓመታት በኋላ የቀድሞ ተመዝጋቢዎች ጭምር መኖሪያ ቤታቸውን ማግኘት ካለመቻላቸው በላይ፣ በሐምሌ 2005 ዓ.ም. በተካሄደው የመኖሪያ ቤት ፈላጊዎች ዳግም ምዝገባ የከተማው የመኖሪያ ቤት ፍላጎት (እጥረት) አንድ ሚሊዮን ደርሷል፡፡

የግንባታ ፍጥነቱ ከአንገብጋቢው የመኖሪያ ቤት ፍላጎት አንፃር ሲታይ ከፍተኛ አለመጣጣም ይስተዋልበታል፡፡ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን መንግሥት 750 ሺሕ ቤት የመገንባት ዕቅድ ይዟል፡፡ በዓመት ሲታይ 150 ሺሕ ቤት መገንባት የሚያስፈልግ ሲሆን፣ ይህንን ግንባታም ለማካሄድ ከ30 ቢሊዮን ብር በላይ ያስፈልጋል፡፡ በተጠናቀቀው የ2009 በጀት ዓመት ግን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ማቅረብ የቻለው 15 ቢሊዮን ብር ብቻ ነው፡፡

በፋይናንስ በኩል ካለው የአቅርቦት ችግር በተጨማሪ ግንባታውን በተያዘው ዕቅድ ማካሄድም ሆነ የፕሮጀክት አስተዳደር ችግር በመኖሩ የመኖሪያ ቤት አቅርቦቱ አሁንም ችግር ውስጥ ይገኛል፡፡

የቀድሞ የአዲስ አበባ ከንቲባ አርከበ የመኖሪያ ቤት እጥረቱን ለመፍታት ትኩረት ያደረጉበት ሌላኛው ዕቅድ የሪል ስቴት ፕሮግራም ነው፡፡ ከንቲባ አርከበ በዚህ ግዙፍ ዕቅዳቸው በዘርፉ ለመሰማራት አቅም ላላቸው ለ105 ሪል ስቴት ኩባንያዎች በአማካይ 50 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ ሰጥተዋል፡፡ በድምሩ በሚሊዮን ካሬ ሜትር የሚቆጠር መሬት ለሪል ስቴት ልማት በጀት ተደርጓል፡፡

ለሪል ስቴት ኩባንያዎች ሰፋፊ መሬት ከማቅረብ ባሻገር በተለይ መካከለኛ ገቢ ያላቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ፣ ከፍተኛ ገቢ ያላቸው የኅብረተሰብ ክፍሎችም እንደየፍላጎታቸው እንዲስተናገዱ 70 በመቶ አፓርታማና 30 በመቶ ደግሞ ቪላዎች እንዲገነቡ ዕቅድ ወጥቶ ነበር፡፡

ይህንን ተግባራዊ ለሚያደርጉ የሪል ስቴት ባለሀብቶች ለተሰጣቸው መሬት ዝቅተኛ የሊዝ ክፍያ እንዲፈጽሙና በሚገነቡት ቤት መጠን ለአንድ ቤት 50 ካሬ ሜትር ቦታ በማበረታቻ መልክ እንዲሰጣቸው ጭምር ተደርጓል፡፡

ነገር ግን የሪል ስቴት ልማት ዘርፉ ከመጀመርያው ጀምሮ በበርካታ ማነቆዎች መተብተብ በመጀመሩ በታሰበው መንገድ መጓዝ ሳይችል ቀርቷል፡፡

በወቅቱ ብዙዎቹ የሪል ስቴት አልሚዎች የተሰጣቸው መሬት በከተማው ዳርቻ ላይ በመሆኑ መንግሥት በተፈለገው መጠን እንደ መንገድ፣ ኤሌክትሪክና ውኃ ያሉትን የመሠረተ ልማቶች ማሟላት አልቻለም፡፡

ከዚህ በተጨማሪም የሪል ስቴት ኩባንያዎች ግንባታ የሚያከናውኑት ከደንበኞቻቸው በተወሰነ ደረጃ ቅድሚያ ክፍያ በማሰባሰብ በመሆኑ፣ በተለይ አፓርትመንቶች ለመገንባት በቂ አቅም አልነበራቸውም፡፡ ባንኮች ለሪል ስቴት ግንባታ የሚሆን የረዥም ጊዜ ብድር የማያቀርቡ በመሆኑ፣ ግንባታቸውን በወቅቱ አካሂደው ለማስረከብ ችግር ተፈጥሯል፡፡

በሪል ስቴት አልሚዎች በኩልም መረር ያለ ችግር ታይቷል፡፡ በተለይ በትንሽ የሊዝ ገንዘብ የወሰዱትን መሬት ምንም ዓይነት ግንባታ ሳያካሂዱ ለሦስተኛ ወገን የሊዝ መብትን አሳልፎ መሸጥ፣ አፓርታማ ለመገንባት የወሰዱትን ቦታ ቪላ ገንብቶ መሸጥ፣ ለማኅበራዊ አገልግሎት መዋል ያለበትን መሬት ለቤት ግንባታ ማዋል፣ ከተሰጣቸው ማበረታቻ አንፃር በተመጣጣኝ ዋጋ መኖሪያ ቤቱን መሸጥ ሲገባቸው ዋጋ ማናር፣ ከደንበኞች ገንዘብ ከሰበሰቡ በኋላ ቤቱን በወቅቱ አለማቅረብና ጭራሽኑ ገንዘቡን ይዞ መጥፋት የተወሰኑት ችግሮች ናቸው፡፡ በነዚህ ውስብስብ ችግሮች ተፈትነው የወጡ ሪል ስቴቶች ቢዘገዩም ለደንበኞቻቸው መኖሪያ ቤት ያስረከቡም መኖራቸው የሚዘነጋ ሀቅ አይደለም፡፡

ባለፉት አሥር ዓመታት በብዙ ውጣ ውረዶች ውስጥ በማለፍ ግንባታቸውን አጠናቀው፣ ለደንበኞች ካስረከቡና እነሱም በቂ ልምድ የያዙ ሪል ስቴቶች፣ በቀጣይ በሰፊው ግንባታ ውስጥ ለመግባት የመሬት አቅርቦት አለመኖር አሳስቧቸዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አሥረኛው ማስተር ፕላን በመሀል ከተማ የሚካሄዱ የሕንፃ ግንባታዎች እስከ 60 በመቶ ድረስ መኖሪያ ቤቶች ማካተት እንዳለባቸው አስገዳጅ በማድረጉ፣ አዳዲስ የሪል ስቴት ኩባንያዎች መፈጠራቸውና በየጊዜው እየጨመረ በመሄድ ላይ የሚገኘው የዋጋ ግሽበት፣ ገንዘብን ሁነኛ ቦታ ለማስቀመጥ የሪል ስቴት ቤቶች አማራጭ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡

ጊፍት ሪል ስቴት በ1998 ዓ.ም. ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሦስት ሳይቶች 16 ሔክታር መሬት ለሪል ስቴት ልማት ተረክቧል፡፡

ጊፍት ሪል ስቴት 1,500 ደንበኞችን ማፍራት የቻለና በሦስቱም ሳይቶች አፓርትመንቶች፣ ታውን ሐውሶችንና ቪላ ቤቶችገንብቶ ለደንበኞቹ አስረከቧል፡፡ በአሁኑ ወቅትም የተለያዩ ቤቶችን በመገንባትም ላይ ይገኛል፡፡

የጊፍት ግሩፕ ኩባንያዎች መሥራችና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ገብረ ኢየሱስ ኢጋታ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ድርጅታቸው በብዙ ውጣ ውረዶች ውስጥ አልፎ በርካታ ልምድ አካብቶ የሪል ስቴት ግንባታውን አገባዷል፡፡

‹‹በአሁኑ ወቅት ለሪል ስቴት ልማት መሬት በድርድር እየቀረበ አይደለም፡፡ በመሆኑም ይህንን ሁሉ ሥራ ከሠራን በኋላ ዘርፉን ለቆ የመውጣት ጉዳይ ያሳስበኛል፤›› በማለት አቶ ገብረ ኢየሱስ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ኅዳር 2009 ዓ.ም. የወጣው የከተማ ቦታ በሊዝ ስለመያዝ የወጣው አዋጅ ቁጥር 721 ለአገልግሎት መስጫ ተቋማት ለአብነት ለሪል ስቴት፣ ለባለኮከብ ሆቴል፣ ለትምህርት ቤትና ለጤና አገልግሎት የሚውሉ ግንባታዎች ለማካሄድ መሬት የሚቀርበው በጨረታ እንደሆነ ይደነግጋል፡፡

‹‹የሪል ስቴት ልማትን በጨረታ በሚገኝ መሬትም ሆነ ከባለይዞታዎች ላይ እየገዙ ግንባታ ማካሄድ አዋጪ አይደለም፣ በዚህ ዓይነት ግንባታ የመኖሪያ ቤት ችግሮችን መቅረፍ አይቻልም፤›› የሰንሻይን ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሳሙኤል ታፈሰ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ ለዓለም  ተሰራ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከሪል ስቴት ልማት መሬት አቅርቦት ጋር ተያይዘው ያሉ ችግሮች የተፈጠሩት በሊዝ አዋጅ ነው፡፡ ‹‹በአሁኑ ወቅት የሊዝ አዋጅ እየተሻሻለ በመሆኑ በሚቀጥለው ዓመት ተሻሽሎ ይወጣልተብሎ ይጠበቃል፡፡ የሊዝ አዋጅ ሲወጣ ችግሮቹ ይፈታሉ፤›› በማለት አቶ ለዓለም አብራርተዋል፡፡

ከዚህም የሊዝ አዋጅ ባሻገር በሪል ስቴት ዘርፍ ያሉ የግብይትና የአሠራር ችግሮችን ለመፍታት የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር የሕግ ረቂቅ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ ነገር ግን ረቂቅ ሕጉ ከተዘጋጀ አራት ዓመታት ቢሆኑትም፣ የሪል ስቴት ኩባንያዎች ረዥም ጊዜ የወሰደ ውይይት ቢያደርጉትም እስካሁን ሕግ ሆኖ አልወጣም፡፡

በአሁኑ ወቅት በሪል ስቴት ልማት ዘርፍ በርካታ ሥራዎችን እያካሄዱ ከሚገኙ ኩባንያዎች መካከል ፍሊንት ስቶን ሆምስ አንዱ ነው፡፡ የፍሊንት ስቶን ሆምስ ኩባንያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ፀደቀ ይሁኔ፣ በሪል ስቴትና በአጠቃላይ በመሬትና ተያያዥ ዘርፎች የተዘጋጁ የሕግ ማዕቀፎችበአፋጣኝ ፀድቀው ሥራ ላይ መዋል አለባቸው ብለዋል፡፡

‹‹ነገር ግን ሕጉ ከተዘጋጀ አራት ዓመት በማስቆጠሩና አዳዲስ ክስተቶች በመኖራቸው፣ በድጋሚ ሊታይ ይገባል፤›› በማለት አቶ ፀደቀ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ባወጣው መረጃ፣ በአጠቃላይ 117 ኩባንያዎች በሪል ስቴት ዘርፉ ለመሥራት ፈቃድ ወስደዋል፡፡ እነዚህ ኩባንያዎች 56 ፕሮጀክቶችንም አስመዝግበዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ 43 የሚሆኑት በአዲስ አበባ የሚካሄዱ ናቸው፡፡

የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር በ2009 ዓ.ም. ግማሽ ዓመት ባወጣው ሪፖርት፣ 35 ሪል ስቴቶች ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ባለሥልጣን የግንባታ ፈቃድ ወስደው በግንባታ ላይ ይገኛሉ፡፡

የሪል ስቴት መኖሪያ ቤቶች ግብይት በሒደት በመጠኑ እየተሻሻለ የመጣ ቢሆንም፣ የሪል ስቴት ኩባንያዎች ግን ዘርፉን እየተቀላቀሉ የሚገኙት አሥረኛው ማስተር ፕላን በከተማው መሀል የሚካሄዱ ሕንፃዎች እስከ 60 በመቶ የሚሆነው ግንባታ ለመኖሪያ ቤቶች አፓርታማ እንዲያውሉ አስገዳጅ በመሆኑ ሊሆን እንደሚችል ይጠረጠራል፡፡

ሆኖም ግን የግንባታው ወጪ እየናረና ግንባታ ለማካሄድ የሚያስፈልጉ ሕጋዊ ሒደቶች ረዥም ውጣ ውረዶች በሚጠይቁበት፣ ባንኮች የረዥም ጊዜ ብድር በማያቀርቡበት በዚህ ወቅት፣ ቤቶችን በውድ ዋጋ የሚገዙ ደንበኞች እየተበራከቱ መምጣታቸው አነጋጋሪም ሆኗል፡፡

ለዚህ ጉዳይ እየቀረበ የሚገኘው ምክንያት ምናልባት የብር የመግዛት አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተዳከመ መሄዱና ገንዘብ በባንክ ማስቀመጥ የተሻለ አማራጭ ባለመሆኑ ነው፡፡ በተጨማሪም ሕጋዊ ያልሆነ ገንዘብን ሕጋዊ አድርጎ ለማቅረብ አማራጭ ሊሆን በመቻሉ ምክንያት ወይም የመንግሥት የመኖሪያ ቤት ፕሮግራሞች አፈጻጸም ደካማ በመሆኑ፣ ውዱን የግል ሪል ስቴት በርካቶች እየተጠቀሙበት እንደሚገኙ መላ ምቶች እየቀረቡ ነው፡፡ አቶ ለዓለም በዚህ ጉዳይ ላይ አስተዳደሩ እንደዳልመከረ ገልጸዋል፡፡

ሰንሻይን ሪል ስቴት በተለያዩ ቦታዎች መለስተኛ ቤቶችን እየገነባ የሚገኝ ግዙፍ ኩባንያ ነው፡፡ የሰንሻይን ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሳሙኤል ታፈሰ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በመሀል ከተማ ከግለሰብ እየገዙ የሪል ስቴት ልማት ማካሄድ አዋጭ አይደለም፡፡ የመኖሪያ ቤት ችግሩን ይፈታል ብለውም አያምኑም፡፡

‹‹እኛ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ግንባታ የምናካሂድበት ቦታ አለን፣ ከዚያ በኋላ ግን ቦታ የማይቀርብ ከሆነ ወደ ሌሎች ዘርፎች ትኩረት እናደርጋለን፤›› በማለት አቶ ሳሙኤል ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በመሀል ከተማ በሚያካሂዳቸው የመልሶ ማልማት ፕሮግራሞች ቦታ ቢያቀርብ፣ የግሉ ዘርፍና ለመኖሪያ ቤት እጥረት ብቻ ሳይሆን በከተማ ልማት ረገድ ትልቅ እገዛ ሊያበረክት እንደሚችል አቶ ሳሙኤል ለሪፖርተር ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ እስከ 1995 ዓ.ም. ድረስ በስፋትየመኖሪያ ቤት ግንባታ አልተካሄደም፡፡ በዚያ ወቅት እንኳ በተካሄደው የመኖሪያ ቤቶች ፈላጊ ሕዝብ በመቶ ሺሕ የሚቆጠር ነበር፡፡

በተለያዩ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያ ችግሮች ምክንያት የከተማ አስተዳደሩ ባቀደው መንገድ የቤቶች ግንባታ መካሄድ ባለመቻሉ ቀውስ እየተፈጠረ ይገኛል፡፡

ቁጥራቸው የማይናቅ የኅብረተሰብ ክፍሎች ከ40/60 ፕሮግራም ወደ ሪል ስቴት ኩባንያዎች መሄዳቸው እየተገለጸ ነው፡፡

ከግለሰቦች ይዞታ እየገዛ ግንባታ በማካሄድ ላይ የሚገኘው የፍሊንት ስቶን ሪል ስቴት፣ የተወሰኑ ገዥዎች ከ40/60 ቤቶች ፕሮግራም አቋርጠው ወይም ተስፋ ቆርጠው ወደ እነሱ እየመጡ መሆኑን አቶ ፀደቀ አረጋግጠዋል፡፡ 

Standard (Image)

ዳንጎቴ ከናይጄሪያና ሴራሊዮን ባሻገር በኢትዮጵያ ትልቁን ሽያጭ ማከናወን እንደቻለ ይፋ አደረገ

$
0
0
  • በስድስት ወራት 1.1 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ሲሚንቶ በኢትዮጵያ ሸጧል
  • በአፍሪካ ከ15 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን በላይ ለገበያ አቅርቧል

የናይጄሪያን 65 በመቶ የሲሚንቶ ገበያ እንደተቆጣጠረ የሚገመተው ዳንጎቴ ሲሚንቶ፣ በኢትዮጵያ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ብቻ 1.1 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ለገበያ ማቅረቡን አስታወቀ፡፡ ይህ የምርት መጠን በናይጄሪያና በሴራሊዮን ለገበያ ከቀረበው ቀጥሎ በአፍሪካ ከፍተኛ ሽያጭ ያስመዘገበበት ሊሆን በቅቷል፡፡

ዳንጎቴ ሲሚንቶ ሰኞ ሐምሌ 24 ቀን 2009 ዓ.ም. ባሰራጨው መረጃ መሠረት፣ ከናይጄሪያ ውጪ በሌሎች የአፍሪካ ገበያዎች ከሚያካሂደው የሲሚንቶ ሽያጭ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ የ12.6 በመቶ ጭማሪ የተመዘገበበት የምርት መጠን ለሽያጭ አቅርቧል፡፡ በዚህም ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ ውስጥ ከተመዘገበው የ24 ሚሊዮን ዶላር ወይም የ76 ቢሊዮን ናይራ (አንድ ዶላር በ315 ናይራ ይመነዘራል) ገቢ ይልቅ ባለፉት ስድስት ወራት የ394 ሚሊዮን ዶላር ወይም የ124.4 ቢሊዮን ናይራ ገቢ በማስመዝገብ የ63.7 በመቶ ጭማሪ ለማሳየት በቅቷል፡፡

ኩባንያው ምንም እንኳ በኢትዮጵያ የ1.1 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን የሲሚንቶ ምርት በማምረት ለገበያ ማቅረቡን ቢጠቀስም፣ በገንዘብ ረገድ ምን ያህል ገቢ እንዳገኘበት አልገለጸም፡፡ ከኢትዮጵያ ባሻገር በናይጄሪያ የ6.9 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን እንዲሁም በሴራሊዮን የ4.7 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ሲሚንቶ በማምረት መንፈቀ ዓመቱን አገባዷል፡፡ ኦዲት ባልተደረገው ሪፖርት መሠረት፣ በናይጄሪያ የተመረተው ሲሚንቶ አምና በተመሳሳይ ወቅት ከተመረተው የ8.8 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን በንፅፅር የዘንድሮ ቅናሽ አሳይቷል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በአገሪቱ ዝናባማ ወቅት በመሆኑ የግንባታ ዘርፉ በመቀዛቀዙ እንደሆነ የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኦን ቫን ድረ ዌድ መግለጻቸው ተዘግቧል፡፡

ከሦስቱ አገሮች በተጓዳኝ በሴኔጋል የ700 ሺሕ ሜትሪክ ቶን፣ በካሜሩን የ600 ሺሕ ሜትሪክ ቶን፣ በጋና የ500 ሺሕ ሜትሪክ ቶን ሲሚንቶ ምርት ለገበያ ያቀረበው ዳንጎቴ፣ በታንዛኒያ የ400 ሺሕ ሜትሪክ ቶን እንዲሁም በዛምቢያ የ300 ሺሕ ሜትሪክ ቶን ሲሚንቶ በመሸጥ በአፍሪካ እየተስፋፋ መጥቷል፡፡ በጠቅላላው ፓን አፍሪካ ገበያ እያለ በሚጠራው የአፍሪካ አገሮች መዳረሻ ገበያዎቹ ያከናወነው የሽያጭ መጠን የ64 በመቶ የገቢ ጭማሪ አስገኝቶለታል፡፡ ይህም ሆኖ በናይጄሪያ ከተመዘገበው የ291.4 ቢሊዮን ናይራ ገቢ አኳያ ሲታይ፣ ከአፍሪካ አገሮች የተገኘው 124.4 ቢሊዮን ናይራ በመገኘቱ የኩባንያው ዋና ገበያ የተመሠረተው በናይጄሪያ መሆኑን ያሳያል፡፡

በጠቅላላው በተገባደዱት ስድስት ወራት ውስጥ የናይጄሪያን ጨምሮ 15.2 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ሲሚንቶ ለገበያ ማቅረቡን የኩባንያው መረጃ ያመለክታል፡፡፡ በናይጄሪያ የተመረተውና ለገበያ የቀረበው ከሌሎች አገሮች አብላጫ ያለው ምርት ቢሆንም፣ በውጭ ምንዛሪ የተገኘው የሌሎች አገሮች ገቢ ወደ ናይጄሪያ መገበያያ ሲመነዘር ግን ከፍተኛ በመሆኑ ለኩባንያው ትልቅ የገቢ መጠን ማስመዝገብ እንዳስቻለው ዋና ሥራ አስፈጻሚው ጠቅሰዋል፡፡

በኢትዮጵያ በስድስት ወራት ውስጥ ለገበያ ያቀረበው የ1.1 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን የምርት መጠን አብዛኞቹ ሲሚንቶ ፋብሪካዎች በዓመት ውስጥ ለማምረት የሚጣጣሩበት መጠን እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ዳንጎቴ በኢትዮጵያ ሙገር አካባቢ በገነባው ፋብሪካ በዓመት የማምረት አቅሙ 2.5 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ነው፡፡ ይህንኑ መጠን በእጥፍ የማሳደግ ውጥን እንዳለውና ለገነባው ፋብሪካ ያወጣውን የ500 ሚሊዮን ዶላር ወጪ በእጥፍ በማሳደግና የማስፋፊያ ግንባታ በማካሄድ ምርቱን በእጥፍ እንደሚጨምር የኩባንያው ባለቤት አሊኮ ዳንጎቴ፣ ፋብሪካው በተመረቀበት ወቅት ማስታወቃቸው አይዘነጋም፡፡ በአሁኑ ወቅትም ምርቱን ወደ ጎረቤት አገሮች በተለይም ወደ ኬንያ መላክ እንደጀመረ ይታወቃል፡፡

ምንም እንኳ በኢትዮጵያ በተቀሰቀሰው ሕዝባዊ ተቃውሞ ምክንያት ጉዳት ከደረሰባቸው የውጭ ኩባንያዎች አንዱ ቢሆንም፣ በሪፖርቱ እንዲህ ያሉትን ችግሮች አልጠቀሰም፡፡ ከዚህም ባሻገር ኩባንያው የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ችግር ትልቅ ራስ ምታት ሆኖበት መቆየቱን ሲገልጽ እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ተደጋጋሚ የኃይል መቆራረጥ በምርት ሥራው ላይ ሳንካ መፍጠሩንም ሲገልጽ ቆይቷል፡፡

ዳንጎቴ በአሁኑ ወቅት 14 አፍሪካ አገሮችን ያዳረሰ የኢንቨስትመንትና የንግድ እንቅስቃሴ የዘረጋ ግዙፍ አፍሪካዊ ኩባንያ ሆኗል፡፡ በሲሚንቶ ዘርፍ የሚያደርገው መስፋፋት እንደ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ያሉትን አገሮች በማካተት ላይ ይገኛል፡፡ ከሲሚንቶ ባሻገር በስኳር ፋብሪካዎች፣ በምግብ ሸቀጦች ማምረቻና ማከፋፈያዎች፣ ወዘተ. ሰፊ የገበያ ድርሻ ለመያዝ የበቃ ኩባንያ ነው፡፡ በኢትዮጵያም በስኳር ልማት ዘርፍ የመሰማራት ፍላጎት እንዳለው ማስታወቁ ይታወሳል፡፡ 

Standard (Image)

ከአንድ ዓመት በላይ የዘገየው የንግድ ምክር ቤቱ ጉባዔና ምርጫ ለመስከረም ቀን ተቆረጠለት

$
0
0

ሲያወዛግብ የቆየው የኢትዮጵያ የንግድና የዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔና የሥራ አስፈጻሚው ቦርድ አመራሮች ምርጫ እንደሚካሄድ መነገር የጀመረው፣ ዓምና ሐምሌ ላይ ነበር፡፡ ተራዘመ ቢባል በ2009 ዓ.ም. መስከረም መጨረሻ ላይ ጠቅላላ ጉባዔው እንደሚጠራ ንግድ ምክር ቤቱ መግለጹ ይታወሳል፡፡ ነገር ግን የተባለው ሳይደረግ፣ ጠቅላላ ጉባዔው እንዳይካሄድ እንቅፋት ሆነዋል የተባሉ ጉዳዮችም መቋጫ ሳያገኙ ድፍን አንድ ዓመት ተቆጠረ፡፡

በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን የሚመራው የዳይሬክተሮች ቦርድ፣ የሥልጣን ዘመኑ ካበቃ ከአንድ ዓመት በላይ ቢሆነውም ሥልጣኑን ለባለተራ ሊያስተላልፍ አልቻለም፡፡ በንግድ ምክር ቤቱ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት፣ የአንድ ቦርድ የሥልጣን ዘመን በሁለት ዓመት የተገደበ ከመሆኑ አንፃር ሕገ ደንቡን መተላለፉም ተቋሙን አጣብቂኝ ውስጥ ከቶታል፡፡

ንግድ ምክር ቤቱን የሚመራው ቦርድ በንግድ ምክር ቤቱ ታሪክ ባልታየ አኳኋን፣ በሕግ ከተቀመጠለት በኃላፊነት የመቆየት ጊዜ በላይ የአመራርነት ቦታውን ይዞ የቆየበት ዋነኛ ምክንያትም ለመስከረም 2009 ዓ.ም. ቀን የተቆረጠለትን የጠቅላላ ጉባዔ ከመጥራት የሚያግድ እንቅፋት እንደገጠመው በማስታወቁ ነበር፡፡

ከአንድ ዓመት በፊት ጠቅላላ ጉባዔውን ጠርቶ ኃላፊነቱን ማስረከብ ያልቻለበት ምክንያት ከ18 አባል ምክር ቤቶች ውስጥ በሁለት ምክር ቤቶች ከሕግና ደንብ ውጭ የተፈጸመ የምርጫ ሒደትና የአባልነት ምግዘባ ክፍተት መታየቱ ሲሆን፣ ይህ ጉዳይ እልባት ሳይሰጠው ጠቅላላ ጉባዔ ማካሄዱ ሕግ መጣስ ነውም ተብሏል፡፡

በኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ወኪሎቻቸውን የላኩበት አግባብ ሕግና ደንብን ያልተከተለ አሠራር በመሆኑ፣ ችግሩ ታይቶባቸዋል የተባሉት ንግድ ምክር ቤቶች ዳግመኛ ምርጫ ያድርጉ ተብሏል፡፡ ሆኖም ግን ዳግመኛ ምርጫው ባለመደረጉ የአገር አቀፉ ንግድ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ሁለት ጊዜ ተሰርዟል፡፡ በዚህ መካከል የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ ተመድቦ ጉዳዩን እንዲከታተል ከተደረገ በኋላም ቢሆን መፍትሔ ሳይገኝ ቆይቷል፡፡

ሕግና ደንቡ በሚያዘው መሠረት፣ በአገር አቀፉ ንግድ ምክር ቤት ውስጥ ለመወከል የሚያስችላቸውን ምርጫ ያላካሄዱና በሕገ ደንባቸው ከተቀመጠው የኃላፊነት ዘመን በላይ በተደጋጋሚ ሥልጣን ላይ እየወጡ ለዓመታት የቆዩ ግለሰቦች ጉዳይ ታይቶ እልባት እንዲሰጥበት ለአጣሪ ኮሚቴው የሁለት ወር ጊዜ ተሰጥቶት ነበር፡፡

መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ ተቋቁሞ እስኪያጣራ የሥልጣን ዘመኑ ያበቃው የቦርድ አመራር፣ ለተጨማሪ ሁለት ወራት በሥልጣን የመቆየት ጊዜው ተራዝሞለት፣ በሚገኘው መፍትሔ መሠረት ምርጫው ከጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. ማለፍ እንደሌለበት ስምምነት ላይ ተደርሶም ነበር፡፡

መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴውም የተቋቋመው ጥቅምት 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ሲሆን፣ ተከሰቱ የተባሉትን ችግሮች በሁለት ወራት ውስጥ በማጥራት፣ በተቀመጠው ጊዜ ውስጥ የደረሰበትን ውጤት አስታውቋል፡፡ በአቶ ሰለሞን እንግዳወርቅ የሚመራው የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ቦርድ፣ ጠቅላላ ጉባዔውና ምርጫው ጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. እንደሚካሄድ ካሳወቀ በኋላ ግን፣ በመካከሉ ንግድ ሚኒስቴር የተጠራው ጉባዔ ላልተወሰነ ጊዜ እንዲታገድ በማለት ጥር 22 ቀን 2009 ዓ.ም. ውሳኔ አሳልፏል፡፡ በመሆኑም ጉዳዩን ከምክር ቤቱ አመራር በማውጣት ዕግዱን ባወጣው በንግድ ሚኒስቴር ሥር እንዲወድቅ አድርጎታል፡፡ ይህ በመሆኑም ቀድሞንም የዘገየውን ጠቅላላ ጉባዔ የንግድ ሚኒስቴር ውሳኔ እስኪታወቅ ድረስ ይበልጥ እንዲዘገይ ምክንያት ሆኗል፡፡

በንግድ ምክር ቤቶቹ ጉዳይ ጣልቃ ላለመግባት ዳር ዳር ሲል የቆየው የንግድ ሚኒስቴር፣ የንግድ ምክር ቤቶች ጠቅላላ ጉባዔ ከመካሄዱ በፊት የተፈጠሩትን ችግሮች በራሴ መንገድ አጣራለሁ በማለት የወሰደው ዕርምጃ ግን፣ እንደተጠበቀው በቶሎ መፍትሔ ሊያስገኝ ስላልቻለ፣ ተሰናባቹ ቦርድ ከተሰጠው ጊዜ በላይ አንድ ዓመት ጨምሮ በኃላፊቱ እንዲቆይ አድርጎታል፡፡

ንግድ ሚኒስቴር ዕገዳውን ሲጥል፣ ጉዳዩን አጣርቶ ችግር እንዳለባቸው የታወቁት ምክር ቤቶችም በድጋሚ ጠቅላላ ጉባዔ እንዲጠሩ በማድረግ፣ ሕጋዊ ወኪሎቻቸው የሚሳተፉበት የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ እንደሚካሄድ ቢያሳውቅም፣ ይህንን ውሳኔ ካስተላለፈ ከሰባት ወራት በላይ ተቆጥረዋል፡፡

ይኸው የተንዛዛው ሒደት መቋጫ በማጣቱ ተሰናባቹ ቦርድ ኃላፊነቱን ይዞ እንዲቆይ ቢያደርገውም፣ ለጉዳዩ ምንም ዓይነት መፍትሔ ሳይሰጠው መቆየቱ ግን በተደጋጋሚ ጥያቄዎችን እያስነሳ ነው፡፡ የምክር ቤቱ አባላት የሥልጣን ዘመኑ ያበቃለት  ቦርድ ጉዳዩን ችላ ብሎታል በማለትም እየተቹ ነው፡፡ ምክር ቤቱ በበኩሉ ጠቅላላ ጉባዔውን ለመጥራት የተቻለውን ሲያደርግ መቀቆየቱን ይናገራል፡፡

ዳግመኛ ጠቅላላ ጉባዔ እንዲጠሩ ከተወሰነባቸው መካከል የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት አንዱ ቢሆንም፣ ጠቅላላ ጉባዔውን ጠርቶ ዳግመኛ የአመራር አባላት ምርጫ ካካሄደ እንኳ ከሦስት ወራት በላይ ተቆጥረዋል፡፡ ሌላው ሕገወጥ ምርጫ አካሂዷል የተባለው የኢትዮጵያ የዘርፍ ምክር ቤት ነው፡፡ ይህ ምክር ቤት በተላለፈበት ውሳኔ መሠረት ማካሄድ ይጠበቅበት የነበረውን ምርጫ ሳያካሂድ እስካሁን መቆየቱም፣ ለአገር አቀፍ ምክር ቤቱ ጠቅላላ ጉባዔ መዘግየት እንቅፋት ፈጥሯል ተብሏል፡፡

በአቶ ሰለሞን የሚመራው የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ቦርድም ቢሆን፣ ከሥልጣን ዘመኑ በላይ የዚህን ያህል ጊዜ መቆየቱ አግባብ እንዳልሆነ በማሳወቅ ንግድ ሚኒስቴር ያገደው ጠቅላላ ጉባዔ መልሶ እንዲጠራ ግፊት ማድረግ ነበረበት እየተባለ ነው፡፡

የኃላፊነት ዘመኑ ያበቃው የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ሰለሞን  ጠቅላላ ጉባዔው መዘግየቱን አምነው፣ እሳቸው የሚመሩት ቦርድ ግን ለንግድ ሚኒስቴር ተደጋጋሚ ደብዳቤ በመጻፍ አስታውቋል ብለዋል፡፡ ‹‹እኛ እንዲህ ባለው ሁኔታ ውስጥ ለመቆየት ፍላጎት ባይኖረንም፣ የንግድ ሚኒስቴር ውሳኔን በመጠበቅ ላይ ነን፤›› በማለት ይገልጻሉ፡፡  

የተጓተተው ምርጫ ከዚህ በላይ መቆየት እንደሌለበት የሚገልጹት አቶ ሰለሞን፣ ከአሥር ወራት በላይ የዘገየው ጠቅላላ ጉባዔም በአስቸኳይ እንዲጠራ መወሰኑን ተናግረዋል፡፡ ምርጫው መስከረም 30 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲካሄድ ቦርዱ ውሳኔ ማሳለፉንና ይህንንም የሚገልጽ ደብዳቤ ለንግድ ሚኒስቴር መላኩን ጠቅሰዋል፡፡ አቶ ሰለሞን ከዚህ በላይ ኃላፊነቱን ይዞ መዝለቅ አስቸጋሪ እንደሆነባቸውም ሳይገልጹ አላለፉም፡፡

ሌሎች ወገኖች ደግሞ ምርጫው እስከ መስከረም ለምን ይቆያል? የሚል መከራከሪያ በማንሳት፣ የንግድ ሚኒስቴር ዝምታ ግራ እንዳጋባቸው ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡  

የትግራይ ክልል የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ አሰፋ ገብረ ሥላሴ በበኩላቸው፣ ምርጫው የዚህን ያህል ጊዜ መቆየቱ አግባብ እንዳልነበር ከሚገልጹት ወገኖች አንዱ ናቸው፡፡  

በክልል ደረጃ ንግድ ምክር ቤታቸው በተገቢው አኳኋን እየሠራ እንደሚገኝ የጠቀሱት አቶ አሰፋ፣ የአገር አቀፉ ምክር ቤት ጉዳይ እንዲህ ባለ መንገድ ያለመፍትሔ መዝለቁ ግን ያሳስበናል ብለዋል፡፡ አቶ አሰፋ አያይዘው እንደገለጹት፣ አንድ ጠቅላላ ጉባዔ ለማካሄድ ለወራት ሲንከባለል መቆየቱ ከደንብና ከአዋጁ ውጭ ያደርገዋል፡፡

ንግድ ሚኒስቴር እስካሁን ጠቅላላ ጉባዔውን ለማካሄድ የሚያስችል ምንም ዓይነት ውሳኔ አለመወሰኑ በብሔራዊ ንግድ ምክር ቤቱ ላይ የሚያሳርፈው ተፅዕኖ ከግምት ውስጥ አልገባም የሚሉት አቶ አሰፋ፣ ጠቅላላ ጉባዔ እንዲጠራ ከስድስት ወራት በላይ ጊዜ መውሰዱ አግባብ እንዳልሆነም ያምናሉ፡፡ ጊዜው በሔደ ቁጥር ደንብና ሕጎች እየተጣሱ መምጣታቸውን ስለሚያሳይ፣ የታገደው ጠቅላላ ጉባዔ በአስቸኳይ መካሄድ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡

የዘርፍ ምክር ቤት ጉዳይ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴርን ውሳኔ የሚመለከት ቢሆንም፣ የዘርፍ ምክር ቤቱ ምርጫ በአስቸኳይ እንዲያካሂድ ንግድ ሚኒስቴር ግፊት ማድረግ ነበረበት ይላሉ፡፡ ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች ደግሞ የዘርፍ ምክር ቤቱ በራሱ ምክንያት ምርጫውን ካላካሄደ በእሱ ምክንያት የብሔራዊ ምክር ቤቱን ጠቅላላ ጉባዔ አለማካሄድ ተገቢነት እንደሌለው ያምናሉ፡፡

አቶ ሰለሞን በበኩላቸው ጠቅላላ ጉባዔው በቶሎ እንዲካሄድ የተለያዩ ጥረቶች ተደርገዋል ይላሉ፡፡ በመሆኑም ጠቅላላ ጉባዔውን ለመጥራት የሚያስችል ሁኔታ ላይ ስለተደረሰ ይህንኑ ለንግድ ሚኒስቴር ገልጸናል ብለዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት ከ18ቱ የአገር አቀፉ ንግድ ምክር ቤት አባል ምክር ቤቶች ውስጥ 17ቱ ማሟላት ያለባቸውን ሒደቶች አሟልተዋል ተብሏል፡፡ በሕገ ደንቡ መሠረት ሐምሌ 2008 ዓ.ም. ያካሄደው ምርጫ ከሕግ ውጭ ነው ተብሎ ውድቅ የተደረገበትና ዳግመኛ ምርጫውን እንዲያካሂድ በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የተወሰነበት የኢትዮጵያ የዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ብቻ ተገቢውን ሒደት እንዳልተወጣ እየተገለጸ ነው፡፡

ይህ ሆኖ ዳግመኛ ምርጫውን ሐምሌ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲያካሂድ በመወሰኑ፣  ታግዶ የቆየውን የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ማካሄድ የሚቻልበት ወቅት መቃረቡን አቶ ሰለሞን ገልጸዋል፡፡

ለጠቅላላው ጉባዔ አለመካሄድ እንደ ችግር የነበሩ ጉዳዮች በመፈታታቸው ሐምሌ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. እንደሚካሄድ የሚጠበቀው የአገር አቀፉ የዘርፍ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ ተደረገም አልተደረገ፣ አገር አቀፍ የንግድና ዘርፍ ምክር ቤቱ ጉባዔና ምርጫ ከመስከረም 30 ቀን 2010 ዓ.ም. ሳያልፍ እንደሚያካሄድ እምነት አላቸው፡፡ ንግድ ሚኒስቴርም በጥር ወር 2009 ዓ.ም. ጠቅላላ ጉባዔ እንዳይካሄድ ያገደበት ምክንያት ስለተፈታ፣ በተያዘው ፕሮግራም መሠረት ጠቅላላው ጉባዔ እንዲካሄድ ይፈቅዳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አቶ ሰለሞን ያምናሉ፡፡

ጉባዔውም ሆነ ምርጫው ከዚህ ቀደም በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መሠረት እንዲካሄድ ያላደረግነው ጥረት አልነበረም ያሉት አቶ ሰለሞን፣ ከምክር ቤቱ አባላት ግፊት አላደረጋችሁም የሚለውን ወቀሳ አስተባብለዋል፡፡ ‹‹ጠቅላላ ጉባዔውን ለመጥራት መስዋዕትነት የከፈልነው በሕጋዊ መንገድ ለማካሄድ ሲባል እንጂ በቦታው ለመቆየት አይደለም፤›› ይላሉ፡፡

 

Standard (Image)

ከ100 ሚሊዮን ዶላር በላይ ያስገኘው የሥጋ ዘርፍ ዓሣን ጨምሮ ማርና ወተት ለውጭ ገበያ አቅርቧል

$
0
0

በተጠናቀቀው የ2009 በጀት ዓመት ወደ ውጭ ከተላኩ የሥጋና የሥጋ ተረፈ ምርቶች፣ የዓሣ፣ የማርና የወተት ምርቶች የወጪ ንግድ፣ ከ104 ሚሊዮን ዶላር በላይ መገኘቱን ያስታወቀው የሥጋና ወተት ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት፣ በዘንድሮው የወጪ ንግድ አፈጻጸም ጥቂት ጭማሪ መታየቱንም ገልጿል፡፡

የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኃይለ ሥላሴ ወረስ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ዘንድሮ ወደ ውጭ ይላካል ተብሎ ከታቀደው 31,400 ቶን የሥጋ ተረፈ ምርት፣ 19,779 ቶን ተልኮ 100.2 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቷል፡፡ ይገኛል ተብሎ የታቀደው ገቢ 146 ሚሊዮን ዶላር ቢሆንም፣ በጠቅላላው ከሥጋና የሥጋ ተረፈ ምርት የወጪ ንግድ የ68.5 በመቶ ክንውን መመዝገቡን ኃላፊው አስታውቀዋል፡፡

ከዓሣ የወጪ ንግድም አንድ ሺሕ ቶን ምርት እንደሚላክና ከግማሽ ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሪ ገቢ ይጠበቅ ነበር፡፡ ይሁንና 44,345 ቶን ዓሣ ለበያ ቀርቦ 250 ሺሕ ዶላር ገቢ ሊገኝ እንደቻለ ተጠቅሷል፡፡ በዓሣ ዘርፍ የ47 በመቶ ክንውን መመዝገቡም ታውቋል፡፡

የሥጋና ዓሣ ሀብት ዘርፍ ከሚያካትታቸው ውስጥ ማርና ሰም አብረው የሚጠቀሱ የወጪ ንግድ ምርቶች ናቸው፡፡ ከ740 ቶን በላይ ማርና ሰም ለውጭ ገበያ ቀርቦ 4.15 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ተመዝግቧል ተብሏል፡፡ በዕቅድ የሚጠበቀው 1822 ቶን ማርና ሰም ተልኮ ከአሥር ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ነበር፡፡

ከእነዚህ ምርቶች ባሻገር ወተትም ለውጭ ገበያ ቀርቧል፡፡ ከ2.7 ሚሊዮን ሊትር ይጠበቅ የነበረው ገቢ 410 ሺሕ ዶላር ቢሆንም፣ ወደ ውጭ መላክ ከተቻለው 2.5 ሚሊዮን ሊትር ወተት ሊገኝ የቻለው 280 ሺሕ ዶላር በመሆኑ ምንም እንኳ የተላከው ምርት ከዕቅዱ ጋር የተቀራረበ መጠን ቢኖረውም ከገቢ አኳያ ግን ሰፊ ልዩነት ሊታይበት ችሏል፡፡

በጠቅላላው በ2009 በጀት ዓመት ከሥጋና ሌሎች ምርቶች ይጠበቅ የነበረው ገቢ 157.2 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን፣ 104 ሚሊዮን ዶላር ክንውን መመዝገቡን አቶ ኃይለ ሥላሴ አስታውቀዋል፡፡ ከዕቅዱ የ66.6 በመቶ ክንውን መተግበሩን ገልጸው አምና ከተመዘገበው የ102.5 ሚሊዮን ዶላር አፈጻጸም አኳያም መጠነኛ ጭማሪ መታየቱን አስታውሰዋል፡፡

ምንም እንኳ በሥጋና የሥጋ ተረፈ ምርት መስክ የአገር ውስጥና የውጭ ቄራዎች እየተሳተፉ ቢመጡም፣ ወደ ውጭ የሚላከው መጠን ግን እንደሚጠበቀው ሊያድግ አልቻለም፡፡ ከዚህም ባሻገር የሥጋ ምርቱን የሚቀበሉ የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች በየጊዜው ዕገዳ በመጣል ምርቱ ተቀባይነት ሲያጣ ይታያል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተደጋጋሚ በተፈጠሩ ችግሮች ሳቢያ፣ ኢትዮጵያ ከሥጋ የወጪ ንግድ በ35 ሚሊዮን ዶላር የሚገመት ኪሳራ እንዳጋጠማት ይገመታል፡፡፡

በ2009 ዓ.ም. በጠቅላላው ከተመዘገበው የ2.9 ቢሊዮን ዶላር የወጪ ንግድ ገቢ ውስጥ ከግብርና ምርቶች 2.1 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን የንግድ ሚኒስቴር መረጃ ይጠቁማል፡፡ ከግብርና ምርቶች ብቻ ከሦስት ቢሊዮን ዶላር ይጠበቅ ነበር፡፡ ከግብርና ምርቶች ቡና 881 ሚሊዮን ዶላር በማስገኘት ቀዳሚውን ድርሻ ይዟል፡፡ በቡና የተመዘገበው ውጤት ከስድስት ዓመት በፊት ከተመዘገበው የ840 ሚሊዮን ዶላር አኳያም የዘንድሮው ከፍተኛው ሆኖ ተገኝቷል፡፡

ከማኑፋክቸሪንግ ውጤቶች 916.8 ሚሊዮን ዶላር እንደሚገኝ ታቅዶ፣ በውጤቱ ከግማሽ በታች 413 ሚሊዮን ዶላር ሊገኝ እንደቻለ ታውቋል፡፡ ሌላው እጅጉን ዝቅተኛ ውጤት የተመዘገበበት የማዕድናት ዘርፍ የወጪ ንግድ ነው፡፡ ከታቀደው የ719 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ውስጥ፣ ከማዕድናት የተገኘው 231 ሚሊዮን ዶላር በመሆኑ ከዕቅዱም ብቻ ሳይሆን፣ ከዚህ ቀደም ከወርቅ ብቻ እንኳ ይገኝ ከነበረውም ይልቅ ዝቅተኛ ሆኗል፡፡ ከወርቅ ብቻ ከ600 ሚሊዮን ዶላር ጀምሮ በዓለም ገበያ መዋዠቅ ሳቢያ አነሰ ቢባል እስከ 400 ሚሊዮን ዶላር ሲገኝ መቆየቱን ይታወቃል፡፡

ንግድ ሚኒስቴር በ2009 ዓ.ም. የተገኘው የ2.9 ቢሊዮን ዶላር ከታቀደው 4.75 ቢሊዮን ዶላር (የብሔራዊ ፕላን ኮሚሽን ግን 6.7 ቢሊዮን ዶላር ይጠበቅ እንደነበር አስፍሯል) አኳያ ዝቅተኛው አፈጻጸም ቢሆንም አምና ከተመዘገበው 2.85 ቢሊዮን ዶላር አኳያ፣ በ50 ሚሊዮን ዶላር ጭማሪ የታየበት ለውጥ መታየቱን ጠቁሟል፡፡ 

Standard (Image)

ነባር አመራሮች የሕግ ጥሰት መፈጸማቸው የተረጋገጠበትና አዳዲስ ኃላፊዎች የተመረጡበት የዘርፍ ምክር ቤት ጉባዔ

$
0
0

 

ከአንድ ዓመት በላይ ሲያወዛግብ የቆየው የኢትዮጵያ የዘርፍ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ፣ በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ውሳኔ ተሽሮ በድጋሚ ተካሄደ፡፡ ዳግም በተካሄደ የአመራሮች ምርጫም አዲስ ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲሁም የቦርድ አባላትን በመምረጥ ተቋጭቷል፡፡ ተሰናባቹ ቦርድ የፈጸማቸው የሕግ ጥሰቶች ይፋ ተደርገዋል፡፡

የኢትዮጵያ የዘርፍ ምክር ቤት ከአንድ ዓመት በፊት ያካሄደው ጉባዔና ምርጫ የሕግ ጥሰት እንደነበረበት በመረጋገጡ ጠቅላላ ጉባዔ ዳግመኛ እንዲካሄድ በተጠራውና ሐሙስ፣ ሐምሌ 27 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሄደው የማስተካከያ ምርጫ መሠረት፣ የኢትዮጵያ የዘርፍ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ የተመረጡት በዕለቱ ብቸኛ ዕጩ ሆነው የቀረቡት አቶ ኢያሱ ሞሲሳ የተባሉ ተወዳዳሪ ናቸው፡፡

የኦሮሚያ የዘርፍ ምክር ቤት ፕሬዚዳንትና የኦሮሚያ የንግድና የዘርፍ ማኅበራት ምክትል ፕሬዚዳንት የሆኑት አቶ ኢያሱ፣ ለኢትዮጵያ የዘርፍ ምክር ቤት ፕሬዚዳንትነት ብቸኛው ተወዳዳሪ ሆነው በቀረቡበት ምርጫ፣ ድምፅ ከሰጡ 99 አባላት ውስጥ የ97ኙን አብላጫ ድምፅ ማግኘት ችለዋል፡፡ ሆኖም ለፕሬዚዳንትነት የቀረቡት አቶ ኢያሱ ብቻ መሆናቸው ጥያቄ አስነስቷል፡፡

ይሁን እንጂ የማስተካከያ ምርጫውን ለማካሄድ ሁሉም የዘርፍ ምክር ቤቶች ለፕሬዚዳንትነት፣ ለምክትል ፕሬዚዳንትነት እንዲሁም ለቦርድ አባልነት የሚወዳደሩ ዕጩዎችን እንዲጠቁሙ ለጉባዔተኞቹ ዕድል ቢሰጥም፣ የኦሮሚያ የዘርፍ ምክር ቤት በብቸኝነት፣ ለፕሬዚዳንትነት ሊወዳደር የሚችል ዕጩ በማቅረቡ አቶ ኢያሱ ተመርጠዋል፡፡ ቀሪዎቹ የዘርፍ ምክር ቤቶች ለቦታው ዕጩዎችን ማቅረብ አልቻሉም፡፡

ለምክትል ፕሬዚዳንትነት ግን የአዲስ አበባና የአማራ ዘርፍ ምክር ቤቶች ዕጩዎችን በማቅረባቸው ከአማራ የዘርፍ ምክር ቤት የተወከሉት አቶ ልሳኑ በለጠ የኢትዮጵያ የዘርፍ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ ተመርጠዋል፡፡

ለቦርድ አባልነት በዕጩነት ከቀረቡት 16 ተወዳዳሪዎቸ ውስጥ አቶ አቶ ቢተው ዓለሙ፣ ሻለቃ ኃይሉ ጉርሙ፣ አቶ ወዮማ ገሜሳ፣ አቶ ሰዒድ አብዱራህማን፣ አቶ ደስታው ሰመነ፣ አቶ ጋሻው ጉግሳ፣ አቶ ሐሰን አብዱላሒም (ዶ/ር)፣ አቶ አበባየሁ ግርማና አቶ ደስታ ብዙየነ ለቦርድ አባልነት የሚያበቃቸውን ድምፅ በማግኘት ተመርጠዋል፡፡ ከተሰናባቹ ቦርድ ሰባቱ በድጋሚ መመረጣቸውን ማረጋገጥ ተችሏል፡፡

ከነባር የዘርፍ ምክር ቤቱ አመራሮች ውስጥ በተለይ በፕሬዚዳንትነት ያገለገሉት አቶ ገብረ ሕይወት ገብረ እግዚአብሔር፣ በጉባዔው ቢታደሙም በምርጫ ሳይሳተፉ ቀርተዋል፡፡ በዕለቱ ንግግር ማድረግ ያልቻሉት አቶ ገብረ ሕይወት፣ እንደ ጠቅላላ ጉባዔ አባል ድምፅ መስጠትም አልተፈቀደላቸውም ነበር፡፡ ይህ የሆነውም የማስተካከያ ምርጫውን ለማካሄድ የሁሉም ክልሎች የዘርፍ ምክር ቤቶች ተወካዮቻቸውን እንዲልኩ በተጠየቁት መሠረት፣ ከዚህ ቀደም አቶ ገብረ ሕይወት የትግራይ ክልል የዘርፍ ምክር ቤት ለእሳቸው የውክልና መተማመኛ ባለመስጠቱ ለመምረጥም ሆነ ለመመረጥ የሚያስችላቸውን ዕድል እንዲያጡ አድርጓል፡፡

የትግራይ ክልል የዘርፍ ምክር ቤት በሐሙሱ ጠቅላላ ጉባዔ እንዲሳተፉ የመምረጥና መመረጥ መብት ኖሯቸው ከተወከሉት 11 ልዑካን ውስጥ የአቶ ገብረ ሕይወት ስም ባለመኖሩ በታዛቢነት በጠቅላላ ጉባዔው ለመታደም ተገደዋል፡፡ ከሕግና ደንብ ውጪ ነሐሴ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የዘርፍ ምክር ቤት በተካሄደው ምርጫ በምክትል በፕሬዚዳንትነት ተመርጠው ነበር የተባሉት አቶ አበባው መኮንንም በዚህ ምርጫ በዕጩነት አልቀረቡም፡፡

ከአንድ ዓመት በላይ ሲያጨቃጭቅ የነበረው የዘርፍ ምክር ቤት የምርጫ ሒደት አወዛጋቢ ሆኖ ከቆየባቸው ምክንያቶች አንዱ ከዘርፍ ምክር ቤት ሕገ ደንብ ውጪ ፕሬዚዳንቱና ምክትል ፕሬዚዳንቱ በተደጋጋሚ ራሳቸውን በማስመረጥ በኃላፊነት ቦታ ቆይተዋል የሚለው ይገኝበታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ባለፈው ዓመት በተካሄደው ጠቅላላ ጉባዔ፣ ከአባላት ዕውቅና ውጪ ሕገ ደንቡን ለማሻሻል ተሞክሯል የሚለው ትችትም ሲሰነዘር መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡ እነዚህን ጉዳዮች ሲመረምር የቆየው የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር፣ የደረሰበትን ድምዳሜ ይፋ አድርጓል፡፡ በሐሙሱ ጉባዔ የተገኙት የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ቦጋለ ፈለቀ ይህንኑ ገልጸዋል፡፡

በአቶ ገብረ ሕይወት ይመራ የነበረው ቦርድ አገር አቀፉ የዘርፍ ምክር ቤት ነሐሴ 28 እና 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ባካሄደው ስምንተኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔ፣ አዲስ የሥራ አመራር ቦርድ ምርጫ ማካሄዱን ያስታወሱት ሚኒስትር ዴኤታው፣ ጠቅላላ ጉባዔው የሕግ ጥሰቶች ተፈጽመውበታል በማለት በበርካታ አባላት ቅሬታዎች ቀርበውበት እንደነበር ገልጸዋል፡፡ በቅሬታዎቹ መነሻነት ሚኒስቴሩ የማጣራት ሥራውን ሲያከወናውን እንደቆየ ገልጸዋል፡፡ የተገኘውን ውጤትም ለጠቅላላ ጉባዔው አሳውቀዋል፡፡

 ነሐሴ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. የተደረገው ምርጫ የንግድና የዘርፍ ምክር ቤቶችን ለማቋቋም ከወጣው አዋጅ ቁጥር 341/96 እንዲሁም ይህንኑ አዋጅ ለማስፈጸም በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከወጣው መመርያ፣ ከማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብና ከጠቅላላ ጉባዔው የስብሰባ ቃለ ጉባዔ አንፃር ጉዳዩን በጥልቀት ሲመረምር እንደቆየ በማብራራት፣ የተደረገው ምርጫ የምክር ቤቱን መተዳደሪያ ደንብ አለመከተሉ ተረጋግጧል ብለዋል፡፡ በአቶ ገብረ ሕይወት የሚመራው ቦርድ አዋጅና ደንብ ያልጠበቀ ምርጫ አካሂዷል በተባለው የዓምናው ጠቅላላ ጉባዔ ወቅት ቀርቦ የነበረው የመተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያም ቢሆን አስፈላጊውን ሕጋዊ አካሄድ ጠብቆ እንዳልተዘጋጀ ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል፡፡ በአዋጅ ቁጥር 341/1995 መሠረት የዘርፍ ማኅበራትም ሆኑ የምክር ቤት አባላት፣ የአምራች ድርጅት ባለቤት መሆን አለባቸው የሚለውን ድንጋጌ ያልጠበቁ አካሄዶች መኖራቸውንና በአገር አቀፍ ደረጃ የሚገኙ የዘርፍ ማኅበራትም በተደረገው የጠቅላላ ጉባዔ እንዲሳተፉ በአግባቡ ጥሪ ስላልተላለፈላቸው ምርጫውም ሆነ ጉባዔ ችግሮች እንደነበሩበት መረጋገጡን ጠቅሰዋል፡፡

የታዩትን ክፍተቶች በመሙላት የምክር ቤቱን ህልውና ማስጠበቅ በማስፈለጉ፣ ሚኒስቴሩ ከሚመለከታቸው ጋር በመሆን የጠራውን የማስተካከያ ምርጫ፣ ያለ ችግር ለማካሄድ ሲጥር ቆይቷል ተብሏል፡፡ የተፈጠሩት ክፍተቶች የምክር ቤቱን ሕጋዊነትና ህልውና ጥያቄ ላይ መጣላቸውን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፣ እነዚህን ችግሮች በማረም የምክር ቤቱን ሕጋዊነትና ህልውና መመለስ እንደሚገባ አስታውቀዋል፡፡

ስለተፈጸሙት የሕግ ጥሰቶች የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የሕግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ተካልኝ ከድር አቅርበዋል፡፡ ትኩረት ሰጥተው ያብራሩት በዓምናው ጠቅላላ ጉባዔ ወቅት የመተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያው እንዲሁም የተመረጠው ቦርድ ሕጋዊነት ላይ ነበር፡፡

ምክር ቤቱ ሁለት መተዳደሪያ ደንቦች እንዳሉት የጠቀሱት ዳይሬክተሩ፣ አንዱ በ1999 ዓ.ም. የወጣው ደንብ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ዓምና በነሐሴ ወር ተሻሽሎ የወጣው አዲሱ ደንብ ነው፡፡ በ1999 ደንብ መሠረት አንቀጽ 24 ውስጥ ‹‹ደንቡን ለማሻሻል ከጠቅላላ ጉባዔው ተሳታፊዎች በ2/3ኛው መደገፍ አለበት፤›› የሚለው ተካቷል፡፡ በመሆኑም ነባሩን መተዳደሪያ ደንብ ለማሻሻል ድምፅ በመስጠት መሳተፍ የነበረባቸው 120 አባላት ቢሆኑም፣ የተሳተፉት ግን 73 ብቻ በመሆናቸው የማሻሻያ ደንቡን ለማፅደቅ ሕጋዊ መሠረት እንዳልነበረው ተጠቅሶ ተሻሻለ የተባለው ደንብ ውድቅ ተደርጓል፡፡

በ1999 ዓ.ም. በወጣውና ዓምና በተሻሻለው ደንብ መካከል ስላለው ልዩነት በሰጡት ማብራሪያም፣ ተለውጠዋል የተባሉትን ነጥቦች ጠቅሰዋል፡፡ በ1999 ዓ.ም. በወጣው ደንብ አንቀጽ 16 መሠረት አንድ የቦርድ አባል የአገልግሎት ዘመኑ ሁለት ዓመት ብቻ እንደሆነ ይጠቅሳል፡፡ አንድ ተመራጭ ማገልገል የሚችለውም ለሁለት የምርጫ ዘመን ብቻ መሆኑን አስፍሯል፡፡ ተሻሻለ በተባለው ደንብ ደግሞ የአንድ ተመራጭ የአገልግሎት ዘመን ሁለት ዓመት እንደሆነ ቢጠቅስም፣ በነባሩ ደንብ የተጠቀሰውን የአንድ ተመራጭ የሁለት የምርጫ ዘመን ቆይታን ሰርዞታል፡፡ ይህም ማለት አንድ ተመራጭ ያለጊዜ ገደብ ደጋግሞ እንዲመረጥ መፍቀዱን እንደሚያሳይ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡ ይህም ከቀረቡት ቅሬታዎች መካከል የቦርድ አባላት ከሁለት የምርጫ ዘመን በላይ በተደጋጋሚ ተመርጠዋል የሚለውን አቤቱታ እንደሚያሳይ ተጠቅሷል፡፡ ስለዚህ ይህ አንቀጽ ያለ ጊዜ ገደብ ለመመረጥ እንዲያስችል ተብሎ መዘጋጀቱ፣ በግልጽ ችግር እንዳለበት ማሳየቱን ከተደረገው ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ሌላው ሰፊ ምርመራ ተደርጎበታል የተባለው ጉዳይ፣ የተመረጠውን ቦርድ ሕጋዊነትን የተመለከተ ሲሆን፣ ነሐሴ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ተመረጠ የተባለውን ቦርድ ሕጋዊነት ለመወሰን በየትኛው ደንብ አግባብ ተመርጧል ከሚለው በመጀመር ፍተሻ መደረጉን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ አንፃር ነሐሴ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. የተደረገውን ጠቅላላ ጉባዔ በተመለከተ የተሰናዳው ቃለ ጉባዔ እንደሚያመለክተው፣ አዲሱን ደንብ በተመለከተ በቃለ ጉባዔው የሰፈረው ማሻሻያ፣ ደንቡን በጥልቀት ተመልክቶ እንዲያፀድቀው ለሚመለከተው የሥራ አመራር ቦርድ ውክልና ሰጥቷል የሚል እንደነበርም ታይቷል፡፡

ይህ የሚያሳየውም አዲሱ ደንብ በዚያን ቀን የፀደቀ ሳይሆን ነሐሴ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. የሚመረጠው ቦርድ ተመልክቶት ውክልና መስጠቱን አመላካች ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ሆኖም በአቶ ገብረ ሕይወት የሚመራውና ነሐሴ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. የተመረጠው ቦርድ፣ የተሻሻለውን ደንብ መስከረም 5 ቀን 2009 ዓ.ም. በማፅደቁና ሥራ ላይ በማዋሉ፣ የቀድሞው ቦርድ ነሐሴ 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ከተመረጠ ተፈጻሚ መሆን የነበረበት ነበሩ እንጂ አዲሱ ደንብ ባለመሆኑ ምርጫው ትክክል አይደለም ወደሚለው ድምዳሜ አድርሷል፡፡ ‹‹ይህ ከሆነ የተመረጡትን አባላት በነባሩ ደንብ አንቀጽ 16/5 መሠረት አዲስ የተመረጡት የቦርድ አባላትን ስንመለከት አብዛኛዎቹ ተመራጮች ከሁለት ጊዜ በላይ እንደተመረጡ በግልጽ ያመለክታል፤›› ያሉት ዳይሬክተሩ፣ ሌሎችም መረጃዎች ይህንኑ እንደሚያረጋግጡ ገልጸዋል፡፡ ስለዚህም በአቶ ገብረ ሕይወት ይመራ የነበረው ቦርድ በሕጋዊ መንገድ እንዳልመጣ ማረጋገጡን ተናግረዋል፡፡

 የሕግ ባለሙያው ማብራሪያ ከተሰማ በኋላ በዕለቱ የተገኙት የጠቅላላ ጉባዔ አባላት አስተያየት እንዲሰጡ ሲደረግ የሕግ ጥሰቱ መኖሩ እየታወቀ ውሳኔ ለመስጠት አንድ ዓመት መፍጀቱ ተገቢ እንዳልነበር የገለጹ ሲሆን፣ ሚኒስቴሩም ለውሳኔ መዘግየቱን በማመን ጥራት ያለው ሥራ ለመሥራት ሲባል ጊዜ መውሰዱን አስታውቋል፡፡  

በዕለቱ ቅሬታቸው ካሰሙ አባላት መካከል በቃለ ጉባዔ ከተያዘው አጀንዳ ውጪ ሐሳባቸው ተጣሞ ቀርቧል በማለት፣ ቦርዱ ከዕውቅናቸው ውጪ የራሱን ቃለ ጉባዔ እንዳዘጋጀ በመግለጽ የወቀሱም ነበሩ፡፡ በጠቅላላ ጉባዔው የተገኙት የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የምክር ቤቱን ህልውና ለመጠበቅ፣ ጣልቃ ላለመግባት ሲል መንግሥት ብዙ መታገሱን፣ ችግሮች ከተፈጠሩ በኋላም ቢሆን ለመፍታት የተደረጉ ምርመራዎችና ነገሩ በአፋጣኝ እንዳይቋጭ ማድጋቸውን ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ‹‹ቃለ ጉባዔ ተጣሞብናል፣ እኛ ያልነው አልተካተተም የሚባል ከሆነ የጠቅላላ ጉባዔው አባላት ብርቱ አመራር መምረጥ ይኖርባቸዋል፤›› በማለት የምክር ቤቱን አባላት ወርፈዋቸዋል፡፡

የኢትዮጵያ የዘርፍ ምክር ቤት ጉዳይ በዚህ መንገድ ሲቋጭ፣ ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከአዲሱ አመራር ጋር በጋራ ለመሥራት ቃል በመግባት ጉባዔውን አጠቃሏል፡፡

 

Standard (Image)

የመኪና ጎማን ከብልሽት የሚታደግ አዲስ ቴክኖሎጂ ለገበያ ቀረበ

$
0
0

 

  • በዓመት ከ180 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለጎማ ግዥ እንደሚውል ይገመታል

ምንጩ ከእንግሊዝ የሆነ፣ ታየር ፕሮቴክተር ሲላንት የተባለና ከ14 የዕፅዋት ዓይነት እንደተቀመመ የተነገረለት ድርድር ፈሳሽ በመኪና ጎማ እየተሞላ ከመፈንዳትና ከመተንፈስ ጉዳት የሚከላከል ብሎም በጎማ ብልሽት ምክንያት የሚደርሱ የትራፊክ አደጋዎችን ከመቀነስ አኳያ ጠቀሜታው እንደሚጎላ የታመነበት ቴክሎጂ ለገበያ ቀረበ፡፡

ቴክኖሎጂውን የፈበረከው ታየር ፕሮቴክተር ኢንተርናሽናል የተባለ የእንግሊዝ ኩባንያ ሲሆን፣ ወደ አገር ቤት ማስመጣት የጀመረው ደግሞ ታየር ፕሮቴክተር ኢትዮጵያ የተባለው የግል ድርጅት መሆኑ ታውቋል፡፡ የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ጄኔራል ባጫ ደበሌ፣ ስለቴክሎጂው ለአገር አቋራጭ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች፣ ሐምሌ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ሲያስተዋውቁ፣ ቴክኖሎጂው ለጎማ ዕድሳት ከሚወጣው ወጪ ውስጥ እስከ 75 በመቶ እንደሚያስቀር አስታውቀዋል፡፡ በዋናው አውቶቡስ ተራ መናኸሪያም ስለቴክኖሎጂው ጠቀሜታዎች በተግባር አሳይተዋል፡፡

ከመነዳሪ በሌላቸው ጎማዎች ውስጥ በተሞላው መከላከያ ፈሳሽ ሳቢያ፣ ተሽከርካሪዎች ጣውላ ላይ በተመቱ ትልልቅ ሚስማሮች ላይ ተነድተው ጎማቸው ቢበሳም ሳይፈዳና ሳይተነፍስ እንደቀድሟቸው ያለ ችግር ሲሽከርከሩ አሳይተዋል፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ በቤት አውቶሞቢል ጀምሮ እጅግ ግዙፍ ለሆኑ የግንባታ ተሽከርካሪዎችና ማሽነሪዎች እንደሚውል ተገልጿል፡፡

እንደ ጄኔራል ባጫ ማብራሪያ፣ የታየር ፕሮቴክተር ጠቃሜታዎች ከሚባሉት ውስጥ ጎማ እንዳይተነፍስ፣ በሙቀት የተነሳ ተለጥጦ ጥንካሬውን እንደያጣ እንዲሁም በከፍተኛ ቅዝቃዜ ምክንያትም እንዳይኮማተር በመከላከል የጎማውን ዕድሜ ይጨምራል፡፡ ከዚህም ባሻገር በስለታም ድንጋይ፣ በሚስማርና በማናቸውም ስለታም ነገሮች የተወጋ ጎማ እንዳይተነፍስ ከማድረግ ባሻገር የተወጋውን ክፍል በፍጥነት በመጠገን የተሽከርካሪ እንቅስቃሴ እንዳይሰተጓጎል የሚያስችል ነው፡፡ ቴክሎጂው በቀላል ተሽከርካሪዎች ጎማ ላይ እስከ ስድስት ሚሊ ሜትር፣ በከባድ ተሽከርካሪዎች ጎማ ላይ ደግሞ እስከ 12 ሚሊ ሜትር ስፋት ያለውን ቀዳዳ በፍጥነት የመድፈን አቅም እንዳለው ተጠቅሷል፡፡ በመሆኑም ለጎማ ጥገና በየጊዜው ከሚወጣው ወጪ እስከ 75 በመቶ እንደሚቀንስ ገልጸዋል፡፡

ለአንዱ ሊትር የጎማ መከላከያ ከ1,000 ብር በታች እንደሚሸጥ ያስታወቁት ጄኔራል ባጫ፣ ቴክኖሎጂው በአገሪቱ በሚገኙ ጎሚስታዎችና በወኪል አከፋፋዮች በኩል እንደሚቀርብ አስታውቀዋል፡፡ ቴክኖሎጂው እስኪለመድና አጠቃቀሙ በአግባቡ እስኪታወቅ ድረስ በኩባንያው የሠለጠኑ ባለሙያዎች አማካይነት በመኪኖች ጎማ ውስጥ እንደሚሞላ ጄኔራሉ ጠቅሰዋል፡፡

የታየር ፕሮቴክተር ኢትዮጵያ የኦፕሬሽን ሥራ አስኪያጅ አቶ ሳሚ ሚሊዮን በበኩላቸው፣ የእንግሊዝ ተመራማሪዎች ለዓመታት በማጥናት ለውጤት ያበቁት ይህ ቴክኖሎጂ ለገበያ መቅረብ የጀመረው እ.ኤ.አ. በ2005 ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት ከ80 በላይ አገሮች እየተጠቀሙበት እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ በአፍሪካም ግብፅ፣ ጋና፣ አልጄሪያ፣ ሞሮኮ፣ ታንዛኒያ፣ አንጎላ፣ ደቡብ አፍሪካ እንዲሁም በናይጄሪያ ጥቅም ላይ የዋለው ይህ ቴክኖሎጂ በኢትዮጵያ ብቻም ሳይሆን፣ በአፍሪካ ቀንድ አገሮች ውስጥ በታየር ፕሮቴክተር ኢትዮጵያ አማካይነት እንደሚሠራጭ አስታውቀዋል፡፡

ለመነሻ ያህልም በመጪዎቹ ስድስት ወራት ውስጥ ለ30 ሺሕ መኪኖች የሚዳረስ አቅርቦት እንደሚመጣ የተገለጸ ሲሆን፣ ቅድሚያውን ከሚያገኙት መካከል የግንባታ ተሽከርካሪዎችና ማሽነሪዎች፣ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡት እንደሆኑም ጄኔራል ባጫና አቶ ሳሚ አስታውቀዋል፡፡ 

አቶ ሳሚ ከዚህ ቀደም በእንግሊዙ ኩባንያ ውስጥ መሥራታቸውን የጠቀሱት ጄኔራሉ፣ በዚያ ያካበቱትን ልምድ በመጠቀም በኢትዮጵያም ምርቱን ከማስተዋወቅ ጀምሮ ወደፊት ምርቱ እዚሁ ተቀነባብሮ ለገበያ የሚቀርብበት ሐሳብ እንዳለም ጠቅሰዋል፡፡ ድርድር ፈሳሽ የሆነውና የማጣበቅ ባህርይ ያለው የጎማ መከላከያ፣ በሰውም ሆነ በአካባቢ ላይ ምንም ጉዳት እንደማያደርስ፣ ከኬሚካል ነፃ እንደሆነ ለማስረዳትም በምላሳቸው በመቅመስ ለታዳሚው አሳይተዋል፡፡ ቴክኖሎጂውን በመኪና ጎማ ውስጥ ለመሙላት አሥር ደቂቃ ብቻ እንደሚጠይቅ፣ የሚሞላውም መኪናው ላይ በተገጠመ ጎማ ውስጥ ብቻ ሲሆን፣ አንድ ጊዜ የተሞላው መከላከያም እስከ ጎማው የአገልግሎት ዘመን ማብቂያ ድረስ እንደሚያገልግል ተነግሯል፡፡ ሳይበላሽ የሚቆይ መሆኑም ለየት እንደሚያደረገው ተገልጿል፡፡ እንደ አቶ ሳሚ ማብራሪያ ከሆነ፣ ለቤት አውቶሞቢሎች ለአራቱም ጎማዎች የሚሞላው መጠን አንድ ሊትር እንደሆነ ሲገመት፣ ለትልልቅ መኪኖች ሁለት ሊትር፣ ለትልልቅ የግንባታ መኪኖች እስከ አራት ሊትር እንዲሁም ግዙፍ ለሆኑ የመስክ ተሽከርካሪና ማሽነሪ ጎማዎች እስከ ስምንት ሊትር መጠቀም እንደሚመከር ተጠቅሷል፡፡ 

የኦሮሚያ ክልል አስተዳደር በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ መሥሪያ ቤቶቹ የሠራተኞች ትራንስፖርት አገልግሎት ለሚሰጡ አውቶቡሶቹ (በተለምዶ ቢጫዎቹ አውቶቡሶች ለሚባሉት) በሙሉ ቴክኖሎጂውን ለመጠቀም መስማማቱ ተጠቅሷል፡፡

 በየዓመቱ ወደ አገር ውስጥ የሚገባው የተሽከርካሪ መጠን የ30 በመቶ ጭማሪ እያሳየ እንደሚገኝ መረጃዎች ያሳያሉ ያሉት የኩባንያው ኃላፊዎች፣ ቴከሳይ የተባለ የምርምር ተቋም በየካቲት ወር ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት እ.ኤ.አ. ከ2022 ጀምሮ ኢትዮጵያ በየዓመቱ የ180 ሚሊዮን ዶላር የጎማ ግዥ እንደምትፈጽም መተንበዩን ጠቅሰዋል፡፡

በእንግሊዙ ኩባንያና በኢትዮጵያውያን የታየር ፕሮቴክተር ድርጅት መሥራቾች መካከል ከሦስት ዓመታት በፊት በተደረገ የፍራንቻይዝ ስምምነት መሠረት በሦስት ሚሊዮን ብር ካፒታል የተመሠረተው አገር በቀሉ ኩባንያ፣ በጎማ ጥገና የተሰማሩትን ጨምሮ ወደፊት ከ30 ሺሕ በላይ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ጄኔራል ባጫ ተናግረዋል፡፡

 

Standard (Image)

‹‹አንዳንድ የባንክ አሠራሮች ግልጽ ከሆነው ሕግ በማፈንገጥ በልማድ የዳበሩ ናቸው››

$
0
0

 

አቶ ገዙ አየለ መንግሥቱ፣ የሕግ ባለሙያ

አቶ ገዙ አየለ መንግሥቱ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሕግ ባለሙያነት በማገልገል ላይ ይገኛሉ፡፡ አቶ ገዙ በሕግ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን (LL.B) ከጅማ ዩኒቨርሲቲ እንዲሁም የሁለተኛ ዲግሪያቸውን በዚያው በሕግ ሙያ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል። በሥራ መስክም በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የሕግ ትምህርት ቤት፣ በሕግ መምህርነትና በተመራማሪነት ከአምስት ዓመታት በላይ አገልግለዋል። በዩኒቨርሲቲው ቆይታቸውም የተለያዩ የምርምር ሥራዎችን አበርክተዋል። አቶ ገዙ አየለ፣ ከዚህ ባሻገር በጎንደር ፋና ኤፍኤም እንዲሁም በወላይታ ሶዶ ፋና ኤፍኤም ሬዲዮ የሕግ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት በማኅበረሰቡ ውስጥ የሕግ ግንዛቤን በመፍጠር ረገድ የድርሻቸውን ተወጥተዋል። ከዚህ በፊትም በተለያዩ የኅትመት ውጤቶች ሕግ ነክ ጉዳዮችን በመተንተንና በመጻፍ የሚታወቁ የሕግ ባለሙያ ሲሆኑ፣ በውጭ አገር የመጻሕፍት አሳታሚ ድርጅት ታትሞና በአማዞን ድረ ገጽ እየተሸጠ የሚገኝ መጽሐፍም ለኅትመት አብቅተዋል። አቶ ገዙ አየለ በቅርቡ “የኢትዮጵያ የባንክና የሚተላለፉ የንግድ ሰነዶች ሕግ” በሚል ርዕስ አዲስ መጽሐፍ ለንባብ ያበቁ ሲሆን፣ የመጽሐፉን ሁለተኛ ኅትመት ለገበያ ለማቅረብ በዝግጅት ላይ ይገኛሉ። ሰለሞን ጎሹ በመጽሐፋቸውና በተያያዥ ጉዳዮች ላይ አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር፡- መጽሐፉ በቅርቡ የታተመ በመሆኑና የተጻፈውም የንግድ ሕጉን ለማሻሻል አገሪቱ በሒደት ላይ ባለበችበት ወቅት በመሆኑ፣ መጽሐፉን የሚያነቡ ሰዎች ምን አዳዲስ ነገሮችን ሊያገኙ ይችላሉ?

አቶ ገዙ አየለ፡- መጽሐፉን የማዘጋጀት ሥራ የጀመርኩት ከዛሬ አራት ዓመት በፊት በመሆኑ፣ በንባብና አዳዲስ ሐሳቦችን በማካተት በዘርፉ ካሉ ባለሙያዎች ጋር የሐሳብ ልውውጥ ለማድረግ ሰፊ ጊዜ ወስጃለሁ። ጊዜው በመርዘሙ በተለይም የንግድ ሕጉ አሁን በመሻሻል ሒደት ላይ ስለሚገኝ፣ ይህንን መጽሐፍ መጻፍ ከማሻሻያው አንፃር ሰፊ ክፍተት እንዳይኖር፣ በማሻሻያ መድረኩ ላይ በመሳተፍና በፖሊሲ ሰነዱ የውይይት መድረክ ላይ በመገኘት ሊደረጉ የታሰቡ የማሻሻያ ነጥቦች ላይ ሙሉ የዳሰሳና የማጣቀሻ ነጥቦችን አካትቻለሁ። ከዚህ በተጨማሪም ሕጉ ሊያካተታቸው የሚገቡ አዳዲስ ጉዳዮችን በሰፊው በማንሳት ሕግ አውጪውም ከግንዛቤ ቢያስገባቸው ይበጃሉ የሚሉ ነጥቦችን ያነሳሁ በመሆኑ፣ እንደ ግብዓት ሊጠቅም ይችላል። በመሆኑም በየመድረኩ ሊሻሻሉ ይችላሉ ተብለው የተነሱ ነጥቦችን ከማካተት ጀምሮ በማሻሻል ሒደቱ ላይ ተሳታፊ ከሆኑ ባለሙያዎችም የተለያዩ ሰነዶችን በመውሰድ ለመመልከት ሞክሬያለሁ። ከዚህ በተጨማሪም የንግድ ሕጉ የወጣው በ1952 ዓ.ም. ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት በዘርፉም ከፍተኛ የባንኮች መስፋፋት፣ የቴክኖሎጂ ዕድገት፣ የክፍያ ሰነዶች መለዋወጥ ጋር ተያይዞ በአገራችን ያሉ ነባራዊ ሁኔታዎችን በማገናዘብ በዘርፉ የተጻፉ መጻሕፍት ባለመኖራቸው አብዛኞቹ ጉዳዮች አዲስ ነገሮችን የሚያስተዋውቁ ይሆናሉ ብዬ አስባለሁ። በተለይም ደግሞ በየከፍተኛ የትምህርት ተቋማችን ያሉ ተማሪዎችም ሆኑ መምህራን የኢትዮጵያን የባንክና የሚተላለፉ የንግድ ሰነዶች ሕግን ለማስተማር የሚጠቀሙት የውጭ አገሮች መጻሕፍትን ማለትም እንደ ህንድ፣ አሜሪካ፣ ፈረንሣይና የሌሎች በውጭ ቋንቋዎች የተጻፉ የውጭ መጻሕፍትን ነው። እነዚህ ስለአገራችን ሕግ እንዲሁም በአገራችን በዚሁ ኢንዱስትሪ ላይ የሚነሱ ነጥቦች በቂ ዕውቀት የሚያስጨብጡ አይደሉም። በመሆኑም ይህ መጽሐፍ በከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን እንደ ማጣቀሻና ማስተማሪያነት የሚያገለግል ነው። መጽሐፉ ያካተታቸው ነጥቦች ከዚህ በፊት ያልተነኩ ግን ሊነሱ የሚገባቸው በርካታ አዳዲስ የሕግ ነጥቦችን በመሆኑ፣ የንግድ ሕጉ ማሻሻያም እንደ ግብዓት ሊጠቀምበት ይችላል የሚል እምነት አለኝ። አንባቢያንም በሕጋችን ሊካተቱ የታሰቡ አዳዲስ ነጥቦችን ከማግኘት በተጨማሪ ሰፊ የሕግ ትንታኔ የሚያስፈልጋቸውን ጉዳዮች፣ በተግባር የሚታዩ አሠራሮች ከነመፍትሔዎቻቸው ማግኘት የሚችሉበት፣ ስለዘርፉ የተጻፈ ፈር ቀዳጅ ሥራ ነው። በሌላ በኩል በባንኮች የሚጠቀሙ ደንበኞችም ሆኑ የንግድ ማኅበረሰብ አባላት፣ በተለይ የባንክ ሠራተኞች በሙሉ ስለባንክ ሕግ፣ በጠቅላላውም ሕጉ የሚለውንና ወደፊት ሕጉ ምን ሊያካትት ይገባዋል የሚሉ ነጥቦችን እንደ አዲስ ግንዛቤ ሊያገኙበት የሚችሉበት መጽሐፍ ነው ብዬ አምናለሁ።

ሪፖርተር፡-መጽሐፉን በመጻፍ ሒደት ውስጥ ያጋጠመዎት መሠረታዊ ችግር ምን ነበር?

አቶ ገዙ አየለ፡-መጽሐፍ መጻፍ በራሱ እጅግ በጣም አድካሚ ሥራ ነው። በተለይም ለመጽሐፉ የሚሆኑ ማጣቀሻዎችን፣ የተለያዩ ጽሑፎችን፣ የፍርድ ቤት ውሳኔዎችን በመፈለግ ከእነዚህ ውስጥ ደግሞ አንብቦ ጠቃሚ የሆኑት መለየት በእውነቱ እጅግ አድካሚ ሥራ ነው። መጽሐፉን ለመጻፍ በአገራችን ስለባንክ አሠራር የተጻፉ በቂ መጻሕፍት የሉም። እኔ ለመጻፍ ስነሳም በባንክ ዘርፍ ያሉ ሕጎች ላይ እንደማጣቀሻ የሚውል ደረጃውን የጠበቀ መጽሐፍ ለመጻፍ በመሆኑ፣ ለማንኛውም የሕግ ሰውም ሆነ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንደ ማጣቀሻነት እንዲያገለግል በማሰብ ማጣቀሻዎችን ለማንበብ ብዙ ጊዜ ወስጃለሁ። ሌላው ግን መጽሐፉን ለማሳተም ኅትመቱን የሚያግዝ ተቋም ወይም ባንክ መፈለጉም በጣም አድካሚ ነበር። በአገሪቱ ቁጥራቸው በርከት ያሉ ባንኮች ቢኖሩና መጽሐፉም የባንኮቹን የየዕለት እንቅስቃሴ የሚያግዝ፣ ለሠራተኞቻቸውም ዕውቀትን የሚያስገበይ እንደሚሆን እርግጥ ነው። ይሁንና አንዳንድ ጊዜ ባንኮቹ ሠራተኞቻቸው ሀብቶቻቸው በመሆናቸው፣ ሠራተኞቻቸውን ለማሠልጠን ትኩረት እንደሚሰጡ እየገለጹልህ፣ በባንክ ዘርፍ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሠራተኛ እንደተሰማራ እየታወቀ እንኳ ይህንን መጽሐፍ ለማሳተም የሄድኩበትን ርቀት ሳስበው በጣም አድካሚ ነበር። በመጨረሻ ከእነዚሁ ተቋማት ውስጥ የመጽሐፉን ኅትመት አቢሲኒያ ባንክ ስፖንሰር በማድረጉ ለመታተም በቅቶ የመጀመርያው ዕትም እያለቀ ስለሆነ፣ የተሰጠኝ ማበረታቻም የገጠሙኝን ችግሮች እንዳልቆጥራቸው አድርጎኛል።

ሪፖርተር፡- የሚተላለፉ የንግድ ሰነዶችን ማለትም እንደ ቼክ፣ የሐዋላ ወረቀት፣ የተስፋ ሰነድ ሌሎችም እንደ ሲፒኦ ያሉ ሰነዶች ያላቸው የሕግ ሽፋን በመጽሐፉ ተካቷል። ይሁንና ቼክ በሰፊው በንግዱ ማኅበረሰብ ዘንድ አገልግሎት ላይ የሚውል ሰነድ ከመሆኑ አንፃር ከቼክ ጋር ግንኙነት ላላቸው የሕግ ጉዳዮች በፍርድ ቤት ክርክሮችን ያስነሳሉ። እነዚህን ስፋት ያላቸውን ከቼክ ጋር የተያያዙ ጉዳዮች በተመለከተ የእርስዎ አጠቃላይ ግምገማ ምንድን ነው?

አቶ ገዙ አየለ፡-ቼክ በሰፊው ሥራ ላይ የዋለ በመሆኑ፣ የመጽሐፉ ሰፊ ክፍልም ከቼክ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ይሸፍናል። በተግባር ቼክ እንደ ዋስትና ሰነድ፣ ለዋስትና የሚጻፍባቸው ሁኔታዎች እጅግ በርካታ እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ በመሠረቱ ቼክ እንደቀረበ የሚከፈል የገንዘብ ሰነድ ነው፡፡ የሌሎች አገሮች ተሞክሮም ቼክ በዋስትና የሚሰጥ የዋስትና ሰነድ ሳይሆን፣ እንደቀረበ የሚከፈል ሰነድ መሆኑን የሚያመላክት ነው። ቼክን በዋስትና ሰነድነት መስጠት መለመዱ በሕጋችን ሰፊ ሽፋን የተሰጣቸውንና ለዚሁ ተግባር የሚውሉትን የሐዋላ ወረቀትና የተስፋ ሰነድ አገልግሎቶችን አቀጭጯል ብዬ አስባለሁ። ለዚህ ዋነኛ ማሳያው እነዚህ ሰነዶች የቼክን ያህል ቀርቶ በትንሹም እንኳ እንደሚገባቸው ያልተዋወቁ፣ በሰፊው አገልግሎት ላይ  የማይውሉ መሆናቸው ነው። ሌላው የክፍያ ጊዜው ወደፊት ተደርጎ የሚጻፍ ቼክን ወይም Postdated Cheque የተመለከቱ ጉዳዮች ላይም ጥያቄዎች ይነሳሉ። በመሠረቱ በሕጋችን ውስጥ ወደፊት ተከፋይ የሚሆን ቼክ መፈቀድና አለመፈቀዱን በተመለከተ የንግድ ሕጉ አንቀጽ 855 እና ሌሎችም አንቀጾች በመጥቀስ በሕግ ባለሙያዎች መካከል ክርክሮች ይነሳሉ። እኔ በበኩሌ ሕጉ ወደፊት ተከፋይ እንዲሆን ተደርጎ የሚጻፍን ቼክ ፈቅዷል የሚል ድምዳሜ የሚያደርስ የሕግ አንቀጽ አላገኘሁም። በአጠቃላይ ሲታይም ቼክ እንደቀረበ የሚከፈል ሰነድ መሆኑን ሕጉ አስቀምጦ ሳለ፣ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ እንዲከፈል ብሎ በዚሁ ሕግ ውስጥ ሊፈቅድ የሚችልበት አግባብ አይኖርም። ይህ ከተደረገም ከላይ እንደገለጽኩት ቼክን እንደ ዋስትና ሰነድ ተገለገልንበት ማለት ነው፡፡ በመሆኑም ቼክ እንደቀረበ የሚከፈል የገንዘብ ሰነድ መሆኑ ቀረ ማለት ነው። በተግባር ይህ ሁኔታ ለብዙ ክርክሮች መነሻ ሆኖ እናየዋለን። አንዳንድ ጊዜም ቼኩ የተጻፈው ወደፊት ተደርጎ በመሆኑ፣ ቼኩ ተጻፈ ከተባለበት ቀን በፊት ቼኩን የጻፈው ግለሰብ ሊሞት ይችላል፡፡ በዚህም ቼኩን ጽፏል የተባለው ግለሰብ፣ ቼኩ በተጻፈበት ወቅት በሕይወት ስላልነበር፣ የተጭበረበረ ቼክ ነው በማለት የሚቀርቡ ክርክሮች የተለመዱ ናቸው። በሌሎች አገሮች ሁኔታም ብታይ ወደፊት ተከፋይ የሚሆን ቼክ በግልጽ የተከለከለ ከመሆኑም በላይ ይህን ዓይነት ቼክ የሚጽፍ ሰው፣ ቼኩ በቀረበ ጊዜ እንደሚከፈልበት አውቆ መጻፍ አለበት የሚል አቋም የሚያንፀበርቅ የሕግ ድንጋጌ እስከ ማስቀመጥ ደርሰዋል። ይህ ሁኔታ የሚያመለክተው ለወደፊቱ የንግድ ሕጉ በዚህ ረገድ ጥርት ያለ አቋም መያዝ እንዳለበት ነው። በአጠቃላይም በተለይ ከቼክ ጋር በተያያዘ የሚደረጉ ግብይቶች የንግድ ሕጋችን አሁን ባለበት እንኳን ካስቀመጠው በተቃራኒውና በልማድ በዳበሩ በርካታ ተግባራት እየተመራ መሆኑንና ይህ ተግባርም መቀጠል እንደሌለበት ታውቆ የሕግ ማዕቀፉ ሊከበርና ሊሠራበት እንደሚገባ አመላካች ሆኖ አግኝቸዋለሁ። የሕግ ማዕቀፍ የሚያስፈልጋቸው በርካታ ጉዳዮች እንዳሉም ለመረዳት ችያለሁ።

ሪፖርተር፡- ከዚሁ ጋር በተያያዘ በመጽሐፍዎ ትኩረት የተሰጠው የደረቅ ቼክ ጉዳይ ነው፡፡ የሕጉ ድንጋጌዎች ምን ያህል ከተግባሩ ጋር የተጣጣሙ ናቸው?

አቶ ገዙ አየለ፡- ደረቅ ቼክ፣ የቼክን ተዓማኒነትና የንግድ እንቅስቃሴን የሚጎዳ ሕገወጥ ተግባር ነው። ለደረቅ ቼክ ዋነኛ ምክንያቶች አንዳንድ ጊዜ በአውጪውና በተከፋዩ መካከል የሚደረጉና ቼክን በዋስትናነት ለመስጠት የሚገፋፉ የውስጥ ስምምነቶች ናቸው። በንግድ ሕጉ መሠረት አንድ ሰው ቼክ ሲጽፍ በሒሳቡ ውስጥ ሊያዝበት የሚችለው በቂ ስንቅ (ሒሳብ) መኖሩን አውቆ መሆን አለበት ይላል። ይህም ቼኩ በሚጻፍበት ጊዜና የቼኩ የመክፈያ ጊዜ እስከሚያልቅ ድረስ ባለው ስድስት ወር ጊዜ ውስጥ በሒሳቡ ውስጥ በተጻፈው ቼክ ልክ ገንዘብ መኖር ይጠበቅበታል። ይህ ካልሆነ ግን ቼኩ ለክፍያ ሲቀርብ ሒሳብ ወይም ገንዘብ የሌለው ከሆነ እንደ ደረቅ ቼክ ተቆጥሮ የወንጀል ተጠያቂነትን ጨምሮ፣ የፍትሐ ብሔር ኃላፊነትንና በብሔራዊ ባንክ የሚወሰድን አስተዳደራዊ ዕርምጃን እንደሚያስከትል ከብሔራዊ ባንክ መመርያዎች አንፃርም ተብራርቷል። ይሁንና ሕጉ ደረቅ ቼክን በተመለከተ አንዳንድ ጊዜ ሰዎች ደረቅ ቼክን በመጻፍ በተለያዩ መንገዶችና ምክንያቶች የክፍያ ይቁም ትዕዛዝ በመስጠት ወይም ቼኩ ከመጀመሪያውንም ማሟላት የሚገባውን በሕጉ የተቀመጡትን መስፈርቶች ሆነ ብሎ በማጓደል የተጻፈው ቼክ፣ በደረቅ ቼክነት እንዳይመታ የሚደረጉባቸው ሁኔታዎች አሉ። እነዚህ ነጥቦች በተለይም ብሔራዊ ባንክ በየጊዜው በሚያወጣቸው መመርያዎች ውስጥ በግልጽ እየተደነገጉ በመምጣታቸው፣ በዚህ ረገድ ደረቅ ቼክን ለመግታት ግልጽ ሕጎች አሉ ማለት እንችላለን።

ሪፖርተር፡- የሕጉ ማዕቀፍ እንደዚህ ግልጽ ከሆነ፣ ሕጉ በተደጋጋሚ ሲጣስ የሚታየው ለምድን ነው? የቼክ የክፍያ እንዲቆም በተደጋጋሚ ጥያቄ የሚቀርበውስ ለምንድን ነው?

አቶ ገዙ አየለ፡- ቼክ ሕጉ የሚፈልገውን መጠይቆች አሟልቶ ለከፋዩ ባንክ ክፍያ እንዲፈጸም ከቀረበ በኋላ፣ ከፋዩ ባንክ ለአምጪው ክፍያ አልፈጽምም ሊል ከሚችልባቸው ምክንያቶች ውስጥ አንዱ የቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝ በአውጪው ለባንኩ የተሰጠ እንደሆነ ነው። በንግድ ሕጋችን አንቀጽ 857 በእንግሊዝኛው ቅጂ እንደተመለከተውም በአውጪው የሚሰጥ የክፍያ ይቁም ትዕዛዝ የቼኩ ከፋይ ባንክ ክፍያ አልፈጽምም ለማለት በቂ ምክንያት ነው እንደሆነ ያስቀምጣል። በተመሳሳይ መልኩ የአማርኛው የንግድ ሕግ አንቀጽ 857 ቅጂ ቼኩ ከመከፈሉ በፊት አውጪው እንዳትከፍል ብሎ የነገረው እንደሆነ፣ ባንኩ የቼኩን ዋጋ አልከፍልም ለማለት ይችላል ይላል። እነዚህ የንግድ ሕጉ ድንጋጌዎች አንደኛ በጣም ጥቅል ሐሳብ የያዙ በመሆናቸው የቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝን የሚያስፈጽሙት ባንኮች በምን በምን ምክንያት ክፍያ ይቁም ትዕዛዝን ተቀብለው ማስፈጸም እንዳለባቸው ባለመግለጹ፣ ለቼክ ተገልጋዮችም ሆነ ለባንኮች አሉታዊ ተፅዕኖ የሚፈጥር ይሆናል። ሁለተኛውና ዋናው ችግር አንቀፁ የቼክ ከፋይ ባንኮች የቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝን እንደ ግዴታ መፈጸም እንዳለባቸው ሳይሆን፣ አልከፍልም ለማለት ይችላሉና በቂ ምክንያት ነው በሚሉ የላሉ ቃላቶች በማስቀመጡ ባንኮችም ቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝን መቀበልና ያለመቀበል መብት ያላቸውና በባንኮች በጎ ፈቃድ (ሥልጣን) ላይ የተመሠረተ እንደሆነ የሚያሳብቅ የሕግ አንቀጽ ነው። በቅርቡ የወጣው የብሔራዊ ባንክ መመርያ፣ መመርያ ቁጥር SBB/61/2016 ግን በአንቀጽ 6 የቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝን የተመለከቱ አንቀጾችን አስቀምጧል። መመርያው በአንቀጽ 6 እንዳስቀመጠው ከሆነ፣ ቼኩን የጻፈው አውጪው አካል የቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝ ቢደርሰው እንኳ፣ የቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዙ ለከፋዩ ባንክ የተሰጠው በዚሁ መመርያ አንቀጽ 5 ላይ የተቀመጠውንና በቂ ስንቅ ሳይኖር ቼክ መጻፍ የሚያስከትለውን አስተዳደራዊ ኃላፊነት ወይም የወንጀል ተጠያቂነት ለማምለጥ በማሰብ ከሆነ ላይቀበለው ይችላል ይላል። በነገራችን ላይ ይህ ጉዳይ በሌሎች አገሮችም ያለ ነው። ሌላው የቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝን ከወንጀል ተጠያቂነት ለማምለጥ ሲባል መስጠት የተከለከለ ተግባር መሆኑ ነው። ይሁንና ግን በአንዳንድ አጋጣሚዎች በቼክ የተገበያዩ ግለሰቦች በራሳቸው በሚፈጥሩት አለመግባባት ምክንያት ወይም ቼኩ የተቆረጠው በወቅቱ በሒሳቡ ውስጥ በቂ ስንቅ ሳይኖር በሚሆንበት ሁኔታ፣ የቼክ ክፍያ ይቁም ተግባር ሲፈጸም ማየት የተለመደ ተግባር ነው። ይሁንና አሁን ቼክ ክፍያ ይቁም ትዕዛዝ መስጠት የሚቻለው ቼኩ ጠፍቶብኛል ወይም ተሰርቄያለሁ በሚሉ ደንበኞች ብቻ መሆን እንዳለበት ብሔራዊ ባንክ መመርያ በማውጣቱ የቼክ ክፍያ ይቁም ተግባር እንደሚቀንስ እሙን ነው።

ሪፖርተር፡- በመጽሐፍዎ በአንዳንድ ባንኮች አሠራር ሒደት ውስጥ ልማዳዊ አሠራሮች እንደሚዘወተሩ ጠቅሰዋል።  እነዚህ አሠራሮች ግልጽ የሕግ ድንጋጌ ባለበት አግባብ የተለመዱ ናቸው ወይስ የባንኩ አሠራር የሕግ ክፍተቶችን ለመሸፈን የተጠቀማቸው ናቸው?

አቶ ገዙ አየለ፡- በጣም የሚገርምህ እነዚህ ጉዳዮች ናቸው መጽሐፉን ለመጻፍ ዋነኛ አነሳሽ ምክንያቶች የሆኑኝ። አንዳንዶቹ ልማዳዊ አሠራሮች ግልጽ ከሆነው ሕግ በማፈንገጥ የዳበሩ ናቸው። በዚህ ረገድ ለምሳሌ ቼክን በከፊል መክፈል በሕጉ የተፈቀደ ተግባር ሆኖ ሳለ፣ በአሠራር ግን ቼክ በከፊል የሚከፈልባቸው አጋጣሚዎች ጠባብ ወይም የሉም ለማለት የሚጋብዙ ናቸው። ቼክን ለክፍያ ማረጋገጥ የሚባል አሠራርም አላቸው፡፡ ቼኩ ከተጻፈና ለክፍያ ለባንኮቹ ሲቀርብ ባንኮቹ ቼኩን አውጪው ስለመጻፉ በስልክ የማረጋገጥ ተግባር ይሠራሉ። ይህ ሙሉ ለሙሉ ከቼክ ካለምንም ቅድመ ሁኔታ እንደቀረበ የሚከፈል መሆኑን የሚያስቀር ነው። እነዚህና ሌሎችም ብዛት ያላቸው ጉዳዮች ግልጽ የሕግ ድንጋጌዎችን በማፈንገጥ የባንኩ ዘርፍ ያዳበራቸው አሠራሮች በመሆናቸው፣ ሕጉን ሊከተሉ የሚገባቸው ናቸው። ሌላው ሕጉ ሳይኖር የዳበሩ በርካታ ልማዳዊ የባንክ አሠራሮችና የሕጉን ክፍተት ሞልተዋል የምንላቸው ጉዳዮችም አሉ፡፡ ለምሳሌ ከሐዋላ የገንዘብ ዝውውር ጋር በተገናኘ፣ የፊርማ ጉዳይን የተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ፍርድ ቤቶችም የባንኮችን ልማዳዊ አሠራሮች በመመርኮዝ ውሳኔ የሚሰጡበት አግባብ እንደ ሕግ የሚቆጠሩበትን አሠራሮች ስለፈጠሩ፣ እነዚህን ጉዳዮች የሚሸፍን የሕግ ማሻሻያ እስከሚወጣ ድረስ ጠቀሜታቸው የጎላ ነው።

ሪፖርተር፡- ከባንክ አገልግሎት ጋር በተያያዘ በተለይ ከወጪ ንግድ መስፋፋት አኳያ እንዲሁም ባንኮች ከሚያቀርቧቸው ብድሮች አንፃር የወጪ ንግድን የሚመለከቱ የሕግ ክፍተቶች አሉ። በዚህም በሰነድ ብድር የመስጠት አገልግሎት ወይም ሌተር ኦፍ ክሬዲት የመሳሰሉትን በሚመለከት የንግድ ሕጉ ሊሸፍናቸው የሚገቡ ነጥቦች የትኞቹ ናቸው?

አቶ ገዙ አየለ፡-የንግድ ሕጋችን ከወጣ ረዥም ጊዜ በማስቆጠሩ፣ ሕጉ በሰነድ ብድር የመስጠት አገልግሎትን በተመለከተ ያስቀመጣቸው ድንጋጌዎች የሕጉን ተራማጅነት የሚያመላክቱ ናቸው። ይሁንና ግን ከዓለም አቀፍ የንግድ መስፋፋት፣ የወጪና የገቢ ንግድ አገልግሎቶችም በዚያው መጠኝ ከመስፋፋታቸው አኳያ፣ በአሁኑ ወቅት የሚነሱ አለመግባባቶችን የሚፈቱ ድንጋጌዎች በሕጉ ውስጥ በበቂ ሁኔታ አልተካተቱም። ከዚሁ አገልግሎት በመነሳት የንግድ ግንኙነቶቹ የሚከናወኑት በባንኮች አማካይነት በመሆኑ፣ ባንኮቹ የብድር ሰነዶቹን ገዥና ሻጭ ወገንን በመወከል የሚሰጡ እንዲሁም ገዥና ሻጭን የሚያማክሩ ጭምር ናቸው። በተጨማሪም በዕቃዎቹ የግብይት ሒደት የሚፈጠሩ ጉዳዮችንም እስከ መከታተልና ለደንበኞቻቸውም ስለግብይቱ ምክር እስከ መለገስ የሚደርስ ኃላፊነት አለባቸው። ከዚህ አንፃር በንግድ ሕጋችን አንቀጽ 959 እና ተከታዮቹ ድንጋጌዎች ውስጥ የተመለከቱ ሐሳቦች፣ አንድ ባንክ አማካሪ ባንክ የሚባለው መቼ ነው? አረጋጋጭ ባንክ ምንድን ነው? የአማካሪም ሆነ የአረጋጋጭ ባንኩ ኃላፊነቶችና ግዴታዎች በግብይት ሒደቱ ምን መምሰል አለበት? የሚሉና ሌሎችም ጉዳዮች በግልጽና በስፋት አልተቀመጡም፡፡ ይህ በመሆኑም በተለይም የሌተር ኦፍ ክሬዲት አገልግሎትን በተመለከተ የሚያጋጥሙ ክርክሮችን በዓለም አቀፍ ደረጃ አስገዳጅነት በሌላቸውና ለርካታ አገሮች ሕጎች እንደ መነሻ በሚያገለግሉ ዓለም አቀፍ ሕጎች ማለትም እንደ UCP600 ባሉ ሕጎች ላይ በመመሥረት ክርክሮች ሲቀርቡ ይስተዋላል። በመሆኑም ይህ የሕጉ ክፍል እየሰፋ ከመጣው የሰነዶቹ ተጠቃሚ አንፃር ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባና በጥልቀት ከሌሎች አገሮች የሕግ ተሞክሮ፣ ከፍርድ ቤት ክርክሮች እንዲሁም ከባንኮቹ አሠራር አንፃር ታይቶ በአጥጋቢ መንገድ መሻሻል አለበት።

ሪፖርተር፡- ከባንኮች ብድር አኳያ የዋስትና ሰነዶችን ወይም Letters of Guarantees በተመለከተም የሚነሱ ክርክሮች አፈጻጸም ላይ ብዥታዎች አሉ። ስለዚህ ጉዳይ የእርስዎ አቋም ምንድን ነው?

አቶ ገዙ አየለ፡- የዋስትና ሰነዶች በአሁኑ ወቅት በጣም ሰፊ አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው። የዋስትና ሰነዶችን የተመለከቱ እስከ ሰበር ሰሚ ችሎት ድረስ ደርሰው ውሳኔ የተሰጠባቸው ጉዳዮች አሉ። በመጽሐፉ እንዳስቀመጥኩትም የሰበር ውሳኔዎቹ የዋስትና ሰነዶችን በፍትሐ ብሔር ሕጋችን ውስጥ ከአንቀጽ 1920 ጀምሮ ስለሰው ዋስትና የተቀመጡትን ድንጋጌዎች በማንሳት የዋስትና ሰነዶችን ከሰው ዋስትና ጋር ለማመሳሰል የተከረበት አግባብ፣ በሰነዶች ዋስትናን የሚሸፍን ሕግ በግልጽ እንደሚያስፈልገን አመላካች ናቸው። ሁለቱም ጉዳዮች በመሠረታዊነት የተለያዩ ናቸው፡፡ አንደኛ በባህሪያቸው የሰው ዋስትና ካለምንም ክፍያ የሚሰጥ ሲሆን፣ የዋስትና ሰነዶችን የሚሰጡ ባንኮች ግን ተመጣጣኝ ክፍያ በኮሚሽን መልክ ይቀበላሉ። ሌላው የሰው ዋስትና በሕጋችን በግልጽ ሽፋን የተሰጠው የዋስትና ዓይነት ሲሆን፣ የዋስትና ሰነዶችን የሚመለከቱ ሕጎች በዓለም አቀፍ ደረጃ መውጣት የጀመሩት እ.ኤ.አ. ከ1992 እስከ 2010 ባሉት ጊዜያት መሆኑን ስንመለከትም፣ ሰነዶቹን የሰውን ዋስትና ከሚገዛውና በ1952 ዓ.ም. ቀደም ብሎ ከወጣው ሕግ እኩል ይጓዛሉ ማለት መሠረታዊ ስህተት እንደሆነ እንረዳለን። በመሆኑም በአብዛኞቹ ሰነዶች ከጽሑፍ ጀምሮ ይዘታቸው ልማዳዊ አሠራርን መሠረት ያደረገ እንጂ በግልጽ የሰፈረ የሕግ አግባብ አለው ለማለት አያስደፍርም፡፡ ፍርድ ቤቶቹም ሆኑ ባንኮቹ የዋስትና ሰነዶችን በተለመከተ የሚከተሉት አሠራርና የሰው ዋስትናን የሚመለከቱ ድንጋጌዎች ለሰነዶች ዋስትናነት እንደሚያገለግሉ አድርጎ መውሰዱም በመሠረታዊነት ከላይ ካነሳኋቸውና ከሌሎችም ምክንያቶች አአኳያ ለእኔ የሚያሳምነኝ ጉዳይ ባለመሆኑ፣ ከዚሁ የተለየ አቋም እንዳለ አንስቻለሁ።

ሪፖርተር፡- ብድር መስጠት የባንኮች ዋነኛ ሥራ እንደመሆኑ መጠን በተበዳሪዎችና በባንኮች መካከል ያለው ግንኙነት በሕጉ በበቂ ሁኔታ ተደንግጓል የሚል አቋም አለዎት?

አቶ ገዙ አየለ፡- ብድር ጥንትም ባንኮች ሲመሠረቱ ጀምሮ ዋነኛ የሥራ ድርሻ ሆኖ የቀጠለ ተግባር ነው። በመሆኑም በሕግ በግልጽ ተቀምጠው የማናገኛቸው ነገር ግን ብድር ለመውሰድ አስፈላጊ የሆኑ ቅድመ ሁኔታዎች አሉ፡፡ ብድር ከተወሰደ በኋላም ቢሆን በአበዳሪው ባንክና በተበዳሪ ግለሰቦች ወይም ተቋማት መካከል የመያዣና የብድር ውልን መሠረት አድርገው የሚነሱ ጉዳዮች አሉ። ከዚህ አንፃር ብድርን በተመለከተ የብድር አገልግሎቶች እየሰፉ ከመምጣታቸውም አንፃር ለምሳሌ እንደ የዋስትና ሰነድ ብድሮች ያሉት በሕጉ ውስጥ በግልጽ መካተት ይኖርባቸዋል። ሌላው ብድር ለመስጠት ሕጉ እንዲሟሉ የሚፈልጋቸው ቅድመ ሁኔታዎችም ቢሆኑ፣ በግልጽ ቢደነገጉ እንኳ እዚህም እዚያም በሕጉ የተጠቀሱትን ነጥቦች በአንድ ማድረጉም ሌላው ጉዳይ ነው። የብድር ግንኙነቱን የሚገዙ ውሎችም ለአንድ ወገን ያደሉ እንዳይሆኑ ገዥ ሕጎች ቢኖሩ የሚሻል ይመስለኛል። ሌላው የብድር ዓይነቶችን ለምሳሌ የንግድ ተቋም አስይዞ መበደርን በተመለከተ በቂ የሕግ ሽፋን ተሰጥቷቸው በስፋት አገልግሎት ላይ ያለመዋል ሁኔታዎች አሉ። በመሆኑም እነዚህንና ሌሎች ጉዳዮችን በበቂ ሁኔታ አጣጥሞ ማስኬድ በጣም አስፈላጊ ነው።

ሪፖርተር፡- የባንክ አገልግሎት ለሁሉም ተደራሽ እንዲሆን ከማድረግ አኳያ በተለይ የአካል ጉዳተኞችን ተጠቃሚነት በተመለከተ በሕጉ ቢካተቱ ብለው ያነሷቸውና አሁን ግን ተፈጻሚነት ሊኖራቸው አይገባም ብለው የጠቀሷቸው በርካታ ነጥቦች አሉ። ባንኮችን ለአካል ጉዳተኞች ተደራሽ ሲባል ለማድረግ ለውጥ ሊደረግባቸው የሚገቡ መሠረታዊ ጉዳዮች ምንድን ናቸው?

አቶ ገዙ አየለ፡- አሁን ዓለም የደረሰበት የአስተሳሰብና የዕድገት ደረጃ በራሱ የሰዎች የሰብዓዊና ተፈጥሯዊ መብቶች የሚከበሩበትና እንዲከበሩም በስፋት እንቅስቃሴ የሚደረግበት ዘመን ነው። ከአካል ጉዳተኞች የባንክ አገልግሎትና ተጠቃሚነት አኳያ የሚነሱ ነጥቦች መሠረታዊ የሰብዓዊ መብት ጥያቄዎችን እንደያዙ አምናለሁ። ስለሆነም አንድ ባንክ አገልግሎቱን ለአካል ጉዳተኞች ተደራሽ ማድረግ አለበት ሲባል ዝም ብሎ ባንኩ ለንግድ እንቅስቃሴው ስለሚያስፈልገው ብቻም ሳይሆን፣ የእነዚህን የኅብረተሰብ ክፍሎች መብት ማክበር ስላለባቸውም ጭምር ነው። አሁን ባሉት የንግድ ሕጋችን እንዲሁም የፍትሐ ብሔር ሕጋችን ድንጋጌዎች ላይ ማየት የተሳናቸው ሰዎች ፊርማ የራሳቸው ስለመሆኑ በውል አዋዋይ ፊት ቀርቦ ካልተረጋገጠ ድረስ በሕግ ፊት የሚጸና ውል መዋዋል እንደማይችሉ ተደንግጎ እናገኘዋለን። በተለይ መጻፍ የማይችሉ ወይም ሕጉ ባስቀመጠው ድንጋጌ ፈርማ ለመፈረም እጅ ወይም እግር ወይም ሁለቱም የሌላቸው የካል ጉዳተኞች ሲያጋጥሙ፣ የገንዘብ ወጪና ገቢ እንቅስቃሴዎችን ለማከናወን አዳጋቸ ይሆንባቸዋል። ዘመኑ ያመጣቸውን የኤሌክትሮኒክስ የባንክ አገልግሎቶች ማለትም የኤቲኤምና ሌሎች የካርድ አገልግሎቶችም በሕግ ዕውቅና ተሰጥቷቸው እነዚህ የኅብረተሰብ ክፍሎች እንዲጠቀሙባቸው አልተደረጉም። ቼክ ጽፎ መሰጠትን በተመለከተ መፈረም የማይችሉ ሰዎች አገልግሎቱን ማግኘት የሚያስችላቸው የሕግ ድንጋጌ ባለመኖሩ፣ ይህንን አገልግሎት ከማግኘት ተገድበዋል። እነዚህ ሁሉ የሕግ ድንጋጌዎችና የልምድ አሠራሮች ቢኖሩም ኢትዮጵያ በዓለም አስገዳጅነት ያለውን የአካል ጉዳተኞች መብት ኮንቨንሽን እ.ኤ.አ. ጁላይ 7 ቀን 2010 አጽድቃለች፡፡ በመሆኑም የዚህ ኮንቬንሽን ድንጋጌ የአካል ጉዳተኞች የእኩልነት መብትን በተለይ የራሳቸውን የገንዘብ እንቅስቃሴ በራሳቸው የመጠቀምና የመቆጣጠር መብትን በግልጽ ደንግጓል። ከዚህ አንፃር የንግድ ሕጉ ሲወጣ አካል ጉዳተኞችን ለመከላከል በማሰብ የተቀመጡት ድንጋጌዎቸ መሠረታዊ የእኩልነት መብትን የሚጋፉ ስለሆኑ፣ አካል ጉዳተኞችም ቢሆኑ በጥቂቱ እንኳ ሒሳብ ለመክፈት ደጋፊም ሆነ ሌላ ምስክር ሳያስፈልጋቸው ራሳቸው በፈለጉትና በመረጡት መንገድ ሁሉንም የባንክ አገልግሎቶችና እንቅስቃሴዎች ከሌላው ማኅበረሰብ እኩል የማግኘት መብት አለባቸው። ለዚህም መሠረታዊ የሕግ ማሻሻያዎች ከዓለም አቀፍ ሕጎች አንጻር እየታዩ መደረግ አለባቸው።

Standard (Image)

የድርቅ ተረጂዎች ቁጥር ወደ 8.5 ሚሊዮን አደገ

$
0
0

 

በ2009 ዓ.ም. በበልግ አብቃይና አርብቶ አደር አካባቢዎች በተደረገ የምግብ ዋስትና የዳሰሳ ጥናት ለመጪዎቹ አምስት ወራት 8.5 ሚሊዮን ሕዝብ ድጋፍ እንደሚያስፈልገው ተገለጸ፡፡

የብሔራዊ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን በበልግ አብቃይና አርብቶ አደር አካባቢዎች የምግብ ዋስትና ጥናት ማድረጉን ለሪፖርተር በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ይኸው ጥናት በሰብል አብቃይና በአርብቶ አደር አካባቢዎች ከግንቦት 15 እስከ ሰኔ 15 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ መካሄዱም ተጠቅሷል፡፡

በጥናቱ የወቅቱ የዝናብ ሁኔታ፣ የእርሻ ሥራ እንቅስቃሴ፣ በማሳ ላይ ያለው የሰብል ሁኔታ፣ የምርት ግምት፣ ግጦሽና የውኃ አቅርቦት፣ የእንስሳት አቋምና የምርት ሁኔታ፣ የሰውና የእንስሳት ጤና እንዲሁም በወቅቱ እየተሠራጨ ያለው የምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ ዕርዳታዎች የሥርጭት ሁኔታ በመዳሰስ የማኅበረሰቡን የምግብ ዋስትና ሁኔታ ለመገምገም የተቻለ ሲሆን፣ በተገኘው ውጤት ቀደም ሲል 7.8 ሚሊዮን ከነበረው የተረጂ ቁጥር ወደ 8.5 ሚሊዮን ከፍ በማለት ለቀጣይ አምስት ወራት ማለትም ከነሐሴ 2009 ዓ.ም. እስከ ታኅሳስ 2010 ዓ.ም. የምግብ ዕርዳታ የሚያስፈልገው መሆኑ ተረጋግጧል፡፡

የዳሰሳ ጥናቱ ሰብል አብቃይና አርብቶ አደር በሆኑ አካባቢዎች የተከናወነ ሲሆን፣ በዘንድሮው ዓመት የተረጂዎች ቁጥር የጨመረባቸው ምክንያቶች የበልግ ዝናብ መዛባት፣ የመኖና ግጦሽ ማነስ እንዲሁም በአንዳንድ አካባቢዎችም የምርት መቀነስና የውኃ እጥረት መሆናቸው በጥናቱ ላይ ተመልክቷል፡፡

በጥናቱ በብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስተባባሪነት የፌዴራል ሚኒስትር መሥሪያ ቤቶች፣ የክልል የዘርፍ ቢሮዎች፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት፣ የሁለትዮሽ ስምምነት ያላቸውና ዓለም አቀፍ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች መሳተፋቸውን ኮሚሽኑ ጠቅሷል፡፡

 

Standard (Image)

ከ14 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው 43 የአቫንዛ ሜትር ታክሲዎች ሥራ ጀምሩ

$
0
0

የአዲስ አበባ ከተማ ቱሪስት ታክሲዎች በዘመናዊ ተሽከርካሪዎች ለመተካት እንዲያስችል መንግሥት ከታክስ ነፃ እንዲገቡ በመፍቀዱ ምክንያት 43 ዘመናዊ አቫንዛ ሜትር ታክሲዎች ወደ ሥራ ገቡ፡፡

በ2008 ዓ.ም. ከተመዘገቡት 26 የታክሲ ማኅበራት ውስጥ አንዱ የሆነው የኮንፎርት ሜትር ታክሲ ማኅበር አንዱ ሲሆን፣ 14,882,321 ብር ወጪ አቫንዛ ሞዴል ቶዮታ ታክሲዎቹን ሐምሌ 23 ቀን 2009 ዓ.ም. ተረክቦ ሰኞ ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ወደ ሥራ አስገብቷል፡፡

ታክሲዎቹን ለመረከብ ስድስት ወራት የፈጀበት ማኅበሩ፣ ቀደም ብሎ ላዳ ላርገስ ከተባለ የተሽከርካሪ አስመጪ ጋር በ300 ሺሕ ብር ለመግዛት ቢስማማም፣ ከግዢ በኋላ የሚሰጡ አገልግሎቶች ላይ ባለመስማማት ስምምነቱ በማፍረስ ከሞኤንኮ ጋር መፈራረማቸው ተገልጿል፡፡

70 በመቶ በብርሃን ባንክ አማካይነት ብድር የተመቻቸላቸው ሲሆን፣ 30 በመቶውን (110 ሺሕ ብር) የማኅበሩ አባላት በማውጣትና በ13.75 በመቶ የብድር ወለድ ታሳቢ ክፍያ ታክሲዎቹን ተረክበዋል፡፡

በአምስት ዓመት የብድር መክፈያ ጊዜ ውስጥ ዕዳቸውን ማጠናቀቅ የሚጠበቅባቸው ሲሆን፣ ሁለት ዓይነት የአከፋፈል ዘዴ እንደተቀመጠላቸውም ተጠቅሷል፡፡ የሦስት ወራት የእፎይታ ጊዜን ጨምሮ ሙሉ ክፍያውን መክፈል ለሚፈልጉ፣ አለያም በየወሩ ከ4000 ብር ጀምሮ መክፈል እንዲችሉ ወይም በወር ከ8,500 ብር በላይ ክፍያ በመፈጸም ዕዳቸውን ማቃለል የሚችሉበትን አሠራር ባንኩ ማመቻቸቱን የኮንፈርት ሜትር ታክሲ ማኅበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ዮሐንስ ባልቻ አብራርተዋል፡፡

ከዓመት በፊት ከቀረጥ ነፃ የሚገቡበት ዋጋ 463 ሺሕ ብር የነበረ ቢሆንም፣ መኪናዎቹ እስኪገቡ ባለው ጊዜ ውስጥ የዶላር የምንዛሪ ዋጋ በመጨመሩ ምክንያት በአንዱ መኪና ብቻ የ22 ሺሕ ብር ጭማሪ በማሳየቱ፣ ዋጋውን ወደ 485 ሺሕ ብር እንደደረሰ አቶ ዮሐንስ አስረድተዋል፡፡

ሰባት ሰው ማሳፈር የሚችሉት አቫንዛ ታክሲዎች፣ ጂፒኤስና የጉዞ ርቀት መለኪያ ሜትር፣ አውቶማቲክ ማርሽ፣ ቪቪቲ-አይ ሞተር የተገጠመላቸው እንደሆኑ የሞኤንኮ ጨረታና ሽያጭ ክፍል ኃላፊ ቀረጥ ሙሉጌታ ሰይፈ አብራርተዋል፡፡

አዲሶቹ ታክሲዎች 1,500 ሲሲ የፈረስ ጉልበት ያላቸው፣ የመቆጣጠሪያ ካሜራ የኪሎ ሜትር መለኪያና መቁጠሪያ፣ የአቅጣጫ ማመልከቻ (ጂፒኤስ) የተገጠመላቸው ከመሆናቸውም ባሻገር፣ ኢትዮጵያ ታክሲ የተባለው ድርጅት ባሰናዳው ዘመናዊ የስልክ ጥሪዎች ማስፈንጠሪያ (አፕልኬሽን) አማካይነት የ24 ሰዓት አገልግሎት መስጠት ይጀምራሉ ተብሏል፡፡ ደንበኞች ኮምፎርት ታክሲ አገልግሎትን ለማግኘት በ8707 በመደወል የ24 ሰዓትና የሰባት ቀናት አገልግሎት በቀላሉ ማግኘት እንደሚችሉ የኢታ ኢትዮጵያ ታክሲ መሥራች አቶ ተመስገን ገብረ ሕይወት አብራርተዋል፡፡

ከመነሻ ጀምሮ በኪሎ ሜትር 13 ብር ተደርጎ የመሳፈሪያ ዋጋው በመንግሥት በተቀመጠው ተመን መሠረት፣ ማኅበሩ ተጠቃሚውን ለማገልገል ቅድሚያ እንደሚሰጥ ይሁንና ክርክር ያስነሳውን ይኼንን የታሪፍ መጠን በሒደት ከመንግሥት ጋር በመነጋገር የማያዋጣ ከሆነ ለመፍታት እንደሚሞከር አቶ ዮሐንስ ገልጸዋል፡፡ የወጣው ታሪፍ ማሻሻያ የሚያስፈልገው ማኅበራቱ ከሚያደርጉት እንቅስቃሴ አንፃር እንደሆነና ማኅበሩን ለማሳደግ የተማረ ኃይል ቀጥረው ለማሠራት ወጪ ስለሚጠይቃቸውና በአገሪቱ ያለው የመንገድ ልማት የተቀመጠው ታሪፍ ማሻሻል እንደሚያስፈልግ የኮንፈርት ማኅበር ሥራ አስኪያጅ አክለዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞም ማኅበሩ የተለያዩ የቁጠባ መንገዶችን በመከታተልና ወደፊት ከመንግሥት መሬት በመጠየቅ የነዳጅ ማደያና የቱሪስት ተሽከርካሪዎች ላይ በሰፊው መሰማራት እንደሚፈልጉ ጠቀሰዋል፡፡

ኮንፈርት ሜትር ታክሲ ማኅበርን ጨምሮ አራት ማኅበሮች ከሞኤንኮ የአቫንዛ  ተሽከርካሪዎችን የተረከቡ ሲሆን፣ በክልልም በሐዋሳ ከተማ ማኅበር ተቋቁሞ  በዘርፉ ለመሰማራት እንቅስቃሴ መጀመራቸው ተገልጿል፡፡

ትዩ ዘመናዊ ታክሲ ማኅበር 35 ታክሲዎችን፣ ቦሌ ኤርፖርትና ሆቴል ታክሲ ማኅበር 79፣ ግሬይ ታክሲ 35፣ እንዲሁም ኮምፎርት ሳሎን ታክሲ ማኅበር 43 ዘመናዊ ታክሲዎችን ጨምሮ በአጠቃላይ 192 ታክሲዎችን አቫንዛ ዘመናዊ ታክሲዎች አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡

ኢታ ግንቦት 2 ቀን 2008 ዓ.ም. የተመሠረተ ሲሆን፣ የታክሲ አገልግሎት የሚሰጥ ድርጅትና የዘመናዊ ስልክ ታክሲ መጥሪያ አፕልኬሸን የ24/7 ቀናት የታክሲ ጥሪ ማዕከል አገልግሎት የሚሰጡ ድርጅት ነው፡፡ ኢታ ታክሲ መጥሪያ ሶፍትዌር በኢትዮጵያውያን ለኢትዮጵያኖች የተሠራ ሶፍትዌር ነው፡፡

 

Standard (Image)

የህንዱ ኩባንያ በ75 ሚሊዮን ዶላር የብረት ማቅለጫ ፋብሪካ ማስፋፊያ ሊገነባ ነው

$
0
0

 

የህንዱ አርቲ ስቲል ኩባንያ በ75 ሚሊዮን ዶላር ወይም በ1.1 ቢሊዮን ብር ወጪ የብረት ማቅለጫ ፋብሪካው ላይ የማስፋፊያ ግንባታ ሊያከናውን እንደሆነ ተገለጸ፡፡

ጠቅላላ ሀብቱ ከ1.7 ቢሊዮን ብር በላይ ይገመታል፡፡ ኩባንያው በገላን ከተማ የተለያዩ ዓይነት የቤት ክዳን ቆርቆሮዎች፣ የላሜራ ብረቶች፣ አልቲዜድና ቱቦላሬዎችን እንደሚያመርት ሐምሌ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. በሸራተን ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስታውቋል፡፡

በ2003 ዓ.ም. በ700 ሚሊዮን ብር ካፒታል በኢትዮጵያ የብረታ ብረት ማምረቻ በመገንባት ሥራ የጀመረው አርት ስቲል፣ በማስፋፊያው አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችንና ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ምርቶችን ለማምረት እንዳቀደም ተገልጿል፡፡

ታኅሳስ ወር ላይ የማስፋፊያ ግንባታውን የሚያካሂደው ኩባንያውን በዓመት 100,000 ሜትሪክ ቶን ምርት ለገበያ ለማቅረብ ያስችለዋል ተብሏል፡፡ በመሆኑም 47 ሚሊዮን ዶላር ለግንባታ ሥራና ለማሽነሪ ግዥ እንደሚውል ሲገለጽ ጋልቫናይዝድ የቆርቆሮ ምርቶችን ጨምሮ ልዩ ልዩ የብረት ውጤቶችን የማምረት አቅም ይኖረዋል፡፡

ማስፋፊያው ሦስት ዓይነት ሒደት ሲኖረው፣ በመጀመርያው የማስፋፊያ ወቅት የግብዓት ምርቶች ላይ እንደሚያተኩር የአርት ስቲል ሥራ አስኪያጅ ራጄሽ ቨርማ በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅት ጠቅሰዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት 40 በመቶ የገበያ ድርሻውን ለመያዝ ብሎም በርካታ ምርቶችን የማምረትና ለገበያ የማቅረብ አቅም የማስፋፊያ ግንባታው እንደሚፈጥርለት አስታውቋል፡፡

አርቲ ስቲል የብረታ ብረት ማምረቻ ፋብሪካ በፊንፊኔ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን ገላን ከተማ የሚገኝ ሲሆን፣ የተቋቋመበት ካፒታል ሰባት መቶ ሚሊዮን ብር ነው፡፡ 29 የውጭ አገር ሠራተኞችና 171 ኢትዮጵያውያን ሠራተኞች በድምሩ 200 ሠራተኞችን በሥሩ እያስተዳደረ የሚንቀሳቀስ ድርጀት ነው፡፡

ኩባንያው ሥራ ከጀመረበት ወቅት ጀምሮ የውጭ ምንዛሪ እጥረት በተደጋጋሚ እያጋጠመውና በሥራው ላይ እንቅፋት ሆኖበት መቆየቱን ሥራ አስኪያጁ ራጄቭ አስታውሰዋል፡፡

Standard (Image)

የውጭ ሕክምናን በአገር ውስጥ ለመስጠት የተነሳው የአንድ ቢሊዮን ብር ሆስፒታል

$
0
0

ከኢትዮጵያ ውጭ በመጓዝ ከፍተኛ ሕክምና የሚከታተሉ ዜጎች ቁጥር በየጊዜው እየጨመረ መምጣቱ ይነገራል፡፡ በአገር ውስጥ ተፈላጊውን ሕክምና ማግኘት ያልቻሉና አቅም ያላቸው ዜጎች ወደ ውጭ በሟገዝ ለሕክምና ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እንደሚያወጡም ይገለጻል፡፡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፣ ለውጭ ሕክምና የሚወጣው ወጪ  በየዓመቱ በአራት በመቶ እያደገ መጥቷል፡፡

በዚህ ምክንያት የውጭ አገር ሕክምናዎችን በአገር ውስጥ ለመስጠት የሚያስችል ሆስፒታል ለመገንባት በማሰብ፣ ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት ኢስተርን ስታር ቴርሸሪ ሆስፒታል የተሰኘ አክሲዮን ማኅበር ተመሥርቶ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡ የቦርድ ሰብሳቢው ዶ/ር መብራቱ ጀምበር እንደሚገልጹት፣ በሰነድ ከተረጋገጡ የውጭ ሕክምና መረጃዎች በመነሳት ዓመታዊው የሕክምና ወጪ ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ይልቃል፡፡ ከሰነድ ውጭ የሚወጣው ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚሆን ይገምታሉ፡፡

 የቴርሸሪ ሆስፒታል ለመመሥረት አንዱ ምክንያትም ለውጭ ሕክምና የሚወጣው የውጭ ምንዛሪ በየጊዜው እያደገ መምጣቱና ዜጎች በውጭ ሆስፒታሎች የአገልግሎት ደረጃ እዚህ መታከም እንዲችሉ በመታሰቡ እንደሆነ ዶ/ር መብራቱ ይገልጻሉ፡፡

በፕሮጀክቱ ኢንቨስት ማድረግ ሊያስገኝ የሚችለውን ጠቀሜታ የሚገልጹት የአክሲዮን ኩባንያው መሥራቾች፣ በአገሪቱና በጎረቤት አገሮች መካከል የሚታየውን የሕክምና ክፍተት ለመቀነስ ልዩ የሕክምና መሣሪያዎችን የሚጠይቁ ሕክምናዎችን ሥራ ላይ በማዋል ሆስፒታል ማቋቋሙ ከአገልግሎቱ ባሻገር ለአትራፊነቱም መልካም  ውጤት እንደሚሰጥ ይገልጻሉ፡፡ ከኢትዮጵያ በየዓመቱ ለውጭ ሕክምና የሚከፈለውን ወጪ በማስቀረት፣ ከምሥራቅ አፍሪካና ከሌሎች አገሮች በሜዲካል ቱሪዝም ተጨማሪ ገቢ የሚያስገኝ ፕሮጀክት በመሆኑ፣ አክሲዮኖቹን በቶሎ ሸጦ ፕሮጀክቱን እውን የማድረግ እምነት እንዳላቸው አስታውቀዋል፡፡

እንደ ዶ/ር መብራቱ ገለጻ፣ ጊዜ ተወስዶ በተደረገ ጥናት፣ ኢትዮጵያን የሕክምና ቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን የሚያስችላት ትልቅ ሆስፒታል መገንባት እንደሚቻል በመረጋገጡ፣ የአክሲዮን ኩባንያ ለመመሥረት የሚያስችል እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡ በሕክምና ዘርፍ በምሥራቅ አፍሪካ ቀዳሚ ሆስፒታል የመገንባት አቅም መኖሩም እንደተረጋገጠ ተገልጿል፡፡ ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ይጠይቃል የተባለው ሆስፒታል በአጭር ጊዜ ወደ ግንባታ እንደሚገባም ይጠበቃል፡፡  

ኢስተርን ስታር ቴርሸሪ ሆስፒታል አክሲዮን ማኅበር በ41 ግለሰቦች መሥራችነት የተቋቋመ ነው፡፡ የአክሲዮን ኩባንያው አማካሪ ሥራና የአክሲዮን ሽያጩን ለማከናወን ኃላፊነት የወሰደው ኮም ሊንክ ቢዝነስ አገልግሎት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ሲሆን፣ የድርጀቱ የማርኬቲንግ ኃላፊ አቶ ታዲዮስ አበበ እንደሚገልጹት፣ ኩባንያው አመኔታ እንዲኖረው ከዚህ ቀደም በአክሲዮን ኩባንያዎች ውስጥ የሚታየውን ክፍተት በመገንዘብ ምሳሌ ሊሆን የሚችል ኩባንያ ለመፍጠር እንደመሥራች የተሰባሰቡት 41 ግለሰቦች በኅብረተሰቡ ዘንድ ዕውቅና ያላቸውና በተለያዩ የሙያ ዘርፎች መልካም የሥራ ምግባር የተላበሱ ናቸው፡፡

ከ41 መሥራቾች ውስጥ 15 የሕክምና ባለሙያዎች ይገኙበታል፡፡ አብዛኛዎቹም ታዋቂ ኩባንያዎችን በመምራት የሚታወቁ ሲሆን፣ አምባሳደሮች፣ መሐንዲሶች፣ ታዋቂ ጠበቆች፣ የኢንሹራንስና የባንክ ባለሙያዎች፣ ነጋዴዎች፣ የተቋራጭ ድርጅትቶች ኃላፊዎችና በሌሎች መስክ የተሰማሩ ኢትዮጵያውያንን አሰባስቧል፡፡

አክሲዮን ኩባንያው ያስቀመጠውን ግብ ለማሳካት ትልቅ ጠቀሜታ የሚሰጠው ሲሆን፣ ለአክሲዮን ኩባንያው መነሻ ካፒታል ይሆን ዘንድም 41ዱ መሥራቾች እያንዳንዳቸው የ20,000 ብር ዋጋ ያላቸው፣ አክሲዮኖች በመግዛት በ820 ሺሕ ብር ኩባንያውን መሥርተዋል፡፡

ይህ የሕክምና ቱሪዝም ጠቀሜታና አትራፊ ዘርፍ ስለመሆኑ በደንብ አይታወቅም ያሉት አቶ ታዲዮስ፣ ሆኖም በአክሲዮን ደረጃ ተቋቁመው ውጤታማ ከሆኑት መካከል የቢራ ፋብሪካዎች፣ የፋይናንስ ኢንዱስትሪዎች ከሚያተርፉት የበለጠ እንደሚያስገኝ ይናገራሉ፡፡

‹‹እንዲያውም ዛሬ አሥር ባንኮች በዓመት ከሚያተርፉት የበለጠ ከሕክምና ቱሪዝም ብዙ ይገኛል፤›› ያሉት አቶ ታዲዮስ፣ ይህም እንዲሁ በማጋነን እንዳልሆነ ለማስረዳት ምሳሌዎችን ጠቅሰዋል፡፡ የአንድ አክሲዮን አነስተኛ የትርፍ መጠን ከ40 በመቶ በላይ እንደሚሆን አቶ ታዲዮስ ገልጸው፣ ዛሬ የሕክምና ቱሪዝምን ያራመዱ አገሮች እያገኙ ያሉት ዓመታዊ ገቢና ኢትዮጵያም በየዓመቱ ለውጭ ሕክምና የምታወጣው ወጪም ጥሩ ማሳያ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡

በሕክምና ቱሪዝም ኬንያ በዓመት አንድ ቢሊዮን ዶላር እንደምታገኝ ጠቅሰው፣ ‹‹ኢትዮጵውያን ለሕክምና የሚሄዱባቸውን አገሮች ደረጃ ያሟላ ሆስፒታል ቢኖረን ከኬንያ የተሻለ ተጠቃሚ የሚያደርገን ዕድል ሊፈጠር ይችል ነበር፤›› ብለዋል፡፡

የሜዲካል ቱሪዝም ገበያ ሰፊ ስለመሆኑም ከኢትዮጵያ ወደተለያዩ አገሮች የሚሄዱ ታካሚዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ መጨምሩን የጠቀሱት አቶ ታዲዮስ፣ ከስድስት ዓመታት በፊት ወደ ኬንያ፣ ወደ ደቡብ አፍሪካና ወደ ህንድ ታካሚዎችን ከኢትዮጵያ የሚልኩ የውጭ ሆስፒታሎች ወኪሎች ሁለት ብቻ እንደነበሩ፣ አሁን ግን ወደ 12 ማሻቀባቸውን አስታውቀዋል፡፡ ወኪሎቹ በየዓመቱ በነፍስ ወከፍ ከ2,500 በላይ ታካሚዎችን ወደ ውጭ ስለሚልኩ፣ የውጭ ታካሚዎችን ቁጥር ዕድገት አመላካች አኃዝ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡

ሌላው ማሳያ የህንድ የሕክምና ተቋማት ከምሥራቅ አፍሪካ ብቻ ከ100 ሺሕ በላይ ታካሚዎችን ተቀብለው ማስተናገዳቸው ነው፡፡ ይህም ከምሥራቅ አፍሪካ የሚጓዙ ታካሚዎች ለህንድ በዓመት 2.5 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ያስገኙላታል፡፡ በመሆኑም እንዲህ ያሉ ተጨባጭ መረጃዎች በዘርፉ ሰፊ ገበያ ለመኖሩ ያመለክታሉ ተብሏል፡፡

እንደ ቦትስዋና ባሉ አገሮች ከ50 በመቶ በላይ ኢትዮጵያውያን ዶክተሮች ተገኝተው አገልግሎት የሚሰጡባቸው ትላልቅ ሆስፒታሎች ከሕክምና ቱሪዝም ከፍተኛ ገቢ እንደሚያስገኙ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በኢትዮጵያ ይቋቋማል የተባለው ሆስፒታልም በሌሎች አገሮች የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የሕክምና ባለሙያዎችን ወዲህ ለመሳብ ጭምር እንደሚያግዝ ታምኖበታል፡፡

ሆስፒታሉ ወጪን ማዳን ብቻም ሳይሆን የውጭ ምንዛሪን ምንጭ እንደሚሆንም ይጠበቃል፡፡ ሥራ በሚጀምርበት የመጀመርያው ዓመት የሕክምና ቱሪዝም የውጭ ምንዛሪ ግኝት ከአገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ማስገኛ ዘርፎች አንዱ ሆኖ እንደሚጠቀስ የሚያምኑት አቶ ታዲዮስ፣ መንግሥት ቸል ብሎ መቆየቱንም ይጠቅሳሉ፡፡ የውጭ ሕክምና ወጪ ከፍተኛ ከመሆኑ አንፃር፣ ለኩላሊት ንቅለ ተከላ በህንድ 17 ሺሕ ዶላር፣ በኬንያ ደግሞ 20 ሺሕ ዶላር እንደሚከፈል፣ ሌሎች ሕክምናዎችም ከፍተኛ ወጪ እንደሚጠይቁ አኃዞችን አጣቅሰዋል፡፡

በመሆኑም እንዲህ ያሉ ለውጦችን የሚያመጣው ይህ ሆስፒታል እውን እንዲሆን የአክሲዮን ሽያጭ ለኢትዮጵያውያንም ሆነ ለውጭ ዜጎች ክፍት ይደረጋል ተብሏል፡፡ ተቋማትና የመንግሥት የልማት ድርጅቶችም ባለአክሲዮን እንዲሆኑ እንፈልጋለን ያሉት ዶ/ር መብራቱ፣ እንደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ያሉት ተቋማት የዚህ ፕሮጀክት አካል እንዲሆኑ መታሰቡንም ጠቅሰዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሕክምና ቱሪዝም ሲታሰብ ያለ አየር መንገድ ስለማይሆን ነው ይላሉ፡፡

የሆስፒታሉ ፕሮጀክት እውን እንደሚሆን ቢታሰብም፣ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ መንገድ የተቋቋሙ ኩባንያዎች ዳር አለመድረሳቸው የሆስፒታሉን የወደፊት አካሔድ ጥያቄ እንዲቀርበበት ያስገድዳልና እናንተስ የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ዶ/ር መብራቱ፣ ከዚህ ቀደም በመሰል ቢዝነስ ላይ ለመሰማራት አክሲዮን ወደ መሸጥ የገቡ ኩባንያዎች ዓላማቸውን ዳር ሳያደርሱ መቅረታቸውን ጠንቅቀው እንደሚያውቁ ገልጸው፣ የአክሲዮን ኩባንያው የቀደመው ታሪክ እንደማይደገም በልበ ሙሉነት ይናገራሉ፡፡

ከዚህ ቀደም እንዲህ ያለውን ሆስፒታል በአክሲዮን ኩባንያ ደረጃ ለመገንባት የተነሱ ኩባንያዎች ለምን ሳይሳካላቸው ቀረ? የሚለውን እንዳጠኑም ጠቅሰዋል፡፡ ከዳሰሳ ጥናቱም አክሲዮን ኩባንያዎቹ ሊሳካላቸው ያልቻለው ‹‹አክሲዮኑን ሲሸጡ ቢዝነሱን ከዕርዳታ ጋር አያይዘው አክሲዮን ለመሸጥ በመሞከራቸው ነው፡፡ የቢዝነሱን አዋጭነት በትክክል ካለማስረዳት የተነሳም ሊሆን ይችላል፤›› ብለዋል፡፡

ከውጭ የሚመጡ ታካሚዎችን በዓለም አቀፍ የሕክምና አገልግሎት ደረጃ መሠረት የክፍያ ዋጋ በመጠየቅ፣ የሕክምና አገልግሎት በመስጠት ትርፋማ መሆን እንደሚቻል  በጥናት መረጋገጡን የሚገልጹት ዶ/ር መብራቱ፣ አክሲዮን ማኅበሩ ከሕክምና አገልግሎት ጎን ለጎን የሕክምና ሥልጠና የሚሰጡ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም ስለሚኖሩት ይህም ሌላ የገቢ ምንጭ ከመሆኑ ባሻገር ባለሙያዎችን ለማፍራትም እንደሚያግዝ ጠቅሰዋል፡፡ የሆስፒታሉ የግንባታ ዲዛይንም ይህንኑ ታሳቢ አድርጎ የተሠራ ሲሆን፣ የተለያዩ የሕክምና መሣሪያዎችና መድኃኒቶችንም የማስመጣትና የማከፋፈል ሥራዎችን የማከናወን ዓላማ እንዳለው የአክሲዮን ኩባንያው መመሥረቻ ጽሑፍ ውስጥ ሰፍሯል፡፡

ቴርሸሪ ሆስፒታሉ ሥራ ሲጀምር ለባለአክሲዮኖች ዓመታዊ ነፃ የሕክምና ምርመራና የዱቤ ሕክምና በመስጠት ጭምር፣ የአክሲዮን ሽያጭ በተጀመረ በስድስት ወራት ውስጥ አክሲዮን ለሚገዙም የመሥራችነት መብትና ጥቅም ይሰጣል ተብሏል፡፡ በገንዘብ አቅም ማነስ ምክንያት ወደ ውጭ አገር ሄደው መታከም ለማይችሉ ለኅብረተሰብ ክፍሎች ነፃ የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኙም እገዛ ያድርጋል ተብሏል፡፡

በ55,000 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ በአዲስ አበባ ከተማ አቅራቢያ የሚገነባው ቴርሸሪ ሆስፒታሉ፣ የተለያዩ የሕክምና አገልግሎቶች መስጫ ክፍሎች፣ የሄሊኮፕተር ማረፊያና የዩኒቨርሲቲ ቦታ ይኖረዋል፡፡ ከመሥራቾቹ መገንዘብ እንደተቻለው ግን እስካሁን የግንባታ ቦታ አላገኙም፡፡ ለግንባታው ቦታ መንግሥት እንደሚሰጣቸው ይተማመናሉ፡፡

የካንሰርና የፓቶሎጂ (ፎረንሲክ ሜዲስን) ምርመራ፣ የልብ ቀዶ ሕክምና፣ የኩላሊት ንቅለ ተከላና ሕክምና፣ የነርቭ ቀዶ ሕክምና፣ የመውለድ ችግርን በዘመናዊ ሕክምና መፍትሔ የመስጠትና ሌሎችም ዘመናዊ የሕክምና አገልግሎቶች ይሰጥበታል የተባለው ይህ ሆስፒታል፣ ከሦስት እስከ አምስት ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ግንባታው እንደሚጠናቀቅም በዕቅድ መያዙን ከዶ/ር መብራቱ ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡  ግንባታው በምዕራፍ ተከፋፍሎ የሚካሄድ ሲሆን፣ የመጀመሪያው ምዕራፍ እንዳለቀ የሕክምና አገልግሎቱን እንደሚጀመር ተገልጿል፡፡  

 

Standard (Image)

አገር በቀሉ ኩባንያ የሲልከን አሸዋ በሰፊው ማምረት የሚያስችለውን ስምምነት ተፈራረመ

$
0
0

ኒውኢራ ማይኒንግ ኩባንያ ለተለያዩ ኢንዱስትሪዎች በጥሬ ዕቃነት የሚያገለግለውን የሲልከን አሸዋ በሰፊው ለማምረት የሚያስቸለውን ስምምት ከማዕድን፣ ፔትሮሊየምና የተፈጥሮ ጋዝ ሚኒስቴር ጋር ተፈራረመ፡፡ ስምምነቱ ለ20 ዓመታት የሚቆይ የማምረት መብትን ለኩባንያው ያስገኛል፡፡

የኒውኢራ ማይኒንግ ምክትል ሥራ አስኪጅና የአክሲዮን ባለድርሻ አቶ ዳዊት ሽብሩ ለሪፖርተር እንዳስታወቁት፣ በኢትዮጵያ የሲልከን አሸዋን በሰፊው ለማምረት የሚያስለቸው ፈቃድና ስምምነት በመፈጸም ኩባንያው የመጀመሪያው ሲሆን፣ በጉራጌ ዞን፣ ቡይ ወረዳ ውስጥ በሚገኘውና ኬላ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በ1.4 ካሬ ኪሎ ሜትር ስፋት ውስጥ እንደሚገኝ የሚገመተውን 91.91 ሚሊዮን ቶን ሲልከን አሸዋ ለማምረት ስምምነት ፈጽሟል፡፡

የምርት ሥራው በ18 ወራት ውስጥ እንደሚጀመር የገለጹት አቶ ዳዊት፣ ኩባንያው ለዚህ ሥራ የመደበው የኢንቨስትመንት ወጪ አሥር ሚሊዮን ዶላር እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡ የሲልከን አሸዋ ፕሮጀክቱ ወደ ሥራ ሲገባም ለ120 ሰዎች የሥራ ዕድል እንደሚያስገኝ ጠቅሰዋል፡፡

የሲልከን አሸዋ ለግንባታ ዘርፍ፣ ለሴራሚክ ማምረቻነት፣ ለዓይን መነፅር ሥራ የሚውለን የፋይበር መስታዋት ለማምረት፣ የሞባይል ስልኮች ስክሪን መሥሪያነት፣ ለቀለም ማምረቻነትና ሌሎችንም ምርቶች በግብዓትነት የሚፈለገው ይህ ምርት እስካሁን በብዛት ከውጭ እየገባ እንደሚገኝ ተጠቅሷል፡፡ በአገር ውስጥ በሰፊው ማምረት በሚጀመርበት ወቅትም ከውጭ የሚገባውን መጠን ለመቀነስ እንደሚያስችል አቶ ዳዊት ገልጸዋል፡፡

ኒውኢራ ማይኒንግ አስፈላጊውን የፍለጋ ሥራና የአዋጭነት ጥናት አጠናቆ ያቀረበው ባለፈው ዓመት እንደሆነ ያስታወሱት አቶ ዳዊት፣ በዚህም መሠረት ለመጠነ ሰፊ የማዕድን አምራችነት ፈቃድን የሚኒስትሮች ምክር ቤት የሚደነግግ በመሆኑ፣ የኩባንያው ዝርዝር ሰነዶች ለምክር ቤቱ ቀርበው በመጽደቃቸው፣ ሐምሌ 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ፈቃድ ማግኘቱን አስታውቀዋል፡፡

ይህንን ተከትሎም በሚኒስቴሩና በኩባንያው መካከል የሲልከን አሸዋ ለማምረት የሚያስችል ስምምነት ሐሙስ፣ ነሐሴ 5 ቀን 2009 ዓ.ም. ሲፈረም ሚኒስትሩ አቶ ሞቱማ መቃሳና የኩባንያው ዋና ሥራ አስኪያጅና የአክሲዮን ባለድርሻ የሆኑት ወ/ሮ ሊዲያ ሞሲሳ ስምምነቱን ፈርመዋል፡፡

እንደ አቶ ዳዊት ገለጻ፣ የ20 ሚሊዮን ዶላር መጠን ያለው ምርት ለውጭ ኩባንያ ለማቅረብ ስምምነት መደረጉን እንዲሁም ከሌላ የአገር ውስጥ መስታወት አምራች ኩባንያም የምርት አቅርቦት ስምምነት በመግባቱ ምርቱን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመጀመር ኩባንያው መዘጋጀቱን ጠቅሰዋል፡፡

ከሲልከን አሸዋ በተጓዳኝ በወርቅ ፍለጋና በድንጋይ ከሰል ምርት ዙሪያ ፈቃድ ለመውሰድ ኩባንያው ጥናት መጀመሩንም አስታውቀዋል፡፡

 

Standard (Image)

ምርት ገበያ በአዲሱ የግብይት ሥርዓት ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያወጡ ምርቶችን አገበያየ

$
0
0

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ የቡና ግብይትን ከእስካሁኑ በተሻለ መንገድ ውጤታማ እንደሚያደርግ የሚነገርለትን አዲሱን የግብይት ሥርዓት በመተግበር ሌሎችንም ምርቶች አካቶ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ከ1.1 ቢሊዮን ብር እንዳገበያየ አስታወቀ፡፡ በግብይቱ ሒደት ቡና ከ70 በመቶ በላይ ድርሻ ይዟል፡፡

ምርት ገበያው የሐምሌ 2009 ዓ.ም. የሥራ አፈጻጸሙን ይፋ ባደረገው ሪፖርት መሠረት፣ በአንድ ወር ውስጥ 1.1 ቢሊዮን ብር ያስመዘገበው ከ27 ሺሕ ቶን በላይ ቡና፣ ቦሎቄና ሰሊጥ በማገበያየት ነው፡፡

ከዚህ መጠን ውስጥ 13,927 ቶን ቡና ሲያገበያይ፣ 12,660 ቶን ሰሊጥ እንዲሁም 1,850 ቶን ነጭ ቦሎቄ ለገበያ አቅርቧል፡፡ ከግብይቱ ውስጥ ቡና ከፍተኛውን ድርሻ እንደያዘ የምርት ገበያው ሪፖርት አመላክቶ፣ በአንድ ወር ውስጥ ግብይት ከተፈጸመባቸው ምርቶች የቡና ድርሻ 49.01 በመቶ እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ በዋጋ በኩልም ከ1.1 ቢሊዮን ብር ከሚሆነው ግብይት ውስጥ 70.96 በመቶ የቡና ድርሻ ሆኗል፡፡ ከሰኔ ወር አፈጻጸም ጋር ሲነፃፀር የቡና ዋጋ በ1.39 በመቶ፣ የሰሊጥ ዋጋ ደግሞ በ13.2 በመቶ ጭማሪ እንዳሳየ ተጠቅሷል፡፡

ወደ ውጭ በሚላኩ ምርቶች ላይ የታየው ግብይት ከሐምሌ ወር የአጠቃላይ ግብይት ውስጥ የ68.43 በመቶና ድርሻ ሲይዙ፣ በዋጋ በኩልም 69.16 በመቶ እንደሸፈኑ ተጠቅሷል፡፡

በተሸኘው የሐምሌ ወር ከተከናወነው ግብይት ውስጥ 7,841 ቶን ያልታጠበ ቡና በ467 ሚሊዮን ብር ተገበያይቷል፡፡ ከቡና አብቃይ አካባቢዎች የነቀምት ቡና ከአጠቃላይ የግብይቱ የ32.54 በመቶ ድርሻ በመያዝ ለሽያጭ መቅረቡ ታውቋል፡፡

የልዩ ጣዕም ወይም የስፔሻሊቲ ቡና ግብይትን በተመለከተ የምርት ገበያው ወርኃዊ ሪፖርት፣ 1,761 ቶን ስፔሻሊቲ ቡና በ131 ሚሊዮን ብር መገበያየቱን ይጠቁማል፡፡ ለአገር ውስጥ ፍጆታ የሚውል 2,635 ቶን ቡና በ1.23 ሚሊዮን ብር ግብይት ተፈጽሞበታል፡፡ ለአገር ውስጥ ፍጆታ ከቀረበው ቡና ውስጥ 68.91 በመቶው ያልታጠበ ቡና እንደነበረም ታውቋል፡፡

ከቡና ባሻገር 12,660 ቶን የሰሊጥ ምርት በ317 ሚሊዮን ብር ተገበያይቷል፡፡ የሁመራ ሰሊጥ ከአጠቃላይ ግብይቱ ውስጥ የ70.74 በመቶ ሲሸፍን፣ የግብይት ዋጋውም 72.52 በመቶ በማስመዝገብ ትልቁን ድርሻ እንደያዘ ተጠቅሷል፡፡

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በ2009 ዓ.ም. 26.5 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው 621,538 ሜትሪክ ቶን የግብርና ምርቶችን አገበያይቷል፡፡ ይህም የግብይት መጠን እስካሁን ከተመዘገበው ከፍተኛ እንደሆነና ከዚህ ውስጥ 19.5 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያለው 302,997 ሜትሪክ ቶን ቡና ማገበያየቱን መግለጹ ይታወሳል፡፡

 

Standard (Image)

የኢትዮጵያ የሠራተኛ መብት ከትናንት እስከ ዛሬ

$
0
0

የዓለም የሥራ ድርጅት (ILO) በ1911 ዓ.ም. ሲመሠረት ኢትዮጵያ ከመጀመርያዎቹ አባል አገሮች አንዷ ነበረች፡፡ በ1916 ዓ.ም. ደግሞ የዓለም የሥራ ድርጅት አባል ሆና ተመዝግባለች፡፡

ከዚህ በኋላ ዓለም አቀፍ ተቋማትና ወዳጅ አገሮች ኢትዮጵያ ባርነትንና ተገዶ መሥራትን በሕግ እንድትከለክል በንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ላይ ግፊት ማድረግ ጀመሩ፡፡

የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት በወቅቱ የዓለም የሥራ ድርጅት ያወጣቸውን ዓለም አቀፍ ስምምነቶች (ኮንቬንሽን) በመቀበል፣ ለዓለም አቀፍ ተቋማትና ወዳጅ አገሮች ግፊት አዎንታዊ ምላሽ መስጠት ጀመረ፡፡

በዚያ ወቅት የውጭ ባለሀብቶች በልዩ ልዩ ፋብሪካዎች፣ በትራንስፖርትና በንግድ ሥራዎች መሰማራት ጀምረው ነበር፡፡ በጭሰኛና በባለርስት የፊውዳል ሥልት ምርት ይመራ የነበረው ኃላቀር ኢኮኖሚ፣ ወደ ኢንዱስትሪ የማደግ አዝማሚያ ማሳየት ጀመረ፡፡

በወቅቱ የነበረው የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ይህ ዕርምጃ ለዲፕሎማሲ ብቻ ሳይሆን ለአገሪቱም ዕድገት አስተዋጽኦ እንዳለው በመረዳት በኢትዮጵያ የመጀመርያውን፣ ‹‹የሠራተኛ ጤናና ደኅንነት አዋጅ ቁጥር 58/1936›› ደነገገ፡፡

ይህ የቁጥጥር አካል በጊዜው በነበረው የኢንዱስትሪና ንግድ ሚኒስቴር ሥር በተደራጀ ቦርድ ይመራ ነበር፡፡ የቁጥጥር ተቋሙ በ1944 ዓ.ም. በአዲስ አበባ፣ በድሬዳዋ፣ በአሥመራና በምፅዋ ከተሞች የሥራ ሁኔታዎችን ቁጥጥር ማድረግ ጀምሮ እንደነበር የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር በ1996 ዓ.ም. ያካሄደው ጥናት ያመለክታል፡፡

ይህ የሕግ ሰነድ መሠረታዊ የሆኑ የሥራ ሁኔታዎች ለመወሰን የቻለ ሲሆን በተለይ የሥራ ሰዓት፣ የሳምንት ዕረፍት፣ የዓመት ዕረፍት፣ የሕመም ፈቃድና የአገልግሎት ካሳ ክፍያ በተመለከተ ፋብሪካዎች በተቋቋሙባቸው የአገሪቱ ክፍሎችና የወደብ እንቅስቃሴ በሚታዩባቸው እንደ ምፅዋ ባሉ ከተሞች የሥራ ሁኔታዎች በሕጉ መሠረት ተፈጻሚ ይሆኑ ዘንድ በድርጅቶችና ንግድ ቤቶች የቁጥጥር ተግባር እንዲካሄድ መሠረት መጣሉ ይነገራል፡፡

ይህ አሠራር እስከ ንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ውድቀት ቢቀጥልም፣ በወታደራዊው መንግሥት የሥልጣን ዘመን ግን ፈሩን ለቋል፡፡

በ1966 ዓ.ም. የተካሄደው ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ያስከተለው የሥርዓት ለውጥ በአገሪቱ የወታደራዊ አገዛዝ እንዲሰፍን፣ የመንግሥት የአስተዳደር ዘይቤም የዕዝ ሥርዓት የሚያራምድና ሶሻሊስታዊ መርህ የተከተለ እንዲሆን አደረገ፡፡ ለውጡ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ መስኮች መሠረታዊ ዕርምጃዎችን የወሰደ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል የመሬት ላራሹ ታወጀ፣ ትርፍ የመኖሪያ ቤቶች፣ ባንኮችና የግል ኢንዱስትሪዎች በአዋጅ ወደ መንግሥት እንዲዛወሩ አድርጓል፡፡

እንዲሁም ሶሻሊስታዊ ባህሪ ያነገበ ‹‹የሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 64/1968›› እንዲታወጅ አድርጓል፡፡ በድርጅቶችና የሥራ ክርክር ኮሚቴዎች መደራጀት፣ የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማኅበር በአዋጅ ቁጥር 222/1974 በአዲስ መልክ በመንግሥት ድጋፍ መደራጀትን፣ የአሠሪዎች ማኅበር በሕጉ መፍረስንም አስከትሏል፡፡

ይህ አካሄድ ከሶሻሊስት መርህ አንፃር ለሠራተኛው ክፍል ከፍተኛ የሆነ የሕግ ጥበቃ የሰጠ፣ በተቃራኒው ደግሞ የድርጅት አሠሪዎች በሕግ የመደራጀትና ጥቅምን በተመለከተ የተደነገገውን ዓለም አቀፍ መብት የተጋፋ አዋጅ በመሆኑ በዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ ተወግዟል፡፡

ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት በ1983 ዓ.ም. አገሪቱን ከተቆጣጠረ በኋላ በሽግግር መንግሥቱ ቻርተርም ሆነ ሕገ መንግሥቱ በአዋጅ ቁጥር 1/1987 ዓ.ም. ከፀደቀ በኋላ የሠራተኞች ጉዳይ በድጋሚ አዲስ መልክ ያዘ፡፡

‹‹ሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 31 ላይ ማንኛውም ሰው ለማንኛውም ዓላማ በማኅበር የመደራጀት መብት አለው፤›› ሲል ደንግጓል፡፡

በአንቀጽ 36 ላይም የሕፃናት ጉልበት ከመበዝበዝ ልማዶች የመጠበቅ፣ በትምህርት፣ በጤናና በደኅንነት ላይ ጉዳት የማያደርሱ ሥራዎችን እንዲሠሩ ያለመገደድ ወይም ከመሥራት የመጠበቅ መብት ተደንግጓል፡፡

በአንቀጽ 42 ላይም እንዲሁ፣ በማምረቻና በአገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች ውስጥ የተሰማሩ ሠራተኞች፣ በእርሻ ሥራ የተሰማሩ ሠራተኞች፣ ገበሬዎችና የገጠር ሠራተኞች የጤናና የኢኮኖሚ ጉዳዮችን ለማሻሻል በማኅበር የመደራጀት መብት አላቸው፡፡ እነኚህ ሠራተኞች ሥራ ማቆምን ጨምሮ ቅሬታቸውን የማሰማት መብት እንዳላቸው በሕገ መንግሥቱ የተደነገገ ሲሆን በፋብሪካ፣ በአገልግሎት ሰጪ ድርጅቶችና በሌሎችም የተሰማሩ ሠራተኞች የተወሰነ የሥራ ሰዓት እረፍትና የመዝናኛ ጊዜ በየጊዜው ከክፍያ ጋር የሚሰጡ የእረፍት ቀናት፣ ደመወዝ የሚከፈልባቸው የሕዝብ በዓላት፣ እንዲሁም ጤናማና አደጋ የማያደርስ የሥራ አካባቢ የማግኘት መብት እንዳላቸው ተደንግጓል፡፡

ነገር ግን ኢትዮጵያ የሠራተኞች መብትን ለማስከበር፣ የሥራ ላይ ደኅንነቶችን በማረጋገጥ ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ከገባች በርካታ ዓመታት ቢቆጠሩም፣ ችግሩ ከመቀነስ ይልቅ እስከዛሬ ድረስ ተባብሶና ተወሳስቦ ቀጥሏል፡፡

የሠራተኛ ማኅበራት ጩኸት ሰሚ በማጣቱም በርካታ ሠራተኞች፣ የመደራጀት መብታቸው ተነፍጎና የሥራ ደኅንነታቸው አደጋ ላይ ወድቆ ኑሮአቸውን ለመግፋት ተገደዋል፡፡  

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) ከአሥር ዓመት በፊት ጥር 1998 ዓ.ም. ባካሄደው 12ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔ ባቀረበው ሪፖርት፣ በአገሪቱ ሕገ መንግሥትና በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/1996 የሠራተኛው የመደራጀት መብት የተደነገገ ቢሆንም፣ በተግባር ግን በርካታ ችግሮች ተደቅነውበታል፡፡ በተለይም በግል ድርጅቶች የሚሠሩ በርካታ ሠራተኞችን በማኅበር ለማደራጀት የሚደረገው ጥረት በአሠሪዎች ማናለብኝነት እየተከለከሉ ይገኛሉ በማለት ገልጿል፡፡

‹‹በማኅበር ለመደራጀት የሚፈልጉ ሠራተኞችን ድርጅቶች ያስፈራራሉ፣ ያባርራሉ፣ ሕገወጥ ዝውውር ያደርጋሉ፣ ፈቃድ ይከለክላሉ፤›› በማለት ኢሠማኮ ጉዳዩን ኮንኖታል፡፡ ኢሠማኮ ይህን ሪፖርት ካቀረበ ከአሥር ዓመታት በኋላ የኢሠማኮ ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ከሪፖርተር ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፣ ይህ ችግር አሁንም ተንሠራፍቶ ቀጥሏል፡፡

‹‹የሠራተኛ የመደራጀት መብት በተመለከተ አሁንም የተፈታ ነገር የለም፤›› በማለት አቶ ካሳሁን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በአዲስ አበባ በ79 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሞጆ ከተማ ሰሞኑን ያጋጠመን ክስተት መመልከት ያሻል፡፡ በሞጆ ከተማ ካሉ በርካታ የቆዳ ፋብሪካዎች ውስጥ እንዱ በቻይና ባለሀብቶች የተቋቋመው ፍሬንድሺፕ ታነሪ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ ነው፡፡  

ይህ ፋብሪካ 1,500 ሠራተኞች ያሉት ሲሆን፣ የኩባንያው ሠራተኞች ማኅበር አቋቁመው ነበር፡፡ ነገር ግን ኩባንያው ለሠራተኞች የሥራ ደኅንነት የሚጠብቅ ባለመሆኑ፣ በርካታ ሠራተኞች ለአካል ጉዳት እየተዳረጉ ነው፡፡፡

ይኼንን አስከፊ ሁኔታ የፍሬንድሺፕ ታነሪ ኩባንያ መሠረታዊ የሠራተኛ ማኅበር ፕሬዚዳንት አቶ አታቄ አዶ ለሚዲያ በመግለጻቸው፣ ከሥራ መታገዳቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በዚህ ኩባንያ ውስጥ ባለፈው ሳምንት በተፈጠረ የሥራ ላይ አደጋ ሁለት ሠራተኞች የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ አቶ አበሩ ንጉሤ የተባሉ የቆዳ ፋብሪካው ማሽን ኦፕሬተር በእጃቸው ላይ ከፍተኛ አደጋ ደርሶባቸዋል፡፡ ሌሎችም ሠራተኞች የተለያዩ የአካል ጉዳት እየደረሰባቸው ይገኛል፡፡

አቶ አታቄ፣ ‹‹በፋብሪካው ውስጥ በርካታ በደሎች እየተፈጸሙ ነው፡፡ የአካል ጉዳትም እየተበራከተ ነው፡፡ የፋብሪካው ማኔጅመንት ይህን አሠራር እንዲያስተካክል በተደጋጋሚ ቢነገረውም ማሻሻያ አላደረገም፤›› በማለት እየደረሰ ያለው በደል ሰሚ እንዳላገኘ ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን የኢንዱስትሪ ሰላምና የማኅበራት ስምምነት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሙሉነህ ደሳለኝ ጉዳዩ ሪፖርት እንደተደረገላቸው ለሪፖርተር ገልጸው፣ በቅርበት እየተከታተሉት መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በሞጆ ከተማ ከ30 በላይ የቆዳ ፋብሪካዎች የሚገኙ ሲሆን፣ ከእነዚህ ፋብሪካዎች ውስጥ ግማሽ ያህሉ ብቻ የሠራተኛ ማኅበራት እንዳሏቸው ተገልጿል፡፡

በአሁኑ ወቅት እየተስፋፋ ያለው ችግር ደግሞ ‹‹ሌበር ኤጀንሲ›› የሚሰኙ ኩባንያዎች፣ ሠራተኞችን እየመለመሉ ለድርጅቶች ማቅረባቸው፣ የሙያ ደኅንነትና ጤንነት ተግባራዊ አለመሆን፣ የዓመት ፈቃድ መከልከል፣ በቂ ደመወዝ አለመክፈል፣ የሴት ሠራተኞችን የወሊድ ፈቃድ መከልከል፣ አደጋ መከላከያ የሥራ አልባሳት አለማቅረብና አደጋ ከደረሰ በኃላ ሠራተኛው ራሱ እንዲታከም መፍረድ፣ ኩባንያዎች የተጣለባቸውን ግዴታ ላለመወጣት የሚሉት ተጠቃሾች ናቸው፡፡

በተለይ የግል ሥራና ሠራተኛ አገናኝ ኤጀሲዎች ‹‹ሌበር ኤጀንሲ›› ቀደም ባሉት ጊዜያት የፅዳት ሠራተኞች፣ የጥበቃ ሠራተኞንና የመሳሰሉ አነስተኛ ሥራዎች የሚሠሩ ሠራተኞችን ብቻ በመመልመል ያቀርቡ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ደግሞ ሥልጡን ባለሙያዎችን ጭምር በመመልመል በሰፊው ማሰማራት ጀምረዋል፡፡

አቶ ፍሬው በቀለ የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን፣ የኃይል ኬሚካልና ማዕድን ፌዴሬሽንን ለበርካታ ዓመታት በፕሬዚዳንትነት መርተዋል፡፡ ከዓመት በፊት ከኮንፌዴሬሽኑ አመራሮች ጋር በተፈጠረ ያለመግባባት ወደ እናት ማኅበራቸው ተመልሰዋል፡፡

አቶ ፍሬው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በአሁኑ ወቅት ሌበር ኤጀንሲዎች እያከናወኑ ያሉት ተግባር በፍፁም ተቀባይነት የለውም፡፡ ምክንያታቸውን አቶ ፍሬው ሲገልጹ፣ ሥራውን የሚሠራው ቅጥር ሠራተኛው ሆኖ ሳለ፣ ተጠቃሚዎቹ ግን ኤጀንሲዎች ናቸው፡፡ ይህ የዓለም አቀፍ የሠራተኛ ድርጅት በሚያዘጋጃቸው መድረኮች ሁሉ ሲወገዝ የቆየ ጉዳይ ነው፡፡

‹‹ውግዘቱ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ አገሮች የሚገኙ ሠራተኛ ማኅበራት ያወገዙትና የሚያወግዙት ጉዳይ ነው፤›› ያሉት አቶ ፍሬው፣ ‹‹ነገር ግን ሌበር ኤጀንሲ ጭራሽኑ ይጥፋ ማለት ሳይሆን፣ የጥቅሙ ጉዳይ ሕጋዊና ፍትሐዊ ሊሆን ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ በፍጥነት በማደግ ላይ ካሉት አገሮች መካከል አንዷ ሆናለች፡፡ በዚህ ሒደት ኢኮኖሚዋ እያደገ በርካታ መንግሥታዊና የግል ኮርፖሬሽኖች በስፋት ዘርፉን እየተቀላቀሉ ይገኛሉ፡፡

መንግሥት ሥራ አጥነትን ለመቅረፍም እየተፈጠሩ ባሉ ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች የሰው ኃይሉን ማሰማራት ይፈልጋል፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ወቅት እየተፈጠሩ ባሉ የሥራ መስኮች እየገቡ ያሉ ሠራተኞች የሠራተኛ ማኅበራት ለማቋቋም በሚሞክሩበት ወቅት እየተከለከሉ ይገኛሉ፡፡

አቶ ካሳሁን እንደሚገልጹት በተለይ በተቋቋሙ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ሠራተኛ ለማደራጀት ተሞክሮ ነበር፡፡ ‹‹ከተቋቋሙት ዘጠኝ ኢንዱስትሪ ዞኖች አንዱ ብቻ ለሠራተኛ ማኅበሩ መልካም ነው፡፡ የተቀሩት ስምንቱ ለተቋቋሙት የሠራተኛ ማኅበራት ዕውቅና አልሰጡም፤›› ብለዋል አቶ ካሳሁን፡፡

በኢትዮጵያ ሠራተኞች ላይ እየደረሰ ያለው ጉዳት እጅግ ከፍተኛ ቢሆንም ችግሩን ለመፍታት የፌዴራል መንግሥት፣ የክልል መንግሥትና የአሠሪዎች ትልቅ ድርሻ ሊኖራቸው ይገባል፡፡

የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር ተወካይ አቶ ባሳዝን ደርቤ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ‹‹ኢትዮጵያ ከዓለም የሠራተኛ ድርጅት መርህ፣ ከሕገ መንግሥቱና ከአዋጅ 377/1996 አንፃር ማኅበራት በነፃ የመደራጀት መብታቸውን አስጠብቃለች፡፡ ‹‹ሠራተኞች በራሳቸው አነሳሽነት ተደራጅተው ሲመጡ ሚኒስቴሩ ዕውቅና ይሰጣል፤›› በማለት የገለጹት አቶ ባሳዝን፣ ‹‹ከሶሻሊስት አስተሳሰብ በመነሳት በሠራተኛ መደራጀት በኩል ጣልቃ ለመግባት የሚመክሩ አሉ፡፡ ይህ ልክ አይደለም፤›› በማለት አቶ ባሳዝን አስረድተዋል፡፡ ‹‹የሠራተኞች መደራጀት ለመብት ብቻ ሳይሆን ለልማትም አስፈላጊ በመሆኑ፣ የሠራተኞች መደራጀት መሥሪያ ቤታቸው ይፈልገዋል፤›› በማለት አቶ ባሳዝን ገልጸዋል፡፡ 

ከዚህም በላይ ግን የኢትዮጵያ ሠራተኛ መሠረታዊ ማኅበራት ያቋቋሙት ኮንፌዴሬሽን ችግሮቹን ለመፍታት ትልቅ ድርሻ ሊኖረው ይገባል፡፡   

አቶ ፍሬው ግን ኮንፌዴሬሽኑ ይህንን ኃላፊነቱን በብቃት እየተወጣ ነው ብለው አያምኑም፡፡ አቶ ፍሬው ምክንያታቸውን ሲያስረዱ፣ የኮንፌዴሬሽኑ አመራሮች የራሳቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ ሲሯሯጡ፣ ሰፊውን ሠራተኛ ዘንግተውታል፡፡

‹‹አመራሮቹ በከፍተኛ የሀብት ቅርምት ውስጥ ናቸው፡፡ አላሠራ ያላቸውንም ጠልፈው ለመጣል በሰፊው ይንቀሳቀሳሉ፤›› በማለት የችግሩን ጥልቀት ያብራራሉ፡፡

የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን በአዲስ አበባ ላይ ለማቋቋም ሲሞከር የካዛብላንካና የሞኖሮቪያ ቡድኖች የሚባሉ ተፈጥረው እንደነበር አይዘነጋም፡፡ የካዛብላንካና ቡድን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት አዲስ አበባ ላይ እንዳይቋቋም ካስተጋቧቸው ተቃውሞዎች መካከል፣ ‹‹ኢትዮጵያ የሠራተኛ ሕግ የሌላት፣ የሠራተኛ መብት የማታከብር፣ ባርያ የሚሸጥበት አገር ናት፣ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት አዲስ አበባ ላይ ሊቋቋም አይገባም፤›› የሚሉ ይገኙበታል፡፡

ይህንን ተቃውሞ ለመግታትም ጭምር በወቅቱ ኢትዮጵያ የዓለም የሠራተኛ ድርጅት አባል ለመሆን መወሰኗም ይነገራል፡፡

ያም ሆነ ይህ፣ ኢትዮጵያ የሠራተኞችን መብት ለማክበር ከተነሳች 100 ዓመታት ቢቆጠሩም አሁንም ችግሩ ጎልቶ እየተነሳ ነው፡፡   

 

Standard (Image)

የሰነዶች ማረጋገጫ ከአገልግሎት ክፍያ 1.2 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን አስታወቀ

$
0
0

የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ኤጀንሲ በ2009 ዓ.ም. ከጠቅላላ አገልግሎት ክፍያና ከቴምብር ቀረጥ ሽያጭ 1.2 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን አስታወቀ፡፡

ተቋሙ በተጠናቀቀው ዓመት 1.5 ሚሊዮን ባለጉዳዮችን አስተናግዶ ከሰበሰበው አጠቃላይ ገቢ 227 ሚሊዮን ብር የሚጠጋውን ወደ መንግሥት ማስገባቱንም ገልጿል፡፡

የኤጀንሲው የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊ አቶ ዓለምሸት መሸሻ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በተጠናቀቀው ዓመት ለኤጀንሲው ከቀረቡት አጠቃላይ ጉዳዮች 747,521 ጉዳዮችን አስተናግዷል፡፡

ከቴምብር ሽያጭ ብቻ የተገኘው ከአጠቃላይ ገቢው 323 ሚሊዮን ብር እንደሚደርስ የገለጹት አቶ ዓለምእሸት፣ ተቋሙ በዓመቱ ሊሰበስብ ያቀደው 350 ሚሊዮን ብር የቴምብር ሽያጭ ገቢ እንደነበርም ገልጸዋል፡፡

በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት የተገኘው ገቢ ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በጉዳይ ብዛት የ81,479፣ የተገልጋይ ቁጥር የ163,443 እንዲሁም በሽያጭ መጠን የ48,977,748 ብር ዕድገት ማሳየቱንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡

በቁጥር ባይገልጹትም ኤጀንሲው በዓመቱ ካዋዋላቸው ስምምነቶችና ሽያጮች ውስጥ የተሽከርካሪዎችና የመኖሪያ ቤቶች የሽያጭ ውሎች ከፍተኛውን ድርሻ እንደያዙ አቶ ዓለምሸት ጠቅሰዋል፡፡

በዓመቱ ለታየው የገቢ ዕድገት ምክንያት ካሏቸው ውስጥ ተቋሙ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን መተግበሩ፣ የአቅም ግንባታ ሥልጠና ለሠራተኞቹ መስጠቱና የአሠራር ማሻሻያዎችን መተግበሩ ይገኙበታል፡፡

ኤጀንሲው በፌዴራል መንግሥት ሥር ከሚተዳደሩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በሥራ ቅልጥፍና በአንፃራዊነት የተሻለ መሆኑ ይነገርለታል፡፡ በገቢ ረገድም ከፍተኛ ገንዘብ ከሚሰበስቡ ተቋማት ተርታም ይመደባል፡፡

Standard (Image)
Viewing all 720 articles
Browse latest View live