Quantcast
Channel: አስተያየት
Viewing all 720 articles
Browse latest View live

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የሚጠበቁትን ያህል ቱሪስቶች እንዳይመጡ እክል መፍጠሩ ታወቀ

$
0
0

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አስቀምጦ በነበረው የጉዞ ገደብ ምክንያት ከ100,000 በላይ የውጭ ጐብኚዎች መቅረታቸው ታወቀ፡፡ ካቻምና ለጉብኝት ወደ አገሪቱ የመጡ ቱሪስቶች ቁጥር 900,000 የነበረ ሲሆን፣ በዚያው ጊዜ ውስጥ ከቱሪዝም ዘርፍ የተገኘው ገቢም 3.5 ቢሊዮን ዶላር ነበር፡፡

ይሁንና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተደነገገበት ወቅት፣ ዜጎቻቸው ወደ ኢትዮጵያ እንዳይመጡ አገሮች የጉዞ እገዳና ማስጠንቀቂያ ሲያወጡ ቆይተዋል፡፡ አንዳንዶቹም እስካሁን ድረስ የእገዳ ማስጠንቀቂያቸውን አላነሱም፡፡ ይህ በመሆኑ ምክንያት እ.ኤ.አ. በ2016 ወደ አገሪቱ የመጡ ጐብኚዎች ቁጥር ወደ 800,000 ዝቅ ሊል መቻሉ በጥናት ታውቋል፡፡ በአንፃሩ በወቅቱ የተገኘው የውጭ ምንዛሪ ገቢ 128 ቢሊዮን ብር ወይም 5.6 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን፣ በኢንተርኔት ለእንግዶች የሆቴል ክፍሎችን በማስያዝ ሥራ ላይ የሚሠራው ጁሚያ ትራቭል ሐሙስ የካቲት 9 ቀን 2009 ዓ.ም. ይፋ ያደረገው ሪፖርት አመልክቷል፡፡

በበተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) መዝገብ ውስጥ ከአሥር በላይ የማይዳሰሱና የሚዳሰሱ ቅርሶችን በዓለም ቅርስነት ያስመዘገበችው ኢትዮጵያ፣ በተለያዩ ምክንያቶች ከቱሪዝም ዘርፍ ማግኘትና መጠቀም የሚገባትን ያህል ሳትጠቀም መቆየቷ ይታወቃል፡፡ ካሏት የቅርጾች ብዛትና የመልክዓ ምድር አቀማመጥና የተፈጥሮ መስህቦች አኳያ እጅጉን ዝቅተኛውን የቱሪስት ቁጥርና የቱሪዝም ገቢ በማግኘት ላይ ነች፡፡

ለዚህም በአገሪቱ ያለው የመስተንግዶ ኢንዱስትሪ ደካማነት በዋናነት ይጠቀሳል፡፡ በቱሪዝም መዳረሻ አካባቢዎች የመሠረተ ልማት ዝርጋታ አለመሟላት፣ የአገሪቱ የቱሪዝም ሀብቶች እንደሚገባቸው አለመተዋወቃቸው፣ የአገር ውስጥ ጐብኚዎች የጉብኝት ልማድ ዝቅተኛ መሆንና ሌሎችም ዘርፉ የሚጠበቅበትን ያህል እንዳያስገኝ ካደረጉት መካከል ሊጠቀሱ የሚችሉ ችግሮች ናቸው፡፡

በሌላ በኩል በአገሪቱ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸው ሆቴሎች እንደሚፈለገው መጠን አለመኖራቸውም እንደ ችግር ይጠቀሳል፡፡ ይሁንና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከቱ መምጣታቸው እየታየ ነው፡፡ በሪፖርቱ መሠረት 84.4 በመቶ ከቱሪዝም የሚገኘው ገቢ ለመዝናናት ብለው ወደ አገሪቱ ከሚገቡ ጐብኚዎች የሚገኝ ነው፡፡ እነዚህ ጐብኚዎች እንደፍላጎታቸው ዘመናዊና ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ባሟሉ ብራንድ ሆቴሎች ለመዝናናት ፍላጎት የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ነገር ግን በአገሪቱ ያሉት ዓለም አቀፍ ሆቴሎች ብዛት በተለይም በክልል ከተሞች የሚገኙት በቁጥር ውስን በመሆናቸው ሳቢያ  ጐብኚዎች ደጋግመው እንዲመጡ የማይጋብዝ ሁኔታ ፈጥሯል፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን የመስተንግዶ ኢንዱስትሪው መሻሻሎችን እያሳየ በመምጣቱ ምክንያት ከቱሪዝም የሚገኘው ገቢም በዚያው መጠን እየጨመረ ይገኛል፡፡ የካቻምና አኃዞች እንደሚያሳዩት፣ የጉዞና የጉብኝት ዘርፍ በኢኮኖሚው ውስጥ ያለው ድርሻ (ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት አኳያ) የ4.1 በመቶ ድርሻ እንደነበረው ነው፡፡ ይህ ኢኮኖሚያዊ ድርሻ እ.ኤ.አ. በ2026 ወደ አምስት በመቶ ከፍ እንዲል በማቀድ መንግሥት እየተንቀሳቀሰ መሆኑ በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡ በመጪዎቹ አሥር ዓመታት ውስጥም ከቱሪዝም የሚገኘውን ገቢ ወደ 675 ቢሊዮን ብር ወይም ወደ 29.8 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ዕቅድ ተይዟል፡፡ ዘርፉ እስካሁን 2,326,500 ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩ ይነገርለታል፡፡ ይህ በመሆኑም በኢኮኖሚው ውስጥ የ8.4 በመቶ የቅጥር ድርሻ እንደሚይዝ የሚያሳይ ነው፡፡

አገሪቱን ከአምስት ቀዳሚ የአፍሪካ የቱሪስት መዳረሻ አገሮች አንዷ ለማድረግ ያላትን እምቅ አቅም ከማስተዋወቅ ጀምሮ የተለያዩ ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን በዕለቱ የተገኙት የቱሪዝም ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሰለሞን ታደሰ ገልጸዋል፡፡

ወደ አገሪቱ የሚመጡ ጎብኚዎች ቁጥር ከፍ እንዲልም ከፍተኛ የማስተዋወቅ ሥራ ይጠበቃል፡፡ 31 በመቶ የሚሆኑት ጐብኚዎች ከተለያዩ የአፍሪካ አገር ሲመጡ፣ 30 በመቶ አውሮፓውያንና ሰሜን አሜሪካውያን ናቸው፡፡ ከውጭ አገር ጐብኚዎች የሚገኘው ገቢ 68.7 በመቶ ሲሆን፣ ከአገር ውስጥ ጐብኚዎች የሚገኘው ደግሞ 31.3 በመቶ ደርሷል፡፡ 39 በመቶ የሚሆኑት ጐብኚዎች አዲስ አበባ ውስጥ ጊዜያቸውን ያሳልፋሉ፣ 11 በመቶ ደግሞ በሐዋሳ፣ 8.1 በመቶ የሚሆኑት ቢሾፍቱን ይመርጣሉ፣ 7.5 በመቶዎቹ ደግሞ ባህር ዳርን የሚያዘወትሩ መሆናቸውን በሪፖርቱ ተዘርዝሯል፡፡  

‹‹አገሪቱ በቱሪዝም ሴክተር ያልተነካ አቅም አላት፡፡ የመስተንግዶ ኢንዱስትሪውም ቢሆን ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ ይገኛል፤›› ያሉት የጁሚያ ትራቭል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፓውል ሜዲ፣ የሚጠበቀውን ያህል ውጤት ለማግኘት የተለያዩ ፈታኝ ነገሮች ቢኖሩም ትልቅ ተስፋ መኖሩን ተናግረዋል፡፡

በኦንላይን ሆቴል ቡኪንግ ላይ የሚሠራው ጁሚያ ትራቭል ኢትዮጵያ መጥቶ አገልግሎት መስጠት ከጀመረ ዓመት አልፎታል፡፡ በመላው አገሪቱ ከሚገኙ 600 ሆቴሎች ጋር አብሮ በመሥራት ላይም ይገኛል፡፡

የድርጅቱ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወ/ት ኤደን ሳህሌ እንደገለጸችው፣ ድርጅቱ በሙሉ አቅሙ እንዳይሠራ አንዳንድ ችግሮች ማነቆ እየሆኑበት ይገኛሉ፡፡ ዋናው ችግር የኢንተርኔት አገልግሎት መቆራረጥ ሲሆን፣ በተለይ በክልል ከተሞች ከሚገኙ ሆቴሎች ጋር አብረው ከመሥራት እያገዳቸው ይገኛል፡፡ ብዙ ጊዜ ከደንበኞቻቸው ጋር በድረ ገጻቸው መገናኘት ስለማይችሉ በስልክ ለመሥራት ይገደዳሉ፡፡ ከዚህ ባሻገርም ኅብረተሰቡ ስለኦንላይን ሆቴል ቡኪንግ አገልግሎት ያለው ግንዛቤ ዝቅተኛ በመሆኑ፣ የአገር ውስጥ ጐብኚዎችን በሚፈለገው መጠን ለማግኘት እንዲቸገሩ አስገድዶናል ብላለች፡፡ 

Standard (Image)

የአማራ ንግድ ምክር ቤት ምርጫና ጠቅላላ ጉባዔ ተሻረ

$
0
0

 

የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ እንዳይካሄድ እንደ አንድ ምክንያት ሲጠቀስ የቆየውና መስከረም 29 ቀን 2009 ዓ.ም. ተካሄዶ የነበረው የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ ተሽሮ፣ ጠቅላላ ጉባዔው እንዲደገምና አዲስ ምርጫ እንዲካሄድ ተወሰነ፡፡

የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት አካሂዶት የነበረውን ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ እንዲሻርና እንዲደገም የወሰነው የአማራ ንግድ ኢንዱስትሪና ገበያ ልማት ቢሮ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ቢሮው ከዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ጠቅላላ ጉባዔውና ምርጫውን የተመለከቱ አቤቱታዎችን ከመረመረ በኋላ መሆኑን ከቢሮው ተፈርሞ የወጣው ደብዳቤ ያመለክታል፡፡ በቅርቡም ንግድ ሚኒስቴር የክልሉ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የምርጫ ሒደት ሕጋዊ መንገድን የተከተለ አልነበረም በሚል በቀረቡለት ተደጋጋሚ አቤቱታዎች፣ የምርጫ ሒደቱ እንዲጣራ ማሳሰቡ ይታወሳል፡፡ ቢሮው ከዚህ ውሳኔ ላይ ከመድረሱ በፊት መስከረም 29 ቀን 2009 ዓ.ም. የተደረገውን የምርጫ ሒደትና አጠቃላይ ክንውኑን በተመለከተ በዕለቱ ተመርጠው የነበሩ አመራሮች፣ ሒደቱ ምንም ዓይነት ችግር ያልነበረበት መሆኑን እንዳስረዱት ይገልጻል፡፡ ቅሬታ አቅራቢዎች ባስገቧቸው አምስት የሚሆኑ ነጥቦች ላይ ባካሄደው ማጣራት፣ በአራቱ ላይ ምንም ችግር አለማግኘቱን፣ በአንዱ ላይ ግን የሕግ ጥሰት ማግኘቱን በማስታወቅ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ቢሮው ውሳኔ ከሰጠባቸው አምስት ነጥቦች መካከል አንዱ ‹‹ጠቅላላ ጉባዔው ምልዕተ ጉባዔ ሳይሟላ የተካሄደ ነው፤›› የተባለው ቅሬታ ይጠቀሳል፡፡ የክልሉ ንግድ፣ ኢንዱስትሪና ገበያ ልማት ቢሮ ምክር ቤት ኃላፊ በተገኙበት ምልዓት ጉባዔው መሟላቱ ተረጋግጦ ወደ ሪፖርት ማቅረብ የተገባ በመሆኑ፣ ይህ ቅሬታ አግባብነት የሌለው ነው ተብሏል፡፡ ‹‹ፕሬዚዳንቱ ለ12 ተከታታይ ዓመታት ሥልጣን ይዟል፤›› የተባለው ቅሬታ፣ በአዋጅ ቁጥር 341/95 አንቀጽ 10 ንዑስ አንቀጽ 3 እና በምክር ቤቱ የመተዳደሪያ ደንብ የቦርድ አባላት የሥልጣን ዘመን ሁለት ዓመት ስለመሆኑ እንጂ አንድ ሰው ለስንት ጊዜ ብቻ መመረጥ እንደሚችል በግልፅ ስለማያመላክት፣ ቅሬታው ተቀባይነት የሌለው መሆኑንም ቢሮው የጻፈው ደብዳቤ ያስረዳል፡፡

‹‹የዳይሬክተሮች የቦርድ አባላት አላግባብ እርስ በርሳቸው ተሸላልመዋል፤›› በተባለው ቅሬታ ላይ፣ የሥራ አመራር ቦርዱ ላለፉት ዓመታት ያገለገሉ የዳይሬክተሮች የቦርድ አባላትን እንዳይሸልም የሚከለክል ሕግ የሌለ በመሆኑ ቢሮው ቅሬታውን አለመቀበሉን ገልጿል፡፡ ነገር ግን በሽልማቱ ዙሪያ የዳይሬክተሮች የቦርድ አባላት ተሰናባች የቦርድ አባላትን ብቻ ቢሸልም ጥሩ ስለሚሆን፣ ቦርዱ የራሱን ውሳኔ እንዲወስን አስተያየት በመስጠት በሽልማቱ ላይ ለቀረበው ቅሬታ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

‹‹ምርጫው አስቀድሞ በተደራጀ ኔትወርክ በአደረጃጀት የተፈጸመው ነው፤›› የተባለውም ቅሬታ ላይ ቢሮው ባደረገው ማጣራት፣ ከቅድመ ምርጫ በፊትም ሆነ በምርጫ ወቅት እንዲሁም በድኅረ ምርጫ በአደረጃጀትና በኔትወርክ የተፈጸመ ምርጫ ስለመሆኑ ተጨባጭ ማስረጃ እንዳላገኘበት አስታውቋል፡፡

አምስተኛ ነጥብ ሆኖ ቢሮው የተመለከተውና ብዙ ሲያጨቃጭቅ የነበረው ‹‹የታችኛው ምክር ቤት ውክልና ሳይኖራቸው ፕሬዚዳንቱን ጨምሮ ነባር የቦርድ አባላት እንዲመረጡ ተደርጓል፤›› የሚለው ቅሬታ ላይ ግን፣ የቢሮው የሕግ ጥሰት የታየበት ሆኖ አግኝቶታል፡፡ የሕግ ባለሙያዎችና የርዕሰ መስተዳድሩ የሕግ አማካሪ ከሕግ አኳያ አስተያየት የተሰጠበት መሆኑን የሚያመለክተው የውሳኔ ደብዳቤ፣ በቢሮው በተጠየቀው መሠረት የባለሙያዎች አስተያየት ከሰጡበት በኋላ የዚህ ቅሬታ ጭብጥ የሕግ ጥሰት ያለበት ስለመሆኑ ያሳየ መሆኑን ይገልጻል፡፡ በባለሙያዎቹ አስተያየት መሠረት ‹‹የአንድን ክልል የንግድና የዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ሊያቋቁሙ የሚችሉት በዚያው ክልል ውስጥ አስቀድመው የተቋቋሙ የከተማ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶችና የክልል ወይም የወረዳ የዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች ስለመሆናቸው በአዋጅ ቁጥር 341/1995 አንቀጽ 14 ንዑስ አንቀጽ 1 ሥር በግልጽ ተደንግጓል፡፡››

በዚህ ዓይነት የሚቋቋመው የክልል አቀፍ ምክር ቤት መሥራች ጉባዔም ከአባላቱ መካከል ፕሬዚዳንቱንና ምክትል ፕሬዚዳንቱን ጨምሮ ከአሥራ አንድ የማይበልጡ ተወካዮችን በቦርድ አባልነት መርጦ እንደሚሰይም በአዋጁ አንቀጽ 10 ንዑስ አንቀጽ 1 እና አንቀጽ 17 መጠቀሱንም ያስታውሳል፡፡

በአንቀጽ 10 ንዑስ አንቀጽ 1 ሥር ‹‹ተወካዮች›› የሚለው ኃይለ ቃል ጉባዔተኛዎቹ በክልል አቀፍ ምክር ቤት ስብሰባ ለመሳተፍ፣ ለመምረጥ፣ ለመመረጥ የታችኞቹን የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶችን ይሁንታ ማግኘት እንዳለባቸው አመላካች ሆኖ መገኘቱን በመግለጽ ውሳኔውን ሊሰጥ ችሏል፡፡

ከዚህ ውጭ በተሰናባቹ ምክር ቤት አማካይነት ለነባር የቦርድ አባላት ተሰጥቶ ነበር የተባለው ‹‹ልዩ ውክልና›› አዋጁ ለታችኞቹ ምክር ቤቶች የሰጠውን በየራሳቸው እንደራሴ የመወከል መብት ጋር የሚጣረስ ነው ብሎታል፡፡ በታችኞቹ ምክር ቤቶች ያልተወከለ ሰው በክልል ምክር ቤት ጉባዔ ተወካይ ሊሆን ስለማይችል፣ የመሳተፍም ሆነ ድምፅ የመስጠት መብት እንደማይኖረው የባለሙያዎች ማብራሪያ እንደሚያስረዳ በቢሮው ምክትል ኃላፊ ተፈርሞ የወጣው ደብዳቤው ጠቅሷል፡፡

ከዚህ በመነሳትም የአማራ ክልል ንግድ፣ ኢንዱስትሪና ገበያ ልማት ቢሮ ከቀረቡ አምስት ቅሬታዎች መካከል በአራቱ ላይ ችግር ያላገኘ መሆኑን አስታውቋል፡፡ ሆኖም በአምስተኛውና በመጨረሻው ቅሬታ ከሕግ ባለሙያዎች ሙያዊ መብራሪያ አኳያ ከአዋጅ ቁጥር 341/95 ድንጋጌ ጋር የሚጋጭ አሠራር አግኝቼበታለሁ ብሏል፡፡ ስለሆነም መስከረም 29 ቀን 2009 ዓ.ም. የተካሄደውን የአማራ ክልል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የጠቅላላ ጉባዔ ምርጫ ሕጋዊ ባለመሆኑ እንዳልተቀበለው አረጋግጦ፣ ጠቅላላ ጉባዔውንና ምርጫውን የሚያግድ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ስለዚህ ጠቅላላ ጉባዔውና ምርጫው ሕጋዊ ባለመሆኑ ቢሮው ደብዳቤ ከተጻፈበት ቀን ጀምሮ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ አስቸኳይ ጉባዔ እንዲጣራም አሳስቧል፡፡ አያይዞም በሕጉ መሠረት ፕሬዚዳንቱንና ምክትል ፕሬዚዳንቱን ጨምሮ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላት ምርጫ እንዲካሄድ በጥብቅ ያሳሰበው የቢሮ ደብዳቤ፣ በግልባጭ ለተለያዩ መሥሪያ ቤቶች አሳውቋል፡፡ ቢሮው ይህንን ውሳኔ ቢወስንም በአንድ ወር ይጠራ የተባለውን ምርጫና ጠቅላላ ጉባዔ ማን ያስፈጽመው የሚለውን አለመጥቀሱ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ ከቢሮው ውሳኔ በኋላ አንዳንድ የንግድ ምክር ቤቱ አባላት እንደገለጹት፣ ምርጫውን ማን ያስፈጽመው የሚለው ጥያቄ ምላሽ ካልተሰጠው አሁንም አስቸጋሪ ሁኔታ ይፈጠራል፡፡ በተለይ ምርጫው ይደገም ከተባለ አመራሮቹም ታግደዋል ማለት ነውና ይህ በግልጽ መገለጽ እንዳለበት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

እንደ አማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ሁሉ ሕግን ተከትለው ምርጫ አላደረጉም እንዲሁም አመራሮቻቸው ከመተዳደሪያ ደንባቸው ውጪ ከሁለት የምርጫ ዘመን በላይ ተመርጠዋል የሚል አቤቱታ የቀረበባቸው የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤትና የአገር አቀፍ ዘርፍ ምክር ቤት ጉዳይም በሚመለከታቸው የመንግሥት ቢሮዎች ጉዳያቸው እየተጣራ ይገኛል፡፡

ሕግን ተከትለው ምርጫ ማድረግ አለማድረጋቸውን እንዲሁም ከሕገ ደንባቸው ውጪ ተመርጠዋል የተባሉ አመራሮች፣ ውክልናቸው ትክክል መሆኑ አለመሆኑን እንዲያረጋግጡለት የዘርፍ ምክር ቤቱን በተመለከተ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴርን ማብራሪያ ጠይቋል፡፡ ከዚህም ሌላ የዘርፍ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት ውክልናንም በተመለከተ የትግራይ ክልል ንግድ ቢሮ ማብራሪያ ተጠይቆ ምላሽ እየተጠበቀበት ነው፡፡ በተመሳሳይ የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ በአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጉዳይ ማብራሪያ እንዲሰጠው በደብዳቤ ጭምር ጠይቋል፡፡

በተለይ ከመተዳደሪያ ደንብ ውጪ ከሁለት የምርጫ ዘመን በላይ በፕሬዚዳንትነት አገልግለዋል በሚል ጥያቄ ከተነሳባቸው መካከል የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው አየነውና የአገር አቀፍ ዘርፍ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ገብረሕይወት ገብረእግዚአብሔር ይገኙባቸዋል፡፡ ሁለቱም ከአሥር ዓመታት በላይ ቦታውን ይዘው የቆዩ እንደሆኑ መዘገቡ አይዘነጋም፡፡

የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ምርጫ ፍትሐዊ አልነበረም የሚለው ትችት ከአባል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጭምር ሲቀርብ የነበረ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤትም አማራን ጨምሮ ከአንዳንድ አባል ምክር ቤቶች ያካሄዱት የምርጫ ሒደት ሕጋዊ አይደለም በሚል አጣሪ ኮሚቴ እስከማቋቋም መድረሱ ይታወሳል፡፡ አጣሪ ኮሚቴውም ሕግን ያልተከተሉ አባል ምክር ቤቶች ሕግ ከጣሱ ዕርምጃ ይወሰድ በሚል ውሳኔ አስተላልፎ ጠቅላላ ጉባዔውም ጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲካሄድ ቢወስንም፣ የመጨረሻ ውሳኔ ባለመሰጠቱ ችግሩን በራሱ መንገድ ለማጣራት ንግድ ሚኒስቴር ጠቅላላ ጉባዔውን እንዳገደው ይታወሳል፡፡

የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ከተቋቋመበት ከ1999 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ መስከረም 2009 ዓ.ም. ድረስ ስድስት ጠቅላላ ጉባዔዎችን እንዳካሄደ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ 

Standard (Image)

የአዲስ ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት ተሳታፊዎች ቁጥር ቀነሰ

$
0
0
  • ቱርክና ግብፅ ኩባንያዎቻቸውን መላክ አልቻሉም

በኢትዮጵያ በቋሚነት ከሚዘጋጁ የንግድ ትርዒቶች መካከል በርካታ የውጭ ኩባንያዎችን በማሳተፍ የሚታወቀው የአዲስ ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ዓውደ ርዕይ፣ በዘንድሮ ዝግጅቱ በተለይ የውጭ ኩባንያዎች ተሳታፎ እንደቀነሰበት ተገለጸ፡፡ በርካታ ኩባንያዎችን ሲያሳትፉ የቆዩት ቱርክና ግብፅ በ21ኛው የንግድ ትርዒት እንዲሳተፉ ሲጠበቁ የነበሩ ኩባንዎቻቸውን መላክ እንዳልቻሉ ታውቋል፡፡

ንግድ ትርዒቱን በባለቤትነት ከሚያስተዳድረውና ከሚያዘጋጀው ከአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው፣ ሐሙስ የካቲት 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ተከፍቶ ለሰባት ተከታታይ ቀናት እንደሚቆይ በተገለጸው 21ኛው ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት ወቅት 180 ኩባንያዎች እንደሚሳተፉ ይጠበቃል፡፡ ከእነዚህ ኩባንያዎች ውስጥ 100 ያህሉ ከ27 አገሮች የተውጣጡ የውጭ ኩባንያዎች እንደሆኑ ተገልጿል፡፡ ቀሪዎቹ 80 ኩባንያዎች በተለያዩ የንግድ ዘርፎች ውስጥ የተሰማሩ የአገር ውስጥ ኩባንያዎች ናቸው፡፡

ሆኖም ‹‹የተመቻቸ ሁኔታ ለተቀላጠፈ የውጭ ንግድ ሥራ›› በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው የዘንድሮው የንግድ ትርዒት ላይ ይሳተፋሉ የተባሉት የኩባንያዎች ቁጥር ከቀደሙት ዓመታት ጋር ሲነፃፀር ዝቅተኛ ሆኗል፡፡ እንደ ምክር ቤቱ መረጃ ከሆነ፣ ዓምና በተካሄደው የንግድ ትርዒት ላይ 202 ኩባንያዎች፣ በካቻምናው ደግሞ 218 ኩባንያዎች ተሳትፈዋል፡፡

ዘንድሮ የሚሳተፉት ኩባንያዎች ብዛት 180 በመሆኑ ከካቻምናው 38፤ ከዓምናው ደግሞ 22 ኩባንያዎች ቀንሰዋል፡፡ በተለይ የውጭ ኩባንያዎች ተሳትፎ ከአገር ውስጥ ይልቅ ብልጫ ቢያሳይም፣ በ2008 ዓ.ም. ተሳታፊ ከነበሩት 131 የውጭ ኩባንያዎች አንፃር ሲታይ፣ የዘንድሮው ተሳታፊዎች ቁጥር በ30 እንደቀነሰ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከካቻምናዎቹ አኳያ የተሳታፊዎቹ ቁጥር በ63 ቀንሷል፡፡ በ2007 ዓ.ም. በተካሄደው የንግድ ትርዒት ወቅት ተሳታፊ የነበሩት የውጭ ኩባንያዎች ብዛት 163 እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኩባንያዎች ቁጥር ለምን እንደቀነሰ ያነጋገርናቸው የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ዋና ጸሐፊ አቶ ጌታቸው ረጋሳ፣ ‹‹በዘንድሮው የንግድ ትርዒት ላይ የተሳታፊዎች ቁጥር ለማነሱ ዋነኛ ምክንያት የሆነው ከዚህ ቀደም በተከታታይ ይሳተፉ የነበሩ የግብፅና የቱርክ ኩባንያዎች መሳተፍ ባለመቻላቸው ነው፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

ከሁለቱ አገሮች የሚመጡ ኩባንያዎች አብዛኛውን ጊዜ ከሌሎች አገሮች ተሳታፊዎች ይልቅ ብልጫ እንደነበራቸው ያስታወሱት አቶ ጌታቸው፣ ዘንድሮ መሳተፍ ባለመቻላቸው የተሳታፊዎች ቁጥር እንዲቀንስ ምክንያት ሆነዋል ብለዋል፡፡

 አቶ ጌታቸው እንደሚሉት፣  በየዓመቱ በንግድ ትርዒቱ ላይ ለመሳተፍ  በርከት ያሉ ኩባንያዎች ከቱርክ ይመጡ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡ ከ30 እስከ 40 ያህል የቱርክ ኩባንያዎች ከአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል አዳራሾች አንዱን ለብቻቸው በመከራየት ሲሳተፉ ቆይተዋል፡፡ ዘንድሮ ግን ኩባንያዎቹን አሰባስቦ ያመጣ የነበረው የንግድ ምክር ቤቱ ወኪል ኩባንያ በቱርክ ከተከሰተው ፖለቲካዊ ችግር ጋር በተያያዘ ኩባንያዎቹን እንዲመጡ ማድረግ እንዳልቻለ ማስታወቁን አቶ ጌታቸው ተናግረዋል፡፡   

በንግድ ትርዒቱ እንዲሳተፉ በርካታ ኩባንያዎችን በመላክ የምትታወቀው ግብፅም ዘንድሮው እንደማትሳተፍ አቶ ጌታቸው ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ከ25 ያላነሱ የግብፅ ኩባንያዎች ሰፊ ቦታ ይዘው ምርትና አገልግሎታቸውን ያስተዋውቁ እንደነበርም ተገልጿል፡፡ በዘንድሮ ዝግጅት ላይ ግን በተናጠል የመጡ አምስት የግብፅ ኩባንያዎች ብቻ ተገኝተዋል ተብሏል፡፡ 21ኛውን የአዲስ አበባ ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት፣ የንግድ ሚኒስትሩ ዶ/ር በቀለ ቡላዶ እንደሚከፍቱት ንግድ ምክር ቤቱ አስታውቋል፡፡  

Standard (Image)

ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ለኢንዱስትሪ ባለሀብቶች የሚሰጠው ማበረታቻ ፖለቲካዊ አንደምታ የለውም አለ

$
0
0

 

-  የሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ከሁለት ዓመት በኋላ የአንድ ቢሊዮን ዶላር ገቢ ያስገኛል አለ

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ በማኑፋክቸሪንግ መስክ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የሚሰጣቸው ማበረታቻዎችና የሚያካሂዳቸው የባለሀብቶች ምልመላ ሥራዎች ፖለቲካዊ አንድምታ እንደሌላቸው ገለጸ፡፡

ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት በመንግሥት ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሠራበት ይገኛል፡፡ አዋጅ ወጥቶለት፣ አዋጁን የሚያስፈጽም ደንብ ለማፀደቅ እንቅስቃሴ ላይ ይገኛል፡፡ ይሁንና በአምራች ኢንዱስትሪዎች መስክ ባለሀብቶች የሚመረጡባቸው አካሄዶች ላይ ከሪፖርተር ጥያቄ የቀረበላቸው የኢንቨስትመንት ኮሚሽነሩ አቶ ፍፁም አረጋ፣ የባለሀብቶቹ ምልመላም ሆነ የማበረታቻ አሰጣጡ ፖለቲካዊ ፍጆታም ሆነ የግልጽነት ችግር እንደሌለበት ገልጸዋል፡፡

በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ ለሚሰማሩ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች የብድር፣ ከቀረጥ ነፃ የማሽነሪ መብት፣ የታክስ እፎይታ፣ የቴክኒክና የመሳሰሉት ሥልጠናዎች የሚካተቱበት፣ ተደማምሮ እስከ 90 በመቶ የሚደርስ የፋይናንስ ድጋፍ እየሰጣቸው እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡ ይህ መሆኑ የመንግሥትን አሠራር ጥያቄ ውስጥ ሊከተው አይችልም ወይ ለሚለው አቶ ፍፁም ሲያብራሩ፣ መንግሥት ማበረታቻዎቹን የሚሰጠው ባለሀብቶች ተገቢውን ድጋፍ አግኝተው በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ አምራችነት መግባት የሚችሉባቸውን መንገዶች ለማመቻቸት ነው፡፡ መንግሥት የመሥሪያ ሼዶችን ከማዘጋጀት ባሻገር ኢንቨስተሮችን በመመልመል እንደሚያመጣ ሲያብራሩ በተለይ የውጭ ባለሀብቶች በዚህ መስክ ሰፊውን ድርሻ እንደሚይዙ ጠቅሰዋል፡፡

በዚህ መሠረት አቅምና ብቃቱ ያላቸው የውጭ ኩባንያዎችና ኢንቨስተሮች ተመልምለው እንዲመጡ ሲደረግ በመንግሥት ከቀረጥ ነፃ ዕድል ካልሆነ በቀር ምንም ዓይነት ብድር ከአገር ውስጥ እንደማይሰጣቸው አቶ ፍፁም አብራርተዋል፡፡ ከውጭ የሚመጡት የራሳቸውን ፋይናንስ ይዘው የሚመጡ በመሆናቸው ከአገር ውስጥ የፋይናንስ ተቋም ብድር እንደማይሰጣቸው ጠቅሰዋል፡፡

በአንፃሩ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ እንዲሳተፉ የሚደረገው ለሕዝብ ይፋ በሚደረግ የማስታወቂያ ጥሪ እንደሆነና አቅም ያላቸው፣ ዝግጁ የሆኑ ባለሀብቶች ይሳተፉበታል በማለት መንግሥት ለየትኛውም ባለሀብት የፖለቲካ ድጋፍ እንደማይሰጥ አስታውቀዋል፡፡

ከዚህ ባሻገር ለአራት ዙር በተለያዩ መንግሥታዊ ተቋማትና የግል ኩባንያዎች ተሳትፎ ውይይት ሲደረግበት የቆየው የኢንዱስትሪ ፓርኮች አዋጅ ማስፈጸሚያ ረቂቅ ደንብ በቅርቡ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቦ እንደሚፀድቅ ይፋ ተደርጓል፡፡ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የተመራ ውይይት፣ ሰኞ የካቲት 13 ቀን 2009 ዓ.ም. በሸራተን ሲካሄድ፣ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ልማት ባንክ፣ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን፣ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ሚኒስቴር፣ የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና ሌሎችም መንግሥታዊ ተቋማት ውይይቱ ላይ ተሳትፈዋል፡፡ በቅርቡ እንደሚፀድቅ በሚጠበቀው ረቂቅ ደንብ ላይ በተካሄደው ውይይት ላይ ተቋማቱ ማሻሻያዎች እንዲደረጉባቸው የሚሿቸው ነጥቦች ላይ ተነጋግረዋል፡፡

አቶ ፍፁም እንደሚገልጹት ከ40 በላይ የመንግሥት ተቋማት በአገሪቱ የወጪና ገቢ ንግድ ላይ የየራሳቸው ድርሻ አላቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ በአንድ ተቀናጅተው በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ አንድ ወጥ አሠራር የሚዘረጉበት የአንድ መስኮት አገልግሎት ማቅረብ በአዲሱ ሕግ እንደሚሠሩ አብራርተዋል፡፡

የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለማስተዳደር የወጣው አዋጅ ቁጥር 886/2007ም ሆነ እሱኑ ተከትለው የሚወጡና የሚተገበሩ ሕጎችን በአንድ ማዕከል እያስፈጸመ አግልገሎቶችን ለማቅረብ የሚያስችል፣ እስካሁን ያልነበረ አዲስ አሠራር በኢትዮጵያ እንዲተገበር እንደሚያስችል አቶ ፍፁም ተናግረዋል፡፡ በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ የሚተገበረው ለየት ያለ ሕግ ውጤታማ መሆን ከቻለ በመላ አገሪቱ እንዲተገበር ለማድረግ እንደሚፈለግም ገልጸዋል፡፡ ሕጉ ደረቅ ወደቦችን የሎጂስቲክስ ፓርኮች በሚል ስያሜ፣ ከአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ጋር በማጣመር በአንድ ወጥ አሠራር ለማስተዳደር እንደሚያስችልም ተጠቅሷል፡፡

በሌላ በኩል በአሥር ወራት ውስጥ ተገንብቶ የተጠናቀቀውና ከጥቂት ወራት በፊት ሥራ የጀመረው የሐዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ ከ37 በላይ ፋብሪካዎች ምርት እንደጀመሩ ሲገለጽ፣ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥም ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚገመት የውጭ ምንዛሪ ገቢ እንደሚያስገኙ አቶ ፍፁም አስታውቀዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ይህ ገቢ ሊገኝ እንደሚችል ሲገለጽ ቢቆይም፣ ከሠራተኞች ቅጥርና ሥልጠና እንዲሁም ከሌሎችም መሟላት ከሚጠበቅባቸው ግብዓቶች አኳያ ከሐዋሳ ኢንዱስትሪ የሚጠበቀው የጨርቃ ጨርቅ የወጪ ንግድና የውጭ ምንዛሪ ገቢ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሊሳካ እንደሚችል ከአቶ ፍፁም ለመረዳት ተችሏል፡፡

ከዚህም ባሻገር በአገሪቱ የተገነቡትም ሆኑ ወደፊት የሚገነቡት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ባዷቸውን ይቀራሉ፣ የሚገባባቸው ባለሀብትም ይታጣል የሚል ሥጋት መንግሥት እንደሌለውም አቶ ፍፁም ይጠቅሳሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት በዓለም እየታየ ባለው የኢንዱስትሪዎች ፍልሰት (ግሎባል ሺፍት ወይም ሪሎኬሽን) ምክንያት በርካታ አምራቾች አዋጭ አገሮችን በማፈላለግ ላይ መሆናቸው ለኢትዮጵያ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ትልቅ አጋጣሚ ሆኖ ቀርቧል፡፡፡ ከዚህ አኳያ ከእስያ አገሮች ጋር ትንቅንቅ ማድረግ ያስፈልጋል ያሉት አቶ ፍፁም፣ ኢትዮጵያ ካላት ዝቅተኛ የሰው ጉልበት ወጪና ከሌሎችም ድጋፎች አኳያ የእስያ ተቀናቃኞቿን መወዳደርና እንደ ቻይና ካሉ አገሮች በመሰደድ ላይ የሚገኙ ባለሀብቶችን መሳብ ከቻለች፣ የምትገነባቸው ፓርኮች ፆም እንደማያድሩ አቶ ፍፁም ያምናሉ፡፡ ይህም ቢባል መንግሥት የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ከመገንባት ጎን ለጎን የውጭ ባለሀብቶችን አፈላልጎ ለማምጣት ስለሚሠራ ፓርኮች ባዶ ይቀራሉ የሚል ሥጋት እንደማያሳስብ ገልጸዋል፡፡ 

Standard (Image)

የቱርክና የግብፅ ታዳሚዎች ሲጠበቁ የቀሩበት የንግድ ዓውደ ርዕይ 180 ኩባንዎችን አሳትፏል

$
0
0

 

በየዓመቱ በቋሚነት ከሚዘጋጁ ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒቶች ውስጥ አንዱ ‹‹አዲስ ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት›› እየተባለ የሚታወቀው ተጠቃሽ ነው፡፡ ይህ ንግድ ትርዒት በዚህ ስያሜው ላለፉት 20 ዓመታት ሲካሄድ ቆይቷል፡፡ ዘንድሮም ለ21ኛ ጊዜ የሚካሄደው ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት ሐሙስ፣ የካቲት 16 ቀን 2009 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ተከፍቷል፡፡

180 የአገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎች የተሳተፉበት የዘንድሮው አዲስ ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒትን የከፈቱት የንግድ ሚኒስትር ዴኤታው አቶ አሰድ ዘይድ ናቸው፡፡

ካለፉት ሦስት ተከታታይ ዓመታት አንፃር ሲታይ በ21ኛው የንግድ ትርዒት ወቅት የተሳተፉ የውጭ ኩባንያዎች ቁጥር ቢቀንስም፣ ከ27 አገሮች የተውጣጡ ኩባንያዎች እንደታደሙበት ተጠቅሷል፡፡ በዕለቱ እንደተገለጸው ዘንድሮ በንግድ ትርዒቱ ከሚጠበቁ የውጭ ኩባንያዎች መካከል ተሳትፏቸው ከቀነሱባቸው ምክንያት አንዱ በርካታ ኩባንያዎችን ሲያሳትፉ የቆዩት ቱርክና ግብፅን የመሰሉ አገሮች ዘንድሮ ኩባንያዎቻቸውን ባለመወከላቸው ነው፡፡ በንግድ ትርዒቱ መክፈቻ ሥርዓት ወቅት የንግድ ምክር ቤቱ ዋና ጸሐፊ አቶ ጌታቸው ረጋሳም ይህንኑ ጠቅሰዋል፡፡

‹‹በቀደሙት ዓመታት በአዲስ ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት ወቅት ከጎናችን ባለመለየት ሲሳተፉ የነበሩት የቱርክ ባለሀብቶች በአገራቸው ባለው ሁኔታ ምክንያት መሳተፍ ስላልቻሉ የተሰማን ሐዘን ጥቅል ነው፤›› በማለት የቱርክ ኩባንያዎች ያልተገኙበትን ምክንያት ገልጸዋል፡፡   

የግብፅ ኩባንያዎችም በዘንድሮው የንግድ ትርዒት ወቅት ላለመሳተፋቸው ምክንያት እንዳላቸው በንግግራቸው የጠቀሱት አቶ ጌታቸው፣ በቀጣዩ ዓመት በሚዘጋጀው 22ኛው ትርዒት ላይ በትላልቅና በርካታ ቁጥር ባላቸው ኩባንያዎች እንደሚወከሉ ከወዲሁ ማስታወቃቸውን አቶ ጌታቸው ተናግረዋል፡፡

የሁለቱ አገሮች ኩባንያዎች አለመሳተፍ በአገሪቱ ትልቅ ከሆኑት ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒቶች አንዱ እንደሆነ በሚጠቀሰው ዝግጅት ላይ የተገኙ የውጭ ኩባንያዎችን ቁጥር 100 ብቻ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ ይህም ከአምናው የውጭ ኩባንያዎች ተሳታፎ አንፃር ሲታይ በ31 መቀነሱን አቶ ጌታቸው አመላክተዋል፡፡

ይህም ሆኖ ዘንድሮ የመጡት ተሳታፊዎች ምርትና አገልግሎታቸውን ከማስተዋወቅ ባሻገር የእርስ በርስ ግንኙነት የሚፈጥሩበት መድረክ ተመቻችቶላቸዋል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ የንግድ ትርዒትም ሆነ በሌሎች ንግድ ምክር ቤቱ በሚያካሂዳቸው ተግባራት ንግድና ኢንቨስትመንት እንዲበረታታ፣ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት እንዲሳብ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት አቶ ጌታቸው ገልጸዋል፡፡

በተለይ የኢንቨስትመንት ፕሮሞሽንና የንግድ ለንግድ ግንኙነት እንዲጎለብት የአገር ውስጥ ኩባንያዎችን ከውጭ ኩባንያዎች ጋር በማስተሳሰር የንግድ ትርዒቱ እንደ ድልድይ እያገለገለ እንደሚገኝ ተጠቅሷል፡፡

21ኛውን የንግድ ትርዒት የከፈቱት የንግድ ሚኒስትር ዴኤታው አቶ አሰድ ዘይድ ባደረጉት ንግግር ወቅት አፅዕኖት የሰጡት፣ ዓለም አቀፋዊውን የንግድ ውድድርና ግሎባላይዜሽን የተመለከተ አካሄድ መከተልና እንደሚገባ ነው፡፡ በተለይ በዘመነ ግሎባላይዜሽን ፈጣን ለውጦች እየታዩ ከመሆኑ አንፃር፣ የኢትዮጵያ ኩባንያዎች ከዓለም እኩል ይራመዳሉ ወይ? የሚለው ጉዳዩ ሊታሰብበት እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡

የትኛውም ኩባንያ ከዓለም አቀፍ የገበያ ውድድር ውጭ ሊሆን እንደማይችል በመጥቀስ፣ የኢትዮጵያ ኩባንያዎችም ከዚህ ውጭ ስለማይሆኑ በዓለም የሚታዩትን ለውጦችን እንዲያጤኑ ጠይቀዋል፡፡ በአጭር ጊዜ ውስጥ ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል እንደምትሆን የገለጹት አቶ አሳድ፣ በዓለም የንግድ ማዕቀፍ መሠረትም  የንግድ ድርጅቶች ሊገዙበት የሚገባ ሕግ እንደሚወጣ በንግግራቸው ጠቅሰዋል፡፡  

ይህ ሕግም የዓለም የንግድ ድርጅት ሕግጋቶችን መሠረት በማድረግ በሁሉም የኢኮኖሚ ዘርፎች ውስጥ ያሉ ቢዝነሶች የሚተዳደሩበት መሆኑን በመጥቀስ፣ ለዚህ ዝግጁ መሆን እንደሚገባም አመላክተዋል፡፡

የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የመንግሥት ስትራቴጂያዊ አጋር ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፣ ንግድና ኢንቨስትመንትን በማበረታት እንዲሁም የአባላቶቹን አቅም ለማጎልበት ኃላፊነቱን እየተወጣና ይህን ኃላፊነት ለመወጣት ከሚያስችለው አንዱ የንግድ ትርዒት ዝግጅቱ ስለመሆኑ ተናግሯል፡፡

ይሁን እንጂ ንግድ ምክር ቤቱ የንግድ ትርዒቱን በሚፈለገው የጥራት ደረጃ ለማስጓዝ ያልቻለ ስለመሆኑ ሳይጠቅሱ አላለፉም፡፡ ለዚህም አንዱ ምክንያት ደረጃውን የጠበቀ የኤግዚቢሽን ሥፍራ አለመኖር ነው፡፡

ለንግድ ትርዒቱን በተሻለ ጥራትና ደረጃ ለማዘጋጀት የንግድ ትርዒት ማሳያ ቦታ ክፍተትን ለመቅረፍ ደግሞ ንግድ ምክር ቤቱ ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽና ኮንቬንሽን ማዕከል ለመገንባት በመንቀሳቀስ ላይ እንደሚገኝም አስታውሰዋል፡፡ ለዚህም ግንባታ መንግሥት የፋይናንስ ድጋፍ በማድረግ ጭምር አጋርነቱን እንዳሳየ ከሚኒስቴር ዴኤታው ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡

በዕለቱ ንግድ ምክር ቤቱን በመወከል ንግግር ያደረጉት የምክር ቤቱ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መኮንንም የአዲስ አበባ ኤግዚቢሽንን ዘመናዊ ለማድረግና ለማስፋት ከአንድ የስፔን ኩባንያ ጋር የተጀመረውን ሥራ አንስተዋል፡፡

በሐሙሱ የንግድ ትርዒት መክፈቻ ላይ ከወትሮ የተለየ ሆኖ የታየው የንግድ ትርዒቱ መክፈቻ ላይ የንግድ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት አለመገኘት ነው፡፡ ንግድ ምክር ቤቱ በተከታታይ ባደረጋቸው የንግድ ትርዒቶች የመክፈቻ ሥርዓቱ ላይ በየወቅቱ በነበሩ የንግድ ሚኒስትሮችና በንግድ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት የሚከፈት ሲሆን፣ በዘንድሮው የንግድ ትርዒት ላይ ይህ አልተስተዋለም፡፡

 

Standard (Image)

መንግሥት ለአርብቶ አደሮች የመድን ሽፋን ድጎማ እንዲሰጥ ጥሪ ቀረበ በኦሮሚያ በድርቅ ሳቢያ ከብቶቻቸውን ያጡ 1000 አርብቶ አደሮች ካሳ ተቀብለዋል

$
0
0

 

በአገሪቱ በየጊዜው በሚከሰተው ድርቅ ሳቢያ የከብት ሀብቶቻቸውን እያጡ የሚገኙት አርብቶ አደሮች፣ የሚደርስባቸውን ጉዳት መቋቋም እንዲችሉ ታስቦ የተጀመረው የመድን ሽፋን በመላ አገሪቱ ማዳረስ እንዲቻል መንግሥት ድጋፍ እንዲሰጥ ተጠይቋል፡፡ በአገሪቱ ከ10 ሚሊዮን ያላነሱ አርብቶ አደሮች ቢኖሩም ለከብቶቻቸው የመድን ሽፋን ማግኘት የቻሉት ግን ከሚታሰበው በታች አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ናቸው፡፡

የካቲት 11 ቀን 2009 ዓ.ም. የኦሮሚያ ኢንሹራንስ ኩባንያ ከብቶቻቸውን ላጡና ጉዳት ለደረሰባቸው የቦረናና የምዕራብ ጉጂ ዞን አካባቢ ለሚገኙ 1,474 አርብቶ አደሮች የ1.6 ሚሊዮን ብር የመድን ካሳ ክፍያ ከፍሏል፡፡ በያቤሎ ከተማ በተደረገው ሥነ ሥርዓት ወቅት እንደተገለጸው፣ በክልሉ የከብት ሀብት የመድን ዋስትና ሽፋን የሚሰጠው ለረዥም ጊዜ በተሰበሰበ የአየር ሁኔታ መረጃና በተጠና ቀመር ላይ ተመሥርቶ ነው፡፡

በመሆኑም አርብቶ አደሮች አገልግሎቱን ለማግኘት በአንድ ዓመት ውስጥ ለሁለት የዝናብ አጠር የበጋ ወቅቶች ለከብት መኖ የሚያወጡትን ወጪ ከሰበታ እስከ 11 በመቶ የሚደርስ ግምት በዓረቦን መልክ መክፈል እንደሚጠበቅባቸው ለሪፖርተር ያብራሩት፣ በዓለማቀፉ የከብት ሀብት ምርምር ተቋም ረዳት ተመራማሪ አቶ ዋቆ ጎቡ ናቸው፡፡ በመሆኑም ረዥም ደረቃማ ወቅት ተብሎ በሚጠቀሰውና ከሰኔ እስከ መስከረም ባሉት አራት ወራት ውስጥ ለሚቆየው ጊዜ እንዲሁም ከየካቲት እስከ ሚያዝያ መጨረሻ ባሉት ሦስት ዝናብ አጠር በሆኑ ወራት ውስጥ የአርቶ አደሩ አካባቢ ሊደርስ የሚችለውን አደጋ ለመከላከል እንዲረዳ የመድን ሽፋን እየቀረበ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ደረቃማ በሆኑ ወቅቶች ከዚህ ቀደም ለሞቱ ከብቶች ምትክ እንዲሆን ተብሎ በሚሰጠው የመድን ሽፋን ፈንታ በሕዝቡ ጥያቄ ከብቶቹ ከማለቃቸው በፊት ለመኖ፣ ለውኃና ለሌሎች ግብዓቶች ማሟያ የሚውል እንዲሁም ቀድሞ መከላከል ላይ ያተኮረ የመድን ሽፋን እየተሰጠ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡ በኦሮሚያ ኢንሹራንስ ኩባንያ የከብት ሀብት ዋስትና ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት አቶ ጌታነህ ኢሬና እንዳብራሩት ከሆነ፣ የዓረቦን ክፍያው ለምሳሌ አንድ ግመል በሁለቱ ደረቃማ ወቅቶች የ5,000 ብር መኖ የሚፈልግ ሲሆን፣ ፍየልና በግ ደግሞ የ500 ብር መኖ ያስፈልጋቸዋል። አንድ በሬ ወይም ላም በአማካይ እስከ 3,000 ብር የሚገመት መኖ ሊያፈልጋቸው እንደሚችል ታሳቢ ተደርጎ፣ ቢዚያ ሥሌት መሠረት ክፍያው እንደሚጠየቅ አቶ ጌታነህ አብራርተዋል። በዚህም ሥሌት መሠረት ለአምስት በሬዎች ዋስትና መግዛት የሚፈልግ አርብቶ አደር የ3,000 ብርን ሰባት በመቶ ሲባዛ በአስምት በማድረግ በድምሩ 1,050 ብር ፕሪሚየም መክፈል ይጠበቅበታል ማለት ነው።

      በየአካባቢው ባሉ አሥር የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ወረዳዎች ውስጥ ለሚገኙ አርብቶ አደሮች የከብት ሀብት ዋስትና ሽፋን ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያስችላቸውን አገልግሎት ለማግኘት የቅድሚያ ክፍያ (የፕሪሚየም) መፈጸም ቢጠበቅባቸውም የመክፈል አቅም ስለሌላቸው፣ ሲፋ ኢትዮጵያ የተባለ አገር በቀል የበጎ አድራጎት ድርጅት ትሮኬር ከተባለ የውጭ ተቋም በሚያገኘው የገንዘብ ድጋፍ አማካይነት እስከ 35 በመቶ የሚደርሰውን የዓረቦን ክፍያ ከአሥሩ ወረዳዎች በሁለቱ ውስጥ ለሚገኙ አርብቶ አደሮች በድጎማ መልክ እየሸፈነላቸው እንደሚገኝ አቶ ጌታነህ  ጠቅሰዋል።  

አርብቶ አደሮቹ አንጡራ ሀብታቸው ለሆኑት ከብቶች ዋስትና ማግኘት መቻላቸው መሠረታዊ ጉዳይ መሆኑን የገለጹት አቶ ጌታነህ፣ ‹‹የክልልና የፈዴራል መንግሥታት እንደዚህ ዓይነት ድጎማ ማድረጉን ከግምት ውስጥ ቢያስገቡ የዋስትናው ተጠቃሚ አርብቶ አደሮችን ቁጥር በማሳደግና ከድርቅ አደጋ ተጋላጭነት ለመከላከል ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል፤›› በማለት ጥሪ አቅርበዋል፡፡

አቶ ዋቆም በዚህ ይስማማሉ፡፡ መንግሥት ለአርብቶ አደሮች የመድን ክፍያ ድጎማ ቢያቀርብ፣ ደጋግሞ እየተከሰተ የበርካታ እንስሳትን ሕይወት እየቀጠፈ የሚገኘውን ድርቅ በተሻለ አቅም ለመለካከል የሚችሉበት አቅም እንዲጠናከር ሊያግዛቸው እንደሚችል ጠቅሰዋል፡፡

የኬንያን ተሞክሮ የጠቀሱት አቶ ዋቆ፣ የኬንያ መንግሥት ባደረገው የመድን ሽፋን ድጎማ መሠረት 20 ሺሕ አርብቶ አደሮችን ተጠቃሚ ያደረገና 40 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ድጎማ በመስጠቱ እስከ አራት ከብቶች ያሏቸው አርብቶ አደሮች የመድን ሽፋኑን በነፃ ማግኘት እንዲችሉ አግዟቸዋል፡፡ ይህም ማለት ከአራት በላይ ከብቶች ያሏቸው በራሳቸው የመድን ሽፋን እንዲፈጽሙ የሚጠይቅ አሠራር ሲሆን፣ በኢትዮጵያም ይህ ቢተገበር በርካቶችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚቻል ጠቅሰዋል፡፡ በሰብል ላይ ለሚደርስ ጉዳት መንግሥት የመድን ሽፋን ድጎማ በመስጠቱ ይህ ዕድል ለአርብቶ አደሮችም እንዲደርሳቸው መደረጉ ድርቅን በመቋቋም ከብቶች ሳይሞቱ እንዲቆዩ ለማገዝ እንደሚረዳም አቶ ዋቆ አክለዋል፡፡

በከብቶች ላይ ለሚደርስ ጉዳት ካሳ ማግኘት የሚያስችል የመድን ሽፋን አገልግሎት ለኦሮሚያ አርብቶ አደሮች መስጠት የተጀመረው በ2004 ዓ.ም. በኦሮሚያ ኢንሹራንስ ኩባንያና በዓለም ዓቀፍ የከብት ሀብት ምርምር ተቋም ትብብር አማካይነት ነበር። የከብት ሀብት መድን ፕሮጀክት ሐሳብን ያመነጨው የምርምር ተቋሙ፣ ከአሜሪካው የጠፈር ምርምር ድርጅት (ናሳ) የሚያገኘውን የከባቢ አየር ሁኔታና የአየር ንብረት ለውጦችን የሚመለከቱ ዝርዝር መረጃዎች አጠናቅሮ ለኢንሹራንስ ኩባንያው በማቅረብና ጥናት በማካሄድ እየተሳተፈ ይገኛል።

       በሁለቱ ድርጅቶችና ተባባሪዎቻቸው አጋርነት የሚካሄደው የአካባቢና የአየር ንብረት ሁኔታን በመከታተል፣ ለውጦች ሲከሰቱ በከብቶች መኖ ይዘት፣ በመኖ እጥረትና በሌሎች ተጓዳኝ ሁኔታዎች ላይ የሚታዩትን ባህርያት ገምግሞ ሊደርስ የሚችለውን ጉዳት በመከላከል ላይ ተመሥርቶ የሚሰጠውን የመድን ዋስትና ከብቶቻቸው ከሞቱባቸው አርብቶ አደሮች ባሻገር ከብቶቻቸው ለከፍተኛ አደጋ የተጋልጡባቸውንም ተጠቃሚ እያደረገ ይገኛል። የዋስትና ሽፋኑም ላም፣ በሬ፣ ግመል፣ በግና ፍየልን የሚያካትት መሆኑን አቶ ጌታነህ ጨምረው ገልጸዋል።  ይህንኑ የዋስትና ዓይነት የበለጠ በማዘመንና በማስፋፋት በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ በመታገዝ ለማሻሻል ባለው ዕቅድ መሠረት፣ የኦሮሚያ ኢንሹራንስ ኩባንያ አገር በቀል ከሆነው ክፍያ ፋይናንሻል ቴክኖሎጂስ ኩባንያ ጋር በመተባበር የከብት ሀብት ዋስትናን ወደ ሌሎች አርብቶ አደር አካባቢዎች ለማስፋፋትና የበለጠ የተቀላጠፈ ለማድረግ እንቅስቃሴ ጀምሯል።   

      ካሳ የተከፈላቸውን 1,474 አርብቶ አደሮችን ጨምሮ በኦሮሚያ ክልል ቦረናና ምዕራብ ጉጂ ዞን የሚገኙ 4,588 አርብቶ አደሮች በዚህ የከብት ሀብት ዋስትና አገልግሎት ታቅፈዋል። የመድን ዋስትና አገልግሎቱ ከተጀመረ ጀምሮ ለአራተኛ ዙር ክፍያ ተፈጸመ ሲሆን፣ ዓላማውም ተጠቃሚ አርብቶ አደሮች ከደረሰባቸው ጉዳት በፍጥነት ማገገም እንዲችሉ ማገዝ እንደሆነ ተገልጿል፡፡

 

 

Standard (Image)

ደቡብ ግሎባል አዲስ ምክትል ፕሬዚዳንት በዕጩነት አቀረበ

$
0
0

በአገሪቱ ውስጥ ከሚንቀሳቀሱ የግል ባንኮች ይልቅ ምክትል ፕሬዚዳንት ሳይኖረው የዘለቀው ደቡብ ግሎባል ባንክ፣ የመጀመሪያውን ምክትል ፕሬዚዳንት ለመሾም በእጩነት ያቀረባቸውን ባለሙያ ተቀብሎ እንዲያፀድቅለት ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ጥያቄ ቀረበ፡፡

የደቡብ ግሎባል ባንክ ቦርድ ለባንኩ ምክትል ፕሬዚዳንትነት ያጫቸው የባንክ ባለሙያ፣ በአሁኑ ወቅት በዘመን ባንክ የዕውቀትና የምርምር ግኝት (ኢኖቬሽን) ሥራ ክፍል ዳይሬክተር በመሆን እያገለገሉ የሚገኙትን አቶ ተስፋዬ ቦሩን ነው፡፡

ላለፉት 13 ዓመታት በፋይናንስ ኢንዱስትሪው ውስጥ በተለያዩ የሥራ ዘርፎች ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ተስፋዬ፣ የደቡብ ግሎባል ባንክ ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ የቀረበላቸውን ጥያቄ ተቀብለዋል፡፡

በዚሁ መሠረት የደቡብ ግሎባል ባንክ የመጀመሪያው ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ ዕጩ አድርጎ ያቀረባቸውን የአቶ ተስፋዬን የሥራ ልምድ ማስረጃ ያጠናከረ ሰነድ ለብሔራዊ ባንክ አቅርቦ ምላሽ በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኝ ከባንኩ የተገኘው መረጃ ይጠቁማል፡፡

አቶ ተስፋዬ በፋይናንስ ኢንዲስትሪው ውስጥ በብሔራዊ ባንክ፣ በአቢሲኒያ ባንክ እንዲሁም በሕብረት ባንክ ውስጥ በተለያዩ የኃላፊነት መደቦች ውስጥ ማገልገላቸው ተገልጿል፡፡ በኢኮኖሚክስና በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን ሦስት ዲግሪዎች እንዳሏቸው የተጠሰቀ ሲሆን፣ የዶክትሬት ዲግሪያቸው ለመቀበል መቃረባቸውም ታውቋል፡፡ ይህ ሹመት በብሔራዊ ባንክ ከፀደቀላቸው፣ አቶ ተስፋዬ ወጣቱ ምክትል የባንክ ፕሬዚዳንት ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ አቶ ተስፋዬ 35ኛ ዓመታቸው ላይ እንደሚገኙ የግል ማኅደራቸው ይናገራል፡፡ በደቡብ ግሎባል ባንክ የምክትል ፕሬዚዳንቱ ቦታ ሲፀድቅላቸው የባንኩን የኦፕሬሽን ዘርፍ ይመራሉ ተብሏል፡፡

ደቡብ ግሎባል ባንክ ቆየት ብለው የባንክ ኢንዱስትሪውን ከተቀላቀሉት ሦስት ባንኮች አንዱ ነው፡፡ ከሰባት ሺሕ በላይ ባለአክሲዮኖች ያሉት ይህ ባንክ፣ በ2008 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ ከታክስ በፊት 68 ሚሊዮን ብር ማትረፉን መግለጹ ይታወሳል፡፡ 

Standard (Image)

መንገዶች ባለሥልጣን ከ21 ቢሊዮን ብር በላይ የሚጠይቁ የ20 መንገዶችን ጨረታ ይፋ አደረገ

$
0
0

የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን በ2009 ዓ.ም. ግንባታቸውን እንዲካሄድ በዕቅድ ከያዛቸው 69 ፕሮጀክቶች ውስጥ በአነስተኛ የዋጋ ግምት ከ21 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ሊጠይቁ ይችላሉ የተባሉ የ20 ፕሮጀክቶች ጨረታ ይፋ አደረገ፡፡

20ዎቹ መንገዶች በጠቅላላው የ1048 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያላቸው ሲሆን፣ በአንድ ጊዜ የ20 ፕሮጀክቶች የግንባታ ጨረታ ይፋ ሲደረግ የመጀመሪያው መሆኑም ተነግሯል፡፡

ከባለሥልጣኑ የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው፣ የዚህን ያህል የመንገድ ግንባታ ጨረታ በአንድ ጊዜ ያወጣው፣ በበጀት ዓመቱ በርካታ አዳዲስ መንገዶችን ለማስጀመር በማቀዱ ነው፡፡ በበጀት ዓመቱ ግንባታቸው እንዲጀመር የታሰቡ መንገዶችን ጨረታ ከፋፍሎ ከማውጣት ይልቅ በአንድ ላይ አሰባስቦ ማውጣቱ የተሻለ ስለሆነ በዚሁ መነሻ የተወሰደ ዕርምጃ እንደሆነም ባለሥልጣኑ አስታውቋል፡፡ 

ከ20ዎቹ የመንገድ ፕሮጀክቶች ውስጥ 12ቱ በዓለም አቀፍ ጨረታ መሥፈት ግንባታቸው የሚከናወን ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥ አብዛኛዎቹ ፕሮጀክቶች ከውጭ የፋይናንስ ተቋማት በሚገኝ ገንዘብ የሚገነቡ ናቸው፡፡ ቀሪዎቹ ስምንት ፕሮጀክቶች ደግሞ በኢትዮጵያ መንግሥት በሚመደብ በጀት እንደሚሠሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የጨረታ ሰነዱ እንደሚያመለክተው፣ በመንግሥት በጀት የሚከናወኑት ግንባታዎች የአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች ተሳታፊ እንደሚሆኑባቸው የሚጠበቁ ናቸው፡፡ በእነዚህ ፕሮጀክቶች ለሚሳተፉ አገር ውስጥ ተቋራጮች ሲባልም የጨረታ ሒደቶቹ  የሚጠይቋቸው መሥፈርቶች ዝቅ መደረጋቸውም ተመልክቷል፡፡

በመሆኑም የአገር ውስጥና የውጭ ተቋራጮች የተለያዩ የመወዳደሪያ መሥፈርት የተቀመጠላቸው ሲሆን፣ ለውድድር የሚቀርብበትም በዚሁ መስፈርቶች እንደተቀመጡላቸው ከሰነዱ ለመረዳት ተችሏል፡፡ ይኸውም ከአገሪቱ የግዥ ሥርዓት ጋር እንደሚጣጣም አመላካች ነው፡፡

ሁሉም የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክቶች ደረጃ አንድ ተቋራጮችን ብቻ የሚሳተፉ ሲሆን፣ እንደየመንገዱ ዓይነትም በጨረታ የሚሳተፉ ተቋራጮች ሊያሟሏቸው የሚገቡ ነጥቦች ተመልክተዋል፡፡ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት መጠናቸው ምን ያህል መሆን እንደሚገባው ተቀምጧል፡፡ የአገር ውስጥ ተጫራቾች ከ98 ሚሊዮን ብር እስከ 348 ሚሊዮን ብር የሚደርስ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት ሊኖራቸው እንደሚገባ በሰነዱ ሰፍሯል፡፡ ይህም ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ የነበራቸውን አማካይ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት መጠን የሚያሳይ ነው፡፡

የውጭ ተቋራጮችም እንደየመንገዱ ፕሮጀክት ዓይነት ከ245 ሚሊዮን ብር እስከ 959 ሚሊዮን ብር የሚደርስ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት ሊኖራቸው እንደሚገባ በጨረታ ሰነዱ ተመልክቷል፡፡ በዚህ ጨረታው ሒደት በሽርክና ተጣምሮ መወዳደር የሚቻል ሲሆን፣ ግንባታዎቹን ተጣምረው ለመሥራት የሚቀርቡ ተቋራጮችም ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ በአማካይ ከ184 ሚሊዮን እስከ 719 ሚሊዮን ብር የሚደርስ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት ማስገባታቸውን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ጨረታው ሌሎች መስፈርቶችንም አካቷል፡፡ ለአገር ውስጥ ተቋራጮች የተቀመጠው አማካይ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት መጠን በዝቷል የሚሉ ቅሬታዎች እየተደመጡ ነው፡፡ የውጭዎቹ ተቋራጮች በሁሉም ጨረታዎች ውስጥ እንዲሳተፉ መፍቀዱም ጨረታው የአገር ውስጥ ኮንትራክተሮችን የመሳተፍ ዕድል የሚያጣብብ ሊሆን  እንደሚችል ሥጋት የገባቸውም አልታጡም፡፡

ከተጠቀሱት 20 አዳዲስ የመንገድ ፕሮጀክቶች ውስጥ ግማሽ ያህሉ በቀጥታ ዲዛይንና የግንባታ ሥራቸው በጣምራ በተቋራጮች እንደሚሠሩ ባለሥልጣኑ አስታውቋል፡፡ ጨረታውም ይህንኑ የዲዛይንና የግንባታ ሥራዎች አጠቃሎ የያዘ ነው፡፡ የቀሪዎቹ ፕሮጀክቶች ዲዛይን ግን ባለሥልጣኑ በሚቀጥራቸው አማካሪ ድርጅቶች እንደሚዘጋጁ ታውቋል፡፡ ለእነዚህ መንገዶች የሚፈለጉት ተጫራቾች ለግንባታ ሥራ ብቻ የሚወዳደሩ ይሆናሉ፡፡

የመንገድ ፕሮጀክቶቹ በአማራ፣ በትግራይ፣ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላ፣ በቤንሻንጉል ጉምዝና በደቡብ ክልል የሚገነቡ ሲሆን፣ 20ዎቹም መንገዶች ከአምስት እስከ 117 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ርዝመት ይኖራቸዋል፡፡

ከእነዚህ መንገዶች ውስጥ ከፍተኛ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት እንዲያቀርቡ ተቋራጮች ከተጠየቁባቸው አንዱ የአዘዞ ጎንደር የመንገድ ግንባታ ነው፡፡ ለዚህ ፕሮጀክት የሚወዳደሩ የአገር ውስጥ ተጫራቾች ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ በአማካይ 355 ሚሊዮን ብር ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት ማስመዝገብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ የውጭ ተቋራጮች ከሆኑ 888 ሚሊዮን ብር የሚደርስ ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ለዚሁ ፕሮጀክት በጥምረት ለሚቀርቡ ተጫራቾች የተቀመጠው ዓመታዊ የገንዘብ ፍሰት መጠን 66 ሚሊዮን ብር እንደሚደርስ ታውቋል፡፡

የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን በቅርቡ እንዳስታወቀው፣ በ2009 ዓ.ም. ብቻ 18 ፕሮጀክቶችን እንዲገነቡለት በጨረታ ላሸነፉ ኩባንያዎች ሰጥቷል፡፡ አጠቃላይ የፕሮጀክት ዋጋቸው 13.7 ቢሊዮን ብር እንደሚገመትም ይጠበቃል፡፡

በአሁኑ ወቅት 29 ፕሮጀክቶች በጨረታና በግምገማ ሒደት ላይ ሲሆኑ፣ አሸናፊ ከሆኑ ተጫራቾች ጋር ስምምነት እንደሚፈረም ይጠበቃል፡፡ ከዚህም ባሻገር ባለሥልጣኑ የ97 የመንገድ ፕሮጀክቶችን የአዋጭነት፣ የዲዛይንና የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ እያካሄደ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

 

Standard (Image)

ለኢንቨስትመንት የተመቹ የለውጥ አሠራሮች ላይ መንግሥትና ተገልጋዮች ለየቅል ሆነዋል

$
0
0

በዓለም ከሚገኙ አገሮች ውስጥ 190 ያህሉን በማካተት በየዓመቱ ይፋ የሚደረገው የዓለም ባንክ ሪፖርት፣ በአገሮቹ መካከል ያለውን ምቹነትና ተስማሚነትን የሚለኩ አሥር ጠቋሚዎችን በመለየት ደረጃዎችን የሚያወጣው የዓለም ባንክ ‹‹ኤዝ ኦፍ ዱዊንግ ቢዝነስ›› የተሰኘው ታዋቂ ሪፖርት ለዓመታት ይፋ ሲደረግ ቆይቷል፡፡

ሪፖርቱ በአብዛኛው አገሮች ለንግድ አሠራርና ለኢንቨስትመንት መቀላጠፍ የሚከተሏቸውንና የሚያራምዷቸውን ሕጎች፣  የሚተገብሯቸውን አሠራሮች ወዘተ በመቃኘት ምቹ ስለመሆን አለመሆናቸው  በየዓመቱ ይፋ ያወጣል፡፡ በዚህ ሪፖርት መሠረት ኢትዮጵያ ለበርካታ ዓመታት ከአብዛኞቹ አገሮች ግርጌ ስትቀመጥ ቆይታለች፡፡ አገሪቱ ከምትወቅስባቸው መካከል በምትከተላቸው ገዳቢ ሕጎች ሳቢያ ወደ ንግድ ሥራም ሆነ ኢንቨስትመንት ለመግባት በርካቶች እንደሚቸገሩ፣ በአገሪቱ የተንዛዛ ቢሮክራሲ፣ በውሳኔና በደካማ የአገልግሎት አሰጣጥ ሳቢያ በርካታ ኢንቨስተሮችም ሆኑ ነጋዴዎች እንደሚጉላሉ ሪፖርቱ ሲጠቀስ ቆይቷል፡፡

የዓለም ባንክ በዋና ዋና መመዘኛ መስፈርትነት የሚጠቅሳቸው የሚከተሉት አሥር መለኪያዎች ናቸው፡፡ የንግድ ሥራ ለመጀመር የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎች፣ የግንባታ ፈቃድ በቀላሉ ለማግኘት መቻል፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ማግኘት፣ ንብረት ማስመዝገብ፣ ብድር ማግኘት መቻል፣ ለአነስተኛ ኢንቨስተሮች ከለላ መስጠት፣ የታክስ መክፈል መቻል፣ ድንበር ተሻጋሪ ንግድ ማካሄድ፣ የውል ስምምነቶችን መተግበር እንዲሁም የኪሳራ ዕወጃን ያለ ውጣውረድ መፍታት የሚሉ አሥር ዋና ዋና መለኪያዎች ኢትዮጵያን ጨምሮ 190 ያህል አገሮች ደረጃ ይወጣላቸዋል፡፡

ሪፖርቱ ዓለም አቀፍ ተደራሽነትና ተቀባይነትን ያተረፈ፣ በርካታ የውጭ ኩባንያዎችም ለእንቅስቃሴያቸው መመዘኛ ከሚያደርጓቸው ነጥቦች መካከል አንዱ በማድረግ የሚጠቅሱት ይህንኑ የዓለም ባንክ ሪፖርት ነው፡፡ የዚህ ዓመቱን የአገሮችን ደረጃ ይፋ ያደረገው የባንኩ ሪፖርት ኢትዮጵያ በ159ኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧታል፡፡ ከሰሃራ በታች ከሚገኙ አገሮችም 31ኛዋ ሆናለች ያለው የዓለም ባንክ፣ አገሪቱ ከወትሮው ይልቅ 12 ነጥቦችን ወደ ታች በማሽቆልቆል ይብሱን ወደታች እንደወረደች አስፍሯል፡፡

በመሆኑም አገሪቱ በኢንቨስትመንት መስህብነት ከሌሎች አገሮች ጋር ለመወዳደር ካሻት ከታች እስከ ላይ መሠረታዊ የለውጥ ሪፎርሞችን መተግበር እንደሚጠበቅባት አሳስቧል፡፡ በዚህ ምክንያት ይመስላል የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የአገሪቱን የአሠራር ማዕቀፎች ለማሻሻልና በባንኩ መለኪያ መሥፈርቶች መሠረት አገሪቱ የምታስመዘግባቸውን ዝቅተኛ ውጤቶች ለማሻሻል መንቀሳቀስ ጀምሯል፡፡

ከሌሎች መንግሥታዊ ተቋማት ይልቅ ለየት ባለ አደረጃጀትና የአመራር ኃይል መንቀሳቀስ የጀመረው ኮሚሽኑ፣ የተመቻቸ የንግድና የኢንቨስትመንት ከባቢ ሁኔታ ለመፍጠር የሚረዱትን የዓለም ባንክ መመዘኛዎችን በጥሩ ውጤት መተግበር የሚያስችሉ ማሻሻያዎችን ማድረግ ከጀመረ አንድ ዓመት አስቆጥሯል፡፡

በዚህ ዓመትም ሁለተኛውን ምዕራፍ የማሻሻያና የለውጥ እንቅስቃሴን የተመለከተ የምክክር መድረክ ሰሞኑን ጠርቶ ነበር፡፡ የካቲት 17 ቀን 2009 ዓ.ም. በጠራው መድረክም ከግንባታ ዘርፍ ጋር ተያያዥነት ያላቸው አካላት ታድመው ነበር፡፡ ኮሚሽኑ ከሥሩ መመዘኛዎች በስድስቱ ማለትም ንግድን ከታች ለመጀመር በሚያስችሉ አሠራሮች፣ በኮንስትራክሽን ፈቃድ አሰጣጥ፣ በንብረት ማስመዝገብ፣ በብድር አሰጣጥ፣ በድንበር ዘለል ንግድ እንዲሁም በታክስ አከፋፈል መስክ ያሉት መመዘኛዎች ላይ ቅድሚያ በመስጠት ለመንቀሳቀስ መነሳቱን ይፋ አድርጓል፡፡ በዚሁ መሠረትም ውይይቱ ተካሂዷል፡፡

እነዚህ መመዘኛዎች ላይ ጥሩ የሚባለውን ውጤት በማስመዝገብ በየደረጃውም ለውጥ በማምጣት በአራት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ ከዓለም 50 አገሮች ምርጧ አገር እንድትሆን የሚያስችል ‹‹ራዕይ 2020›› የተባለ እንቅስቃሴ ማድረግ መጀመሩን አስታውቋል፡፡ ይህ እንዲሳካም በያመቱ የ40 ከመቶ ለውጥ ማስመዝገብን መሠረት ያደረገ ውጤት እንዲመዘገብና የአገሪቱ አጠቃላይ ውጤትም አሁን ካለበት 159ኛ ወደ 34ኛ እንዲመጣ ማቀዱን ይፋ አድርጓል፡፡ ይህ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲፈጸም ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመሩትና በየጊዜው ስለ አፈጻጸሙ ሪፖርት የሚያቀርብላቸው አካል በኢንቨስትመንት ኮሚሽን በኩል እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ምክትል ኮሚሽነር አቶ አበበ አባየሁ ለሪፖርተር ጠቅሰዋል፡፡

በዓለም ባንክ መለኪያ መሠረት ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለውጦችን መተግበር ትፈልጋለች ለዚህም ሥር ነቀል ለውጦችን ማድረግ ያስፈልጋታል ያሉት አቶ አበበ፣ በመለኪያዎቹ ዝርዝር ነጥቦች ላይ የንግድ ማኅበረሰቡ ተገቢውን ግንዛቤ መጨበጥ እንዳለበትም ገልጸዋል፡፡

አገሪቱ ማስመዝገብ ስለምትፈልጋቸው ውጤቶችና በአሁኑ ወቅት ስለምትገኝበት ሁኔታ ከኮንስትራክሽን መስክ የተውጣጡና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውስጥ ከግንባታ ፈቃድ አሰጣጥ፣ ከቤቶች ልማት፣ ከውኃና ፍሳሽ አወጋገድ ጋር ግንኙነት ያላቸው አካላትና ሌሎችም ታድመው ነበር፡፡ የግል ተቋራጮች፣ መሐንዲሶች፣ አርክቴክቶችና የእነዚህ ባለሙያዎች ማኅበራትም ተገኝተው ነበር፡፡

ኮሚሽኑ ለውጥ ያስፈልጋቸዋል ያላቸው መለኪያዎች በአብዛኞቹ ተሳታፊዎች ዘንድ ተችትን አስተናግደዋል፡፡ ለአብነት የግንባታ ፈቃድ ማግኘትን በተመለከተው መለኪያ መሠረት እስካሁን ባለው አሠራር መሠረት 12 የተለያዩ ዝርዝር ሒደቶችን ማለፍ፣ ፈቃድ ለማግኘት 130 ቀናትን መጠበቅና ለዚህ ሒደት የሚያስፈልገው ወጪም በእያንዳንዱ ሒደት 18.7 በመቶ እንዲገመት በምሳሌ ተደግፎ ቀርቧል፡፡

በግንባታ ፈቃድ መስክ ይጠየቃሉ ከተባሉት 12 ሒደቶች መካከል የግንባታው ዕቅድ ከከተማው ማስተር ፕላን ጋር መስማማቱን ማረጋገጥ፣ ከተጎራባቾች በግንባታው ሥራ ስምምነት መገኘቱን ማረጋገጥና ይንንኑ ስምምነትም ለማዘጋጃ ቤት ማሳወቅ፣ የግንባታ ዕቅዱና የግንባታ ፈቃዱ የፀደቀባቸውን ማረጋገጫዎች ማግኘት የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡ በጠቅላላው የግንባታ ፈቃድ ለመግኘት የሚጠይቀውን 130 ቀናት ወደ 24 ቀናት ዝቅ የማድረግ ዕቅድ ይዞ ብቅ ማለቱን ኮሚሽኑን አስተችቶታል፡፡

አብዛኞቹ ይህንን ተግባራዊ ማድረግ ቀላል እንደማይሆን በአሁኑ ወቅት ከሚታየው የከተማው ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት ተችተዋል፡፡ በተለይ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን በመወከል የተገኙት አቶ ዮሐንስ ወልደገብርኤል፣ ከዚህም በማሻገር ኮሚሽኑ የወጠነው ለውጥ የዜጎች የንብረት ባለቤትነት መብትን የሚያረጋግጡ ሕግጋትን በመጋፋት ሊተገበር የታሰበ አካሄድ እንደሆነ በማብራራት ኮንነዋል፡፡

ይሁንና ኮሚሽኑ እነዚህን ለውጦች በአጭር ጊዜ ውስጥ በማስመዝገብ የኢንቨስትመንትና የንግድ አሠራር ሒደቶች ላይ የሚታዩ ቢሮክራሲዎችን የማስተካከልና የማቀላጠፍ ዓላማ እንዳለው አስታውቋል፡፡ ምክትል ኮሚሽነሩ አቶ አበበ እንደሚገልጹት፣ መሠረተ ልማቶችን ከመስፋፋት አኳያ ሲመዘን የአሠራር ሥርዓት ላይ የሚደረገው ማሻሻያ አነስተኛ ጫና ያለው ነው፡፡ ይኸውም አገሪቱ እንደ ኢነርጂ ያሉ ትልልቅ ግብዓቶችን አሟልታ መገኘቷ ቅድሚያ እንደሚሰጠው ለማመልከት ነው፡፡ ይሁንና የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ካቢኔ በዓለም ባንክ ማሻሻያዎች ላይ ጥብቅ ክትልል እንደሚያደርግና እንቅፋት በሚሆኑ ጉዳዮች ላይም አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጥበት በማድረግ ለውጦች እንዲደረጉ ግፊት እያደረገ መሆኑን አቶ አበበ ጠቅሰዋል፡፡

 

Standard (Image)

ከአዲስ አበባ ካርቱም የሚጓዙ አውቶቡሶች ሥራ ሊጀምሩ ነው

$
0
0

- ተጓዦች 60 ዶላር ይከፍላሉ 

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኢትዮጵያን ክልል አልፎ፣ ድንበር ተሻግሮ የመጀመሪያዎቹን የበረራ መዳረሻዎቹ ካደረጋቸው የአፍሪካ አገሮች መካከል ግብፅ፣ ጂቡቲና ሱዳን ተጠቃሾች ናቸው፡፡

አየር መንገዱ ድንበር ተሻጋሪ አገልግሎት ለመስጠት ወደ ካርቱም ያደረገው የመጀመሪያ በረራ ከ60 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡ በየብስ ትራንስፖርት ዘርፍ፣ በባቡር ድንበር የተሻገረው አገልግሎት፣ በአፄ ምኒልክ ዘመን አዲስ አበባን ከጂቡቲ ለማገናኘት አስችሏል፡፡  

ከእኒህ ትራንስፖርት አገልግሎቶች ባሻገር፣ በቅርቡ በመኪና ድንበር አቋራጭ የሕዝብ ማመላለስ አገልግሎትን በአዲስ አበባና በካርቱም ከተሞች መካከል ለማስጀመር የመጨረሻው ምዕራፍ ተጠናቋል፡፡ ከኢትዮጵያ ወገን የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጭ ኩባንያዎች ዝግጅታቸውን አጠናቀው መንገደኞችን ወደ ሁለቱ ከተሞች ማመላለስ የሚጀምሩበት ቀን ተቆርጧል፡፡ ከሁለት ሳምንት በኋላ እንደሚጀመርም ይጠበቃል፡፡ ከፌዴራል ትራንስፖርት ባለሥልጣን ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ የመጀመርያው የአዲስ - ካርቱም የአውቶብስ ትራንስፖርት አገልግሎት መጋቢት 2 ቀን 2009 ዓ.ም. በይፋ ይጀመራል፡፡

በሕዝብ ማመላለሻ አውቶብሶች የሚደረግ ድንበር ተሻጋሪ አገልግሎት የሆነው የአዲስ - ካርቱም ትራንስፖርት አሁን ለደረሰበት ደረጃ የበቃው ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ እንደሆነ የኢትዮ - ሱዳን የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ጥምር ኮሚቴ ሰብሳቢና የጎልደን ባስ ኩባንያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ወጋየሁ አራጋው ይገልጻሉ፡፡  

ሱዳንን ጨምሮ ሌሎች አጎራባች አገሮችን በየብስ ትራንስፖርት ለማስተሳሰር እንቅስቃሴ ከተጀመረ ከስምንት ዓመታት በላይ ተቆጥሯል፡፡ ይሁንና በተፈለገው ፍጥነት ዕቅዱን መተግበር ሳይቻል ቆይቷል፡፡ የኢትዮጵያ የየብስ ትራንስፖርት አቅራቢ ድርጅቶች ድንበር አቋራጭ አገልግሎት መስጠት እንዲጀምሩ ሐሳቡን በማመንጨት የሚጠቀሰው ሰላም ባስ አክሲዮን ማኅበር ነው፡፡ የኩባንያው የቀድሞ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ብርሃኑ ከበደ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ለዓመታት ቢዘገይም አገልግሎቱ ሊጀመር መቃረቡ ትልቅ ነገር ነው፡፡ አክሲዮን ማኅበሩ በአገር ውስጥ ከሚሰጠው አገልግሎት ባሻገር ድንበር ዘለል ትራንስፖርት የማቅረብ ውጥን ስለነበረው፣ ይህንኑ ዕቅዱን ለትራንስፖርት ባለሥልጣን አቅርቦ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡  

አገልግሎቱን ለመጀመር ከአጎራባች መንግሥታት ጋር ስምምነት ሊደረግባቸው የሚገቡ ጉዳዮች ተደማምረው ስላዘገዩት እንጂ፣ አገልግሎቱ አሁን ከሚጀመርበት ጊዜ ቀድሞ ሊጀመር ይችል እንደነበር አቶ ብርሃኑ አስረድተዋል፡፡

በዚህ የአገልግሎት ዘርፍ ሌሎች አጎራባች አገሮችንም ማካተት እንደሚቻል የሚገልጹት አቶ ብርሃኑ፣ ወደ ኬንያ፣ ሱማሌላንድና ጂቡቲ ለመጓዝ የሚያስችሉ ዕድሎች እንዳሉም ጠቅሰዋል፡፡ ከእነዚህ አገሮች ጋር ድርድሮች እየተካሄዱ እንደሚገኙም ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ የትራንስፖርት ድርጅቶች ወደ ሌሎች ጎረቤት አገሮች ለመጓዝ ዝግጁ መሆናቸው የሚገልጹት አቶ ወጋየሁ በበኩላቸው፣ የሚጠበቀው ከየአገሮቹ ጋር መፈረም ያለበት ስምምነት ነው ብለዋል፡፡

ለዓመታት ሲጠበቅ የነበረው ድንበር ዘለሉ የሕዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት አገልግሎት፣ ከሁለት ሳምንት በኋላ ሲጀመር የመጀመሪያውን ጉዞ የሚያደርገው አገልግሎቱን እንዲያቀርቡ ፈቃድ ካገኙ አራት ልዩ የትራንስፖርት አገልግሎት ድርጅቶች አንዱ በሆነው ዓባይ ባስ ነው፡፡

ከዓባይ ባስ በተጨማሪ ለድንበር አቋራጭ አገልግሎቱ ፈቃድ ያገኙት ጎልደን ባስ፣ ሰላም ባስና ኢትዮ ባስ የተባሉት ድርጅቶች መሆናቸውን የገለጹት ከጥምር ኮሚቴው የዓባይና የኢትዮ ባስ ተወካይ የሆኑት አቶ ካሳሁን አቡሐይ ናቸው፡፡

የመጀመሪያው ጉዞ በዓባይ አውቶብሶች እንዲካሄድ የተወሰነው አራቱ የትራንስፖርት ድርጅቶች ባካሔዱት የዕጣ ድልድል መሠረት እንደሆነ ታውቋል፡፡ ከዓባይ ባስ በመከተል ኢትዮ ባስ፣ ጎልደን ባስና ሰላም ባስ በየተራ እየተፈራረቁ ከአዲስ - ካርቱም የሕዝብ ማመላለስ አገልግሎቱን ለማቅረብ ተስማምተዋል፡፡ ለዚህም የጋራ ኮሚቴ አዋቅረው እየሠሩ እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡

1,490 ኪሎ ሜትር ርቀት ለሚሸፍነው የአዲስ - ካርቱም የጉዞ መስመር ታሪፉ ምን ያህል ይሁን? የሚለው ጥያቄ በሁለቱ አገሮች መካከል ውይይቶች ከተደረገበት በኋላ፣ ከዚህ ቀደም ለአንድ መስመር ጉዞ ብቻ 90 ዶላር እንዲከፈል ስምምነት ተደርጎ ነበር፡፡

ነገር ግን ከሁለት ሳምንት በፊት በሁለቱ አገሮች የትራንስፖርት ድርጅቶች መካከል በባህር ዳር ከተማ በተደረገ የጋራ ምክክር ቀድሞ የተተመነውንና በአንድ የሚከፈለውን የ90 ዶላር ታሪፍ ከልሰዋል፡፡ በመሆኑም ለጉዞ እንዲከፈል የተባለው 90 ዶላር ወደ 60 ዶላር ዝቅ እንዲል በመደረጉ፣ በዚህ ዋጋ መሠረት ተጓዦች ክፍያ ይፈጽማሉ ተብሏል፡፡ ክፍያው የቁርስ አገልግሎትን የሚያካትት ሲሆን፣ በተቀረው የጉዞ ወቅት የማደሪያና ሌሎች ወጨዎችን ተጓዦች በራሳቸው መሸፈን ይጠበቅባቸዋል፡፡

ቀድሞ የነበረው ዋጋ ማስተካከያ የተደረገበትን ምክንያት በተመለከተ ያነጋርናቸው አቶ ወጋየሁ እንደሚገልጹት፣ ዋጋው እንዲቀነስ ማድረጉ አግባብ ነበር፡፡ ምንም እንኳ የመጀመሪያው ታሪፍ ከወጣ ረጅም ጊዜ ቢቆይም፣ አዲሱ የታሪፍ ማሻሻያ ግን የወቅቱን የነዳጅ ዋጋ ታሳቢ ያደረገ እንደሆነም አብራርተዋል፡፡ አቶ ወጋየሁ እንደሚሉት፣ የቀደመው ታሪፍ በወጣበት ወቅት ‹‹የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ስለነበር የጉዞው ዋጋ 90 ዶላር ይሁን ተብሎ እስካሁን ድረስ በዚሁ ዋጋ ቆይቷል፡፡ አሁን ደግሞ ነዳጅ በመቀነሱ እንደገና የአዋጪነት ጥናት ተሠርቶ በባህር ዳሩ ስብሰባ 60 ዶላር እንዲሆን ተወስኗል፡፡››

ድንበር አቋራጭ የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎቱ የሚሰጠው ቪዛ ላላቸው ተሳፋሪዎች ነው፡፡ እንደ አቶ ካሳ ገለጻ፣ ከአዲስ አበባ ካርቱም የሚደረገው ጉዞ ሁለት ቀናት ይፈጃል፡፡ በመሆኑም ከአዲስ አበባ የተነሳው አውቶቡስ ጎንደር ከተማ አድሮ በማግሥቱ ካርቱም ይገባል፡፡ የመጀመሪያው ጉዞ ግን ስለአገልግሎቱ መጀመር የሚያበስሩ ሥርዓቶች ተካተውበት ጉዞው ሦስት ቀናት ይወስዳል ተብሏል፡፡

በሁለቱ መንግሥታት ስምምነት መሠረት በሱዳን በኩል አገልግሎቱን የሚሰጡት፣ በሱዳን የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ድርጅቶችን በማዕከል በሚያስተባብረውና ቻምበር ትራንስፖርት በተሰኘው ተቋም አማካይት የሚሰማሩ አውቶብሶች ናቸው፡፡

የትራንስፖርት አገልግሎቱ መጀመር የሁለቱን ጎረቤታም አገሮች ግንኙነት ለማጠናከር ጠቀሜታ እንዳለው የሚጠቅሱት አቶ ብርሃኑ፣ መንገደኞችም በአነስተኛ ዋጋ አገልግሎት እንዲያገኙ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል፡፡

አቶ ወጋየሁ በበኩላቸው የኢትዮ - ሱዳን የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት መጀመር በተለይ ከሱዳን ወደ ኢትዮጵያ ለሚመለሱ ዜጎች ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል፡፡ መመለስ የሚፈልጉ ዜጎች ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት ይጠቀሙበት የነበረው ትራንስፖርት መደበኛ አይደለም፡፡ በአብዛኛው በጭነት ተሽከርካሪዎች የሚጓጓዙና ከፍተኛ ወጪ ከማውጣታቸው ባሻገር ለእንግልት ተዳርገው ሲጓጓዙ የነበሩትን የሚያግዝ አገልግሎት ነው፡፡ በየኬላዎቹ ተጨማሪ ክፍያ የሚጠየቁ በመሆናቸው ጭምር በርካታ መጉላላት ይገጥማቸው የነበረ ሲሆን፣ አሁን ግን ኢትዮጵያውያን ሱዳን ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ በኩል ተገቢውን መረጃ በመያዝ በቀላሉ ተሳፍረው መገልገል እንደሚችሉ ይጠበቃል፡፡ የዚህ አገልግሎት መጀመር ሌላው ጠቀሜታ ከአውሮፕላን በተጓዳኝ አመቺ የትራንስፖርት አማራጭ ማስገኘቱ ነው፡፡ ለአውሮፕላን የሚከፈለውን ወጪ የማይችሉ ተጓዦች፣ ከአውሮፕላን ዋጋ ባነሰ እንዲገለገሉ ማስቻሉ የትራንስፖርቱን አማራጭነት ጠቀሜታ እንደሚያሳይ አቶ ወጋየሁ ገልጸዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በአውሮፕላን ካርቱም ደርሶ መልስ ለመጓዝ 13,700 ብር ይጠይቃል፡፡ ለአንድ ጉዞ ከ7,000 ብር በላይ እንደሚከፈል ያስታወሱት አቶ ወጋየሁ፣ በአውቶብስ ለመጓዝ ግን 60 ዶላር ወይም ከ1,500 ብር ያልበለጠ መሆኑ ጥሩ አማራጭ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ አቶ ካሳ በበኩላቸው የኢትዮጵያ የትራንስፖርት አገልግሎት ብቃት እንዲኖረው ከማገዙም በላይ የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች የውጭ ምንዛሪ ማስገኛ እንዲሆኑ የሚያስችላቸው እንደሆም ጠቅሰዋል፡፡

ከሱዳን ባሻገር ወደ ሌሎች አጎራባች አገሮች ለሚደረገው የትራንስፖርት እንቅስቃሴ በአገሮቹ መካከል የሚደረጉ ስምምነቶች ብቻም ሳይሆኑ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እስኪጎለብቱ መጠበቅ ግድ እየሆነ ነው፡፡  

የሪፖርተር ምንጮች እንደሚገልጹት፣ ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ ለሚዘረጋው ትራንስፖርት ሁለቱ አገሮች ከሚያደርጓቸው ስምምነቶች ባሻገር የተጀመረው የመንገድ ግንባታ መጠናቀቅ ይኖርበታል፡፡ ወደ ሱማሌላንዷ ሐርጌሳ ከተማ ለመዝቀለቅ የሚያበቃ ገበያ ቢኖርም፣ የመኪና መንገዱ ጉዳይ እልባት የሚፈልግ ነው፡፡ በአንዳንድ ወገኖች አስተያየት ወደ ሱዳን የሚረገው ጉዞ ቪዛ የሚጠይቅ መሆኑ አገልግሎቱን ለማቀላጠፍ እንቅፋት ሊሆን እንደሚችል ሥጋት ፈጥሯል፡፡ በመሆኑም መንግሥት ይህንን የሚያስቀር ስምምነት ማድረግ እንደሚኖርበት ተነግሯል፡፡ ወደ ኬንያ የሚደረገው ጉዞ ቢጀመር ተጓዦች ቪዛ ስለማይጠየቁ ከቪዛ ጋር በተያያዘ ሊፈጠሩ የሚሉች መስተጓጉሎች አይኖሩም፡፡ ከሱዳንም ጋር ያለ ቪዛ ዜጎቻቸው እንዲጓጓዙ የሚያስችል ስምምነት ማድረግ እንደሚገባም እየተገለጸ ነው፡፡

አራቱ የትራንስፖርት ድርጅቶች በጠቅላላው 96 አውቶብሶች አሏቸው፡፡ ሰላም ባስ 61፣ ጎልደን ባስ 15፣ ኢትዮ ባስ 13 እንዲሁም ዓባይ ባስ ሰባት አውቶብሶችን ገዝተዋል፡፡ እያንዳንዱ አውቶብስ 51 ሰው የመጫን አቅም አለው፡፡ ከአዲስ አበባ ካርቱም በቀጥታ ከሚደረገው ጉዞ ባሻገር፣ አውቶብሶቹ ተሳፋሪዎችን ከጎንደር፣ ከባህር ዳርና ከሌሎች ከተሞችም መጫን ተፈቅዶላቸዋል፡፡ ከአቶ ወጋየሁ ገለጻ ለመረዳት እንደተቻለው፣ ከጎንደር ተነስቶ ካርቱም ለመግባት 40 ዶላር ይጠይቃል፡፡ ከባህር ዳር ካርቱም ለሚገቡም 47 ዶላር እንዲከፍሉ ታሪፍ መውጣቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡  

Standard (Image)

ዱከም በ400 ሚሊዮን ብር የሚገነባ ግዙፍ የመዝናኛ ፓርክ ሊኖራት ነው

$
0
0

- የፕሮጀክቱ ባለቤት አሥር ባለአምስት ኮከብ ሆቴል የመገንባት ዕቅድ አላቸው

በአሜሪካ ካሊፎርኒያ ግዛት ውስጥ የተመሠረተው ዲዝኒላንድ ፓርክ፣ በአሁኑ ወቅት አሜሪካን ጨምሮ በሦስት አገሮች ወደ 11 ፓርኮች ይዞታነት ተስፋፍቶ ይገኛል፡፡ ፓሪስ፣ ሆንግ ኮንግ፣ ቶኪዮ እንዲሁም በቅርቡ ደግሞ ሻንጋሃይ የተቀላቀለቻቸው ትልልቅ ከተሞች የዲዝኒላንድ መዝናኛ ፓርኮች መገኛ ማዕከል በመሆን ይታወቃሉ፡፡ በእነዚህ ፓርኮች ዝነኛ የሆሊውድ ፊልሞችን ጨምሮ ትልልቅ የሙዚቃ ድግሶችን በማስተናገድ ይታወቃሉ፡፡

እንዲህ ያሉ መዝናኛ ፓርኮች ያሏቸውን ዘመናዊ የመዝናኛ ይዘት በማሟላት ተመጣጣኝ ደረጃ ያለው መዝናኛ ፓርክ በኢትዮጵያ ዕውን ለማድረግ እንቅስቃሴ የጀመረው ኩባንያ፣ በዱከም ከተማ በአሥር ሔክታር መሬት ላይ የሚንሰራፋ ፓርክ ለመገንባት መነሳቱን አስታውቋል፡፡ አለታላንድ ቢዝነስ ግሩፕ በተሰኘው ኩባንያ ሥር የሚመራው ወሊማ ሪዞርትስ ኤንድ አሚዩዝመንትስ የተባለው ድርጅት፣ ከሚያስተዳድራቸው አንዱ እንደሚሆን የሚጠበቀው ግዙፉ የመዝናኛ ፓርክ፣ ከ400 ሚሊዮን ብር ያላነሰ ፋይናንስ እንደሚጠይቅ የአለታላንድ ግሩፕ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሙሉቀን አሥራት ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ከአምስት ዓመታት ቀድሞ በዱከም ከተማ ገደራ ሆቴልን በ22 ሚሊዮን ብር በመግዛትና ከ12 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ በማድረግ ዕድሳት ሲያከናውን መቆየቱን የጠቀሱት አቶ ሙሉቀን፣ በዚህ ይዞታው ሥር የሚገኘውን ይህንን ሆቴል ጨምሮ ከኋላው በሚገኝ ቦታ ላይ እንደ ዲዝኒላንድ ዓይነት ግዙፍ የመዝናኛ ማዕከል የመገንባት ፍላጎት በመያዝ፣ ኩባንያው ለዱከም ከተማ አስተዳደር የቦታ ጥያቄ አቅርቦ ምላሽ እስኪሰጠው እየተጠባበቀ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

ለመዝናኛ ማዕከሉ ግንባታ ለልዩ ልዩ የውኃ መዝናኛዎችና ለአረንጓዴ ሥፍራ የሚውለው የሰባት ሔክታር መሬት ጥያቄ ምላሽ ካገኘ፣ ፕሮጀክቱ በሦስት ዓመት ተኩል ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ተገልጿል፡፡  እንደ አቶ ሙሉቀን ማብራሪያ እንዲህ ያለውን ግዙፍ መዝናኛ ማዕከል መገንባት ኢትዮጵያ የምታቀርባቸው የቱሪስት አገልግሎቶች የተሟሉ እንዲሆኑ ከማስቻል አልፈው፣ በምሥራቅ አፍሪካ የቱሪዝም ገበያ ጥሩ ተፎካካሪ እንድትሆን እንደሚያስችላት ጠቅሰዋል፡፡ መዝናኛ ፓርኩ ኮንፈረንስ ቱሪዝምን መሠረት ያደረገ ባለአምስት ኮከብ ሆቴል ግንባታን ጨምሮ ለኮንሰርት፣ ለልዩ ልዩ ስብሰባዎች የሚውል እንደ ሚሊኒየም ያለ ትልቅ አዳራሽ መገንባት በፓርኩ ዕቅድ ውስጥ የተካተቱ ሥራዎች መሆናቸውን አቶ ሙሉቀን አብራርተዋል፡፡

መዝናኛ ፓርኩ ከቤት ውስጥ ልዩ ልዩ መጫወቻዎች ባሻገር ከቤት ውጭ የሚካሄዱ አዳዲስ መጫዎቻዎችንም እንደሚያካትት ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሮለር ኮስተር፣ ፍላይግ ታወር፣ ስፔስ ሻት፣ ዎነደር ዊል የተባሉ በአየር ላይ የሚቀዝፉ እስከ አራት ኪሎ ሜትር የሚረዝሙ ልዩ ልዩ የጨዋታ መኪኖችን እንደሚያመጣ ይጠበቃል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የውኃ ትርዒቶችን አካቶ የኦሊምፒክ ደረጃ ያለው መዋኛ ገንዳ፣ የካምፕ አገልግሎትና የመሳሰሉትን መዝናኛዎች እንደሚያቀርብም ተብራርቷል፡፡

በሆቴልና ቱሪዝም መስክ መዝናኛን ጨምሮ የሚያንቀሳቀሰው አለታላንድ ቢዝነስ ግሩፕ፣ በቅርቡ ግንባታውን አጠናቆ በሐዋሳ ከተማ ሥራ ለማስጀመር የተሰናዳውን ሆቴል በ230 ሚሊዮን ብር እንዳጠናቀቀ አስታውቋል፡፡ ሮሪ የሚል መጠሪያ የተሰጠው ይህ ሆቴል፣ ካሉት 100 ክፍሎች ውስጥ 56ቱን ክፍሎች በደቡብ ክልል ውስጥ የሚገኙትን ብሔር ብሔረሰቦች በሚወክሉ ሥያሜዎች እንዲጠሩ ማድረጉንም ለመረዳት ተችሏል፡፡ ሆቴሉ ይህንን ጨምሮ ለሕፃናት የቤት ውስጥ መጫወቻ ቦታ በማዘጋጀት ማስተናገድ እንደጀመረም አስታውቋል፡፡

ከአንድ ወር በኋላ ሥራ መጀመሩን የሚያበስረው ይህንን ሆቴል ጨምሮ በአገሪቱ ባለአምስት ኮከብ ደረጃ ያላቸው አሥር ተጨማሪ ሆቴሎችን የመገንባት ዕቅድ እንዳላቸው የአለታላንድ ቢዝነስ ግሩፕ ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሀብታሙ ሲላ አስታውቀዋል፡፡

ከሆቴልና መዝናኛው ዘርፍ ባሻገር በማኑፋክቸሪንግ መስክም በተለይ በፕላስቲክ ኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚታወቀው አለታላንድ ቢዝነስ ግሩፕ፣ በዱከም ከተማ የኮስሞቲክስ ፋብሪካ በመገንባት ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡

በሐዋሳ ከተማ ሲገባ ትልቁና የመጀመሪያ የሆነውን ብረት ማቅለጫ ፋብሪካን ጨምሮ የፓስታና መኮረኒ ማምረቻ፣ በገላን ከተማ የወረቀት ፋብሪካ እንዲሁም በዱከም የውበት መጠበቂያ ኮስሜቲክሶችን የሚያመርት ፋብሪካ ግንባታዎች እየተካሄዱ ይገኛሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት የሁሉም ፋብሪካዎች ግንባታ በመገባደድ ላይ ሲሆን፣ የማሽን ተከላ እየተካሄደ እንደሚገኝም አቶ ሀብታሙ አብራርተዋል፡፡

በሐዋሳ ከተማ እየተገነባ የሚገኘው አለታላንድ የብረት ማቅለጫ ፋብሪካ ከ13 ሺሕ ካሬ ሜትር በላይ በሆነ ቦታ ላይ የሰፈረ ሲሆን፣ በዓመት 300 ሺሕ ቶን ብረት የማምረት አቅም እንዳለው ለማወቅ ተችሏል፡፡ ፋብሪካው ሥራ ሲጀምር ለ200 ሰዎች የሥራ ዕድል ያስገኛል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በክልሉ በዚህ ደረጃ የብረት ማቅለጫ ፋብሪካ ሲገነባ የመጀመሪያው እንደሆነና ይህ ፋብሪካ ለግንባታ የሚሆኑ ብረቶችን በደቡብ ክልል ማምረት መቻሉ ከሌሎች አካባቢዎች የሚጓጓዘውን መጠን እንዲቀንስ በማድረግ የግንባታ ሥራዎችን እንደሚያፋጥን አቶ ሀብታሙ ይናገራሉ፡፡ ይህ ፋብሪካ ከስምንት እስከ 24 ሚሊ ሜትር መጠን ያላቸውን የአርማታ ብረቶች በማምረት የክልሉን የብረታ ብረት ፍላጎት ከማሟላት ባሻገር ለሌሎች ገበያዎችም ሊያቀርብ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡ በሐዋሳ ከተማ የሚገነባው ሌላው ፕሮጀክት የፓስታና የዱቄት ፋብሪካ ነው፡፡ በ190 ሚሊዮን ብር ካፒታል የሚገነባው ይህ ፋብሪካ በ2010 ዓ.ም. ሥራ ይጀምራሉ ከተባሉት ውስጥ ሲመደብ፣ ከውጭ የሚገባውን የፓስታና የማካሮኒ መጠን ለመተካት እንደሚያግዝና ለ200 ሰዎችም የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ይጠበቃል፡፡

በገላን ከተማ በ10 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ በ80 ሚሊዮን ብር ካፒታል ግንባታው ተገባዶ እንደሌሎች ፋብሪካዎች ማሽን እየተገጠመለት የሚገኘው የወረቀት ፋብሪካ ነው፡፡ ይህ ፋብሪካ ለማንኛውም ዓይነት የሕትመት አገልግሎት የሚውል ወረቀት የሚያመርት ሲሆን፣ በዓመት ሰባት ሺሕ ቶን ያመርታል ተብሏል፡፡ ለ60 ሰዎች ቋሚ የሥራ ዕድል እንደሚሰጥም ይጠበቃል፡፡

አለታላንድ ግሩፕ እየገነባቸው ከሚገኙት አራተኛው የሆነው ለውበት መጠበቂያ የሚሆኑ ቅባቶች ማምረቻ ፋብሪካ ነው፡፡ በዚህ ዘርፍ ለውበት መጠበቂያነት ከሚውሉት ቅባቶች ውስጥ ከ90 በመቶ በላይ ከውጭ የሚገቡ በመሆናቸው፣ የፋብሪካው ግንባታ ሲጠናቀቅ በዚህ መስክ አስተዋጽኦ ያበረክታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ 80 ሚሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ በ12 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ አብዛኛው የፋብሪካው ግንባታ ተጠናቆ የኤሌክትሪክ ኃይል መስመር ዝርጋታ እንዲሁም የማሽን ተከላ እየተካሄበደት እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡ ሁሉም የአለታላንድ ግሩፕ ፋብሪካዎች በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ሥራ የሚጀምሩ ከሆነ፣ ከ540 በላይ በተለያየ የሥራ መስክ የሚሰማሩ ሠራተኞች ያስፈልጓቸዋል፡፡  

አቶ ሀብታሙ እንደሚናገሩት፣ ኩባንያው በአባታቸው የቡና ንግድ መነሻነት ቀስ በቀስ አሁን ለሚገኝበት ደረጃ የበቃ ሲሆን፣ ወደፊት የሚከፈቱትን ፋብሪካዎች ጨምሮ ሰባት ድርጅቶች በሥሩ የሚያስተዳድር ግሩፕ ኩባንያ እየሆነ መጥቷል፡፡ በንግድ፣ በእርሻ ሥራ፣ በፋብሪካ፣ በመዝናኛ እንዲሁም በአስመጪና ላኪነት ሥራ ላይ የሚሳተፉ ድርጅቶችንም ከወዲሁ በማስተዳደር ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል የሚያንሳቅሰው አለታላንድ ግሩፕ ከ20 ሺሕ በላይ ሠራተኞችን መቅጠር የሚችሉ ኩባንያዎችን እያስፋፋ እንደሚቀጥል ባለሀብቱ ጠቅሰዋል፡፡ 

Standard (Image)

አክሲዮን ኩባንያዎች የሚገዙበት አዲስ ረቂቅ ሕግ ለውይይት ሊቀርብ ነው

$
0
0

በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ለመሰማራት በአክሲዮን የሚቋቋሙና የተቋቋሙ ኩባንያዎች የሚገዙበት ይሆናል የተባለው አዲስ ረቂቅ ሕግ ለውይይት ሊቀርብ መሆኑ ተገለጸ፡፡

በሚቀጥሉት ሳምንታት በተከታትይ በቀጥታ ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር  ውይይት ይደረግበታል የተባለው ረቂቅ ሕግ፣ በንግድ ሚኒስቴር የተዘጋጀ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የንግድ ሚኒስቴር የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶችና የአክሲዮን ኩባንያዎች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ኑረዲን መሐመድ ለሪፖሪተር እንደገለጹት፣ በረቂቅ አዋጁ ላይ ውይይት እንዲያደርጉ የተመረጡት ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች፣ አክሲዮን ኩባንያዎችና የሕግ ባለሙያዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ አካላት ጋር ለየብቻ በሚደረገው ተከታታይ ውይይቶች  የሚገኙትን ግብአቶች በማከል ረቂቁን በማዳበር፤ የመጨረሻውን ረቂቅ ሕግ ለጠቅላይ አቃቢ ሕግ እንደሚላክ ከአቶ ኑረዲን ለመረዳት ተችሏል፡፡ ጠቅላይ አቃቤ ሕግም ወደ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲቀርብ በማድረግ ረቂቁ እንዲፀድቅ ይደረጋል፡፡

እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ ሕጉ በርካታ ችግሮች እየታዩበት ያለውን የአክሲዮን ኩባንያዎች ጉዳይና አንዳንድ የሕግ ክፍተቶችን ለመድፈን ያስችላል፡፡ አዲሱ ረቂቅ ሕግ አሁን ባንኮችና የኢንሹራንስ ኩባንያዎች ከሚገዙበት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሕግ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ይዘት እንዲኖረው ተደርጎ የተዘጋጀ ስለመሆኑም ተጠቁሟል፡፡

በተለይ የአክሲዮን ኩባንያዎቹን የሚመሩ የቦርድ አመራሮች ብቃትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የተለያዩ መስፈርቶችን ከመያዙም በላይ፣ በአንድ አክሲዮን ኩባንያ ውስጥ በአመራርነት ያለ ግለሰብ በሌላ አክሲዮን ኩባንያ ውስጥ በተመሳሳይ ኃላፊነት እንዳይገባ የሚከለክል አንቀጾችም ይኖሩታል፡፡

በአክሲዮን ኩባንያዎችም ሆነ በተመሳሳይ የንግድ ተቋማት ሥራ ጋር በተያያዘ በወንጀል የተጠየቀ ግለሰብ፣ በአክሲዮን ኩባንያዎቹ ውስጥ በቦርድ አመራርነት እንዳይመረጥ የሚያግዱ አንቀጾች እንደሚኖሩት የተጠቀሰ ሲሆን፣ እያንዳንዱ የቦርድ አባል የኋላ ታሪክ እንዲቀርብ የሚያስገድድ ይሆናል፡፡

ከዚህ ቀደም የአክሲዮን ኩባንያዎች በራሳቸው መንገድ የሚያካሂዳቸው ስብሰባዎች በአዲሱ ረቂቅ ሕግ አንድ ወጥ እንዲሆኑ የሚያግዙ አንቀጾች አሉ፡፡  አክሲዮን ኩባንያዎቹ ጠቅላላ ጉባዔዎች መቼ ማካሄድ እንዳለባቸውና ድንገተኛ ጉባዔዎችን እንዴት ማካሄድ እንደሚኖርባቸውና የቦርድ አባላት በምን ያህል ጊዜ መሰብሰብ እንዳለባቸው ጭምር የሚያመለክቱ ዝርዝር ሕግጋቶችን የያዘ ነው፡፡

   አንድ አክሲዮን ኩባንያ እንዴት መቋቋም እንዳለበትና ሲፈርስም እንዴት መፍረስ እንደሚኖርበት የሚያመላክቱ ዝርዝር ሕግጋቶችን የያዘው ይህ ረቂቅ፣ ከንግድ ሕጉ ጋር የተጣጣመ እንዲሆን ታስቦ የተሰናዳ ነው፡፡ እንዲሁም የንግድ ሕጉ ያሉበትን ክፍተት ይደፍናሉ የተባሉ አዳዲስ ድንጋጌዎችን አካትቷል፡፡

እያንዳንዱ የቦርድ አባል የሥልጣን ኃላፊነትና የሥራ ዘመንን በግልጽ የያዘ ነው የተባለው ረቂቅ ሕግ፣ የባለአክሲዮኖች ሥልጣን ምን ድረስ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ሌሎች የአክሲዮን ኩባንያዎችን እንቅስቃሴ ጤናማ ያደርጋሉ የተባሉ አንቀጾችን ይዟል ተብሏል፡፡ በረቂቅ አዋጁ ከተቀመጠው የኃላፊነት ገደብ የወጣ ወይም ሊያስጠይቅ የሚችል ወንጀል የሚፈጽም ተጠያቂ የሚሆንበትና ለፈጸመው ጥፋት ሊቀጣ የሚችልበት የገንዘብና የእሥራት መጠንንም ያካተተ ነው፡፡ ለአክሲዮን ኩባንያዎች ተብሎ የተሰናዳው ይህ ረቂቅ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ባንኮችን ከሚቆጣጠርበት ሕግ ጋር ተመሳሳይ እንዲሆን የተፈለገው የብሔራዊ ባንክ መቆጣጠሪያ ውጤታማ ሆኗል ከሚል ነው፡፡

በኢትዮጵያ በአክሲዮን ኩባንያ ደረጃ ከተቋቋሙ ኩባንያዎች ባንኮችና ኢንሹራንሶች አትራፊ ሆነው የዘለቁት፣ ጥብቅ ቁጥጥር የሚደረግበት ሕግ ስላለ ነው የሚል እምነትን ስላለ ነው፡፡

እስካሁን ባለው ሁኔታ በርካታ የአክሲዮን ኩባንያዎች ሲመሠረቱ የተጠያቂነት ወሰናቸው ውስን በመሆኑ፣ ጠበቅ ያለ ሕግ መውጣት በመታመኑ መሆኑን አቶ ኑረዲን ያስረዳሉ፡፡

በአሁኑ ወቅት በአክሲዮን ኩባንያዎች ደረጃ ፈቃድ ወስደው የተመዘገቡ 472 የሚሆኑ ኩባንያዎች አሉ፡፡ ነገር ግን እንቅስቃሴ ውስጥ ናቸው የሚባሉት ከ200 የማይበልጡ መሆናቸውንም ከንግድ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያስረዳል፡፡ 

Standard (Image)

ኔስሌ በኢትዮጵያ ፋብሪካ የመክፈት ሐሳብ እንዳለው ይፋ አደረገ

$
0
0

- አትሌት ኃይሌን የብራንድ አምባሳደር በማድረግ ሰየመ

የስዊዘርላንዱ ኔስሌ ኩባንያ፣ በኢትዮጵያ በወተት ማቀነባበር መስክ ፋብሪካ የመክፈት ፍላጎት እንዳለው አስታወቀ፡፡

በኢትዮጵያ ወደፊት እንደሚገነባ የሚጠበቀው የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ መቼ ዕውን ሊሆን እንደሚችል የሚወስኑት በአገሪቱ የሚገኘው የወተት ምርትና የአቅርቦት መጠን፣ የወተት ጥራት ደረጃና ጤንነት እንደሆኑ የገለጹት በኢኳቶሪያል አፍሪካ ቀጣና የኔስሌ የአፍሪካ ቀንድ ክላስተር ማናጀር የሆኑት አቶ ወሰንየለህ ፍቅሬ ናቸው፡፡

አቶ ወሰንየለህ ለሪፖርተር እንዳብራሩት ከሆነ፣ የኔስሌ የወደፊት የኢንቨስትመንት መዳረሻ ከሆኑ 20 አገሮች ውስጥ እንዲሁም ከአምስት አቅም ያላቸውና ምርጫው ካደረጋቸው አገሮች ተርታ ኢትዮጵያ ትካተታለች፡፡ ይሁንና የፋብሪካው ምሥረታ መቼ ሊሳካ እንደሚችል ገና ያልታወቀ ሲሆን፣ ከዚህ ይልቅ የዱቄት ወተት ምርቶቹን እዚሁ ለማሸግ የሚያበቁትን ዝግጅቶች በማድረግ ይህንን የሚያከናውን ፋብሪካ መመሥረቱ እንደማይቀር አቶ ወሰንየለህ አረጋግጠዋል፡፡  

የማሸጊያ ፋብሪካው በቅርቡ ዕውን ሊሆን እንደሚችል ቢገለጽም፣ በምን ያህል ጊዜ ውስጥና በምን ያህል ወጪ ለሚለው ምላሹ ወደፊት እንደሚታወቅ የጠቀሱት አቶ ወሰንየለህ፣ ከዚህ ባሻገር ግን ኔስሌ ኢትዮጵያን ጨምሮ በበርካታ አገሮች የሚታወቅበትን የኒዶ ዱቄት ወተት ምርት በአዲስ መልክ አሽጎ ማቅረቡን አስታውቀዋል፡፡ ይህንኑ በማስመልከት፣ አትሌት ኃይሌ ገብረ ሥላሴን የምርቱ አምባሳደር አድርጎ መሰየሙ ይፋ ተፈርጓል፡፡ ረቡዕ የካቲት 22 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሄደ ሥነ ሥርዓት ኃይሌ የኒዶ ወተት የብራንድ አምባሳደር ለመሆን የአንድ ዓመት ስምምነት መፈጸሙን ይፋ አድርጓል፡፡  

በመላው ዓለም ከ2,000 በላይ ብራንዶችን የሚያስተዳድረው ኔስሌ፣ ከ10 ሺሕ በላይ ምርቶችን በማምረት ከአንድ ቢሊዮን በላይ የምርት ሽያጭ የሚያከናውን የምግብና የመጠጥ አምራች ኩባንያ ነው፡፡ በአብዛኛው በውኃ፣ በወተት፣ በቡና እንዲሁም በልዩ ልዩ የበለፀጉ ምርቶቹ የሚታወቀው ኔስሌ፣ በኢትዮጵያ የውኃ ማዕድን መስክ ከአገር ውስጥ አምራቾች ጋር አብሮ ለመሥራት መስማማቱ ይታወሳል፡፡

ከኔስሌ ባሻገር ከቶታል እንዲሁም ከዜድቲኢ ጋር በተመሳሳይ መልኩ ከሌሎችም ልዩ ልዩ ኩባንያዎች ጋር የብራንድ አምባሳደር በመሆን በማስታወቂያ ሥራ እየተሳተፈ የሚገኘው አትሌት ኃይሌ ገብረ ሥላሴ፣ ኒዶን ለማስተዋወቅ ምን ያህል እንደተከፈለው ከመናገር ተቆጥቧል፡፡ ገንዘቡን መግለጽ ለሥራው መበላሸት አስተዋጽኦ ሊያደርግ እንደሚችልም ያምናል፡፡

ይሁንና ከዚህ ቀደም በ100 ሺሕ ዶላር ክፍያ የጆኒ ዎከር ዊስኪን ለማስተዋወቅ ያደረገው ስምምነት ትችትን እንዳስከተለበት ይታወሳል፡፡ ይህንኑ ያስታወሰው አትሌት ኃይሌ፣ የደረሰበት ወቀሳ የእሱን የሥራ ድርሻና ያደረገውን ስምምነት ካለመረዳት የመነጨ እንደነበር ገልጿል፡፡ ሆኖም ከስፖርታዊ ሰብዕናው በተጻረረ መልኩ መጠጥ ማስተዋወቁ ነበር ለኃይሌ ትችትን ያስከተለበት፡፡

ምንም እንኳ በማስታወቂያ ሥራዎች ውስጥ እየተሳተፈ ቢሆንም አትሌት ኃይሌ፣ በርካታ ቢዝነሶችን በማንቀሳቀስ ትልቅ የኢንቨስትመንት ካፒታል መገንባት የቻለ ሰው ለመሆን በቅቷል፡፡ በሆቴል መስክ የሚያስተዳድራቸው ሪዞርቶች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በአስመጪነት መስክም ከጃፓኑ ሃዩንዳይ ኩባንያ የሚያስመጣቸውን ልዩ ልዩ ተሽከርካሪዎችን የሚያከፋፍለውን ማራቶን ሞተርስ ኩባንያ መሥርቷል፡፡ የማር ምርት ወደ ውጭ በመላክ ላይ የጀመረውን የእርሻ ኢንቨስትመንትም ወደ ቡና በማስፋፋት ሰፊ የቡና እርሻ መሬት መግዛቱም ይታወቃል፡፡  

 

 

 

Standard (Image)

ብዙ መሻሻሎችን የጠቆመው የሶሺዮ ኢኮኖሚክ የዳሰሳ ጥናት

$
0
0

ከዓለም ባንክና ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ጋር በመተባበር የተሰናዳው የማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤንጀሲ ሪፖርት፣ በግብርና የሚተዳደረውን ሕዝብ የኑሮ ደረጃ ለመለካት ባለፈው ዓመት የተደረጉ ጥናቶችን አጠቃሎ ያቀረበ ሲሆን፣ የጥናቱ ውጤቶችም በቅርቡ ይፋ ተደርገው ነበር፡፡

በዓለም ባንክ የኑሮ ደረጃ መለኪያ ጥናት መሠረት፣ ለሦስተኛ ጊዜ በኢትዮጵያ የተደረገው የሶሺዮ ኢኮኖሚክ የዳሰሳ ጥናት፣ ከአምስት ሺሕ ያላነሱ ቤተሰቦችን በናሙናነት በማካተት ከቤተሰብ አባላት ብዛት እስከ ባንክ ቁጠባ፣ ብድርን አካቶ እስከ መድን ዋስትና ተጠቃሚነት ድረስ ያሉትን ልዩ ልዩ መለኪያዎች አካቷል፡፡

በዚሁ መሠረትም አማካይ የቤተሰብ አባላት ብዛት በገጠራማው የአገሪቱ ክፍሎች ከአምስት በላይ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ በአነስተኛ ከተሞች ከአራት በላይ ሲሆን፣ በትልልቅ ከተሞችም ከሦስት በላይ የቤሰተብ አባላት በአንድ ላይ እንደሚኖሩ ጥናቱ ይጠቁማል፡፡

በጥናቱ መሠረት የአገሪቱ የቤተሰብ ጥገኛ አባላት አማካይ ብዛት 88 በመቶ እንደሆነ ሲያመላክት፣ በገጠራማው የአገሪቱ ክፍል የጥገኛ አባላቱ ብዛት መቶ በመቶ እንደሚደርስ ያሳያል፡፡ በከተሞች ከሚኖሩ ቤተሰቦች ውስጥ የጥገኛ አባላት ብዛት 48 በመቶ እንደሚገመት ታይቷል፡፡ ከዚህ ባሻገር በትምህርት መስክ ጥናቱ ከአምስት ዓመታቸው ጀምሮ ያሉና ወደ ትምህርት ገበታ የተቃረቡትን ሰዎችን ያካተተ ሲሆን፣ በዚህ መሠረት በየትኛውም የአገሪቱ ቋንቋ ማንበብና መጻፍ የሚችሉ ወንዶች ብዛት 64 በመቶ መድረሱ ሲጠቀስ፣ የሴቶች ቁጥር ግን 48 በመቶ ላይ እንደሚገኝ ያሳያል፡፡ ይህ የትምህርት ደረጃ ማንበብና መጻፍን መሠረት ያድርግ እንጂ በጥናቱ መሠረት ዕድሜያቸው ከሰባት እስከ 18 ዓመት የሆናቸው 30 በመቶ ወንዶችና ሴቶች በትምህርት ገበታ ላይ እንደሚገኙ ተመልክቷል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ግን 64 በመቶው በመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ ከስድስት በመቶ በታች ያነሱትን ግን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ የሚገኙ መሆናቸውም ታውቋል፡፡ ጥናቱ በአገሪቱ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ምን ያህል አነስተኛ ሽፋን እንዳለው አመላካች ውጤት አቅርቧል፡፡

ከጤና አኳያ አገሪቱ ሶሺዮ አኮኖሚያዊ ጥናት እንደሚያሳየው፣ በጠቅላላው የጤና አጠባበቅ ተጠቃሚነት ሽፋን፣ በተለይም ቅድመ ክትትልና ምርመራን መሠረት በማድረግ በተደረገው የዳሰሳ ጥናት መሠረት የወንዶች ቁጥር ስምንት በመቶ ሲሆን፣ የሴቶች 11 በመቶ ላይ ይገኛል፡፡ ይህም ቅድመ ክትትልና ምርመራ የማድረግ ልማድ በአገሪቱ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ስለመገኘቱ ፍንጭ የሚሰጥ ውጤት ሆኖ ይገኛል፡፡

በሌላ በኩል በሕፃናት ሕክምና መስክ እንደታየው ከሆነ፣ አብዛኞቹ በገጠር የሚኖሩ ሕፃናት በከተማ ከሚኖሩት ይልቅ ለተመጣጠነ ምግብ እጥረት የተጋለጡ ሆነው መገኘታቸው በጥናቱ ውጤቱ ከተጠቀሱት መካከል አንዱ ሲሆን፣ በተለይ በጠቅላላ በአገሪቱ የታየው የሕፃናት መቀንጨር፣ አነስተኛ ክብደት መጠንና የመሳሰሉትን መሠረት በማድረግ በተደረገው ጥናት መሠረት 42 በመቶው የአገሪቱ ሕፃናት ለመቀንጨር ችግር ተዳርገዋል፡፡ ክብደታቸው ከተገቢው በታች የሆኑ ሕፃናት ብዛትም ከጠቅላላው አገሪቱ ሕፃናት ቁጥር አኳያ 24 በመቶውን ይዘዋል፡፡

በአገሪቱ ከሚኖሩ ቤተሰቦች ውስጥ 80 በመቶው በገዛ ራሳቸው ቤቶች ውስጥ እንደሚኖሩ አመላካች ጥናቱ ሲያሳይ፣ የተቀሩት ግን በኪራይና በሌሎች አማራጮች በቀረቡላቸው ቤቶች ውስጥ እንደሚኖሩ ይጠቁማል፡፡ ይህም ሆኖ አብዛኞቹ ቤቶች ለመኖሪያነት በማይመቹ አካባቢዎች የተቸመቸሙ፣ ወለልና ክዳናቸው፣ ግድግዳና ማገራቸው ለኑሮ ተስማሚ ባልሆኑ አሠራሮች የተዋቀሩ ሆነው ተገኝተዋል፡፡

በግብርና አኳያም የሶሺዮ ኢኮኖሚክ የዳሰሳ ጥናቱ እንደሚያሳየው የሰብልና የከብት እርባታ ሥራዎች በአብዛኛው በገጠሩ ክፍል የሚዘወተሩ የመተዳደሪያ ሥራዎች ናቸው፡፡ 98 በመቶው ሕዝብ በእነዚህ ሥራዎች ተሰማርቷል፡፡ በአነስተኛ ከተሞች ከሚኖረው ሕዝብ ውስጥ 64 በመቶው በሰብል ምርትና በከብት እርባታ ይተዳደራል፡፡ ይሁንና በአማካይ አንድ አባወራ የሚተዳደርበት የግብርና መሬት ከ1.4 ሔክታር ያነሰ ስፋት እንዳለውም ታውቋል፡፡

በፍጆታ፣ በልዩ ልዩ ወጪዎች፣ በምግብ ዋስትና እንዲሁም በአደጋ ክስተትና መልሶ መቋቋም በመቻል ረገድ ያሉትን ክንውኖች በተመለከተ ጥናቱ እንዳሳየው፣ በተለይ ጥራጥሬ 90 በመቶ የሚሆነውን የቤተሰብ የምግብ ፍጆታ ይሸፍናል፡፡ ለአልባሳትና ለመጫሚያ የሚወጣው ወጪም ከሌሎች ምግብ ነክ ካልሆኑ ወጪዎች ይልቅ ትልቁን ድርሻ እንደሚይዝ በጥናቱ ተመልክቷል፡፡ በአብዛኛው የገጠሩ ክፍል ለሳሙና፣ ለላምባ፣ ለማገዶ እንጨት፣ ለከሰል፣ ለትራንስፖርት ታክስ፣ ለመሬት ግብርና ለሌሎችም የሚያወጣቸው ወጪዎች ቦታ ይሰጣቸዋል፡፡ ይህም ሆኖ በከተማ የሚኖረው ሕዝብ ከገጠሩ ይልቅ አብዛኞቹን ወጪዎች በማውጣት፣ ለፍጆታዎችም ትልቁን ድርሻ በመያዝ ተመድቧል፡፡

የምግብ አቅርቦት ወቅታዊነት እንደሚታይበት ያመላከተው ይህ ጥናት፣ በተለይ ከመጋቢት እስከ ጥቅምት ያለው ጊዜ የምግብ እጥረት የሚታይበት የእህል መዝሪያ ወቅት ሲሆን፣ በተለይ የገጠሩ ክፍል ለምግብ እጥረት ከሚጋለጥባቸው ወቅቶች ውስጥ እነዚህ ወራት እንደሚያመዝኑ ተጠቅሷል፡፡ ከዚህ ባሻገር በቤተሰብ ላይ የሚደርሰው አደጋ ወይም ጉዳት የሚባባሰው በቤተሰብ አባላት ላይ ሕመም ሲከሰት፣ ድርቅ ሲመታቸው፣ አለያም የምግብ ሸቀጦች ዋጋ ሲንር እንደሆነ ጥናቱ ጠቅሶ፣ እንዲህ ያሉ ነገሮች የቤተሰብ ጥሪትን በማሟጠጥ ለችግር የሚያጋልጡ፣ ከብቶቻቸውን እንዲሸጡ የሚያስገድዱ ችግሮች ሆነዋል፡፡

በፋይናንስ ረገድ በተለይ በባንክ አገልግሎት እንዲሁም በመድን ሽፋን አኳያ በተደረገው ጥናት መሠረት በአገሪቱ መደበኛ የፋይናንስ ተቋማት ተጠቃሚ የሆኑ ሰዎች ብዛት 22 በመቶ ብቻ ናቸው፡፡ ይህም ሆኖ የመንግሥት ባንኮችና አነስተኛ የገንዘብ አቅርቦት የሚሰጡ ድርጅቶች ከፍተኛውን የፋይናንስ አገልግሎት የሚሰጡ ሆነው ሲገኙ፣ ለቁጠባም ትልቁን ድርሻ የሚይዙት እነዚሁ ድርጅቶች ሆነዋል፡፡ 32 በመቶ ግለሰቦችና 48 በመቶ ቤተሰቦች እንደየአቅማቸው የቁጠባ ልማድ እንዳላቸው ተመዝግቧል፡፡ ይሁንና በአገር አቀፍ ደረጃ 600 ብር ለመቆጠብ አቅም ያላቸው ሰዎች ብዛት ከ30 በመቶ ያልበለጠ ሆኗል፡፡

በጠቅላላው በአብዛኛው የጥናቱ መለኪያዎች መሠረት አገሪቱ የምትገኝበት የሶሺዮ ኢኮኖሚክ የዳሰሳ ጥናት፣ ብዙ ክፍቶች እንደሚታዩ አመላካች ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ጥናቱ ባለፈው ዓመት ውስጥ የነበሩትን ክንውኖች ያስቃኘ ሲሆን፣ ከጥናቱ ውጤት የታየው አፈጻጸም ዝቅተኛም ቢሆን መላ አገሪቱን የሚወክል ነው ለማለት በጥናቱ ለናሙና የተጠቀሱት ሰዎች ብዛት አብዛኛውን ሥዕል ሊያሳይ እንደማይችል በጥናቱ ተጠቅሷል፡፡

 

 

Standard (Image)

በውጭ ዜጎች የተያዙ የባንኮችና የኢንሹራንስ ኩባንያዎች አክሲዮኖች ጨረታ ሁለት ገጽታ

$
0
0

የውጭ ዜግነት ባላቸው ኢትዮጵያውያን ተይዘው የቆዩ ናቸው የተባሉ የባንክና የኢንሹራንስ ኩባንያዎች አክሲዮኖች በግልጽ ጨረታ እንዲሸጡ ከተወሰነ ወዲህ ኩባንያዎቹ አክሲዮኖችን በመሸጥ ላይ ናቸው፡፡

እስካሁን ይፋ ከተደረጉ መረጃዎች አዋሽና ኅብረት ባንኮች በውጭ ዜግነት የተያዙ ናቸው የተባሉ አክሲዮኖችን የሽያጭ ጨረታ አካሂደዋል፡፡ ከ340 ሺሕ በላይ አክሲዮኖችን ለሽያጭ ያቀረበው ኅብረት ባንክ ባለፈው ማክሰኞ ባደረገው ጨረታ፣ ተጫራቾች አንድ መቶ ብር ዋጋ ላለው አክሲዮን እስከ 1,700 ብር መስጠታቸውን ከባንኩ ያገኘነው መረጃ ያስረዳል፡፡ ኅብረት ባንክ ለጨረታ አቅርቧቸው የነበሩት የአክሲዮኖች መጠን ከ34.1 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው ናቸው፡፡

አዋሽ ባንክ ደግሞ በአራት ተከታታይ ጨረታዎች የ216 የውጭ ዜግነት የያዙ ባለአክሲዮኖችን ሽያጭ ያጠናቀቀ ሲሆን፣ በጨረታው 1,000 ብር ዋጋ ያለውን አንድ አክሲዮን እስከ 20,100 ብር ድረስ ሽጧል፡፡ ባንኩ 82 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸውን አክሲዮኖች በጠቅላላ ከ150 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ዋጋ መሸጡን ለማወቅ ተችሏል፡፡

አዋሽ ባንክ ከ82 ሺሕ በላይ አክሲዮኖች ውስጥ ለ328 አክሲዮኖች ብቻ ተጫራች ባለመቅረቡ ሳይሸጣቸው ቢቀርም፣ ከቀረቡት የአክሲዮን ሽያጭ የተገኘውን ትርፍ ለመንግሥት ገቢ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ኅብረት ባንክ በመጀመሪያው ዙር ካቀረባቸው ከ340 ሺሕ አክሲዮኖች መካከል ተጫራች ቀርቦባቸው የሸጣቸው ከ100 ሺሕ በላይ አክሲዮኖች ሲሆኑ፣ ተጫራች ያልቀረበባቸው ላይ ድጋሚ ለጨረታ እንደሚያቀርባቸው ከባንኩ የተገኘ መረጃ ያስረዳል፡፡

የአዋሽ ባንክም 328 አክሲዮኖች በድጋሚ ለተጫራች ይቀርባሉ፡፡ እስካሁን ከተካሄዱ ጨረታዎች አንዳንድ ተጫራቾች ያቀረቡት ዋጋ የኢንዱስትሪውን ገበያ ያላመላከተ ሆኖ ተገኝቷል ተብሏል፡፡ ያነጋገርናቸው አንድ የባንክ ባለሙያ 1,000 ብር ዋጋ ላለው አንድ አክሲዮን 14,000 ብር 17,000 ብርና 20,000 ብር መስጠቱ ስሰማ ግር ብሎኝ ነበር ይላሉ፡፡ ለአንድ አክሲዮን የዚህን ያህል ዋጋ መሰጠቱ ተገቢ ነው ብለው አያምኑም፡፡ 2,000 ብር ዋጋ ያላቸውን ሁለት አክሲዮኖች በ28 ሺሕ ብር በመግዛት የአክሲዮኖቹ ባለቤት ለመሆን መፈለግ፣ ምን ዓይነት ጥቅም ለማግኘት አስበው እንደሆነ ግልጽ እንዳልሆነላቸውም ይገልጻሉ፡፡

የእኚህን የባንክ ባለሙያ አመለካከት የሚጋሩት የኅብረት ባንክ ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉ በበኩላቸው፣ 1,000 ብር ዋጋ ላለው አክሲዮን 20 ሺሕ ብር ድረስ መስጠቱ ጤናማ የሆነ የመወዳደሪያ ዋጋ ነው ብለው አያምኑም፡፡

ሁለት አክሲዮኖችን በ28 ሺሕ ብር ለመግዛት የቀረቡ ተጫራቾች 28 ሺሕ ብሩን በምን ያህል ጊዜ እመልሳለሁ ብለው ያሰሉ አይመስሉም ይላሉ፡፡ ምክንያታቸው ደግሞ ሁለቱ አክሲዮኖች በየዓመቱ ሊያስገኙ የሚችሉት ትርፍ በየትኛውም መለኪያ ለአክሲዮን ግዥው ያዋሉትን ገንዘብ በአጭር ጊዜ ለመመለስ የማያስችል በመሆኑ ነው፡፡  

አሁን ባለው የአገሪቱ የባንክ ኢንዱስትሪ አማካይ ዓመታዊ የትርፍ ድርሻ 40 በመቶ አካባቢ ነው፡፡ ስለዚህ በ14,000 ብር የተገዛ አንድ አክሲዮን ግዥ የተፈጸመበትን ገንዘብ ለመመለስ ቢያንስ ከ15 እና 20 ዓመታት በላይ ይፈጃል፡፡ ስለዚህ እንዲህ ባለ የተጋነነ ዋጋ መገዛቱ ምክንያታዊ ያለመሆኑን ያስረዳሉ፡፡ እስካሁን የባንክ አክሲዮኖች ሽያጭ ትላልቅ በሚባሉ ባንኮች የአንድ የአክሲዮን ዋጋ ላይ ከ25 እስከ 75 በመቶ ዋጋ በመጨመር ይገዙ ነበር፡፡ በዚህ ዋጋ የተገዛ አክሲዮን ያወጣውን ወጪ ከአምስት እስከ ሰባት ዓመት ሊመልስ ይችል እንደነበር የሚያስታውሱት አቶ ኢየሱስ ወርቅ፣ አሁን በአንዳንድ ወገኖች እየተሰጠ ያለው ዋጋ ግን ትርፍ ለማግኘት እስከ  20 ዓመት የሚያስጠብቅ ከሆነ የኢንቨስትመንቱ ትርጉም አልባ ይሆናል የሚልም ሥጋት አላቸው፡፡ በእርግጥ በዚህን ያህል ዋጋ የተገዙ አክሲዮኖች ቁጥር አነስተኛ ቢሆኑም፣ አሁን ያለውን የባንኮች የአክሲዮን ገበያ ዋጋ ያዛባ ነው የሚል እምነታቸውንም አክለዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ባንኮች በሚያካሂዷቸው ጨረታዎች አሁን በኅብረትና በአዋሽ ባንኮች ላይ የታየውን ያህል የተጋነነ ዋጋ ይሰጣል የሚል እምነት የሌላቸውም አሉ፡፡

እንዳነጋገርናቸው የባንክና የኢንሹራንስ ባለሙያዎች ገለጻ የአንዳንድ ባንኮች የአክሲዮን ሽያጭ የተጋነነ ዋጋ የሚቀርብበት አይሆንም፡፡ ለዚህም እንደምክንያት የሚያቀርቡት ኩባንያዎች ካፒታላቸውን ለማሳደግ መደበኛ የአክሲዮን ሽያጭ እያካሄዱ በመሆናቸው ነው፡፡

መደበኛ የአክሲዮን ሽያጩ የሚያስከፍሉት ፕሪሚየር ከ20 በመቶ ያልበለጠ በመሆኑ፣ በውጭ ዜግነት የተያዙ አክሲዮኖች ሽያጫቸውም በመደበኛ የአክሲዮን ሽያጭ ከሚያስከፍሉት ያነሰ ሊሆን ስለሚችል ነው ይላሉ፡፡

የውጭ ዜግነት ባላቸው ኢትዮጵያውያን የተያዙ አክሲዮኖች ሽያጭ ጉዳይ ግን አሁንም አነጋጋሪ መሆኑ አልቀረም፡፡ ይህም አክሲዮናቸው የተሸጠባቸው ትውልደ ኢትዮጵያውያን እንደ ሕገወጥ የታዩት ኢትዮጵያዊ ሆነው የገዙትን አክሲዮን ዜግነት ሲቀይሩ ባለመመለሳቸው ነው፡፡ ወደፊትም ቢሆን ግን 140 ሺሕ የሚገመቱ ባለአክሲዮኖች ያላቸው የፋይናንስ ተቋማት ነገና ከነገ ወዲያ ሌሎች ዜግነታቸውን ሊቀይሩ የሚችሉ ባለአክሲዮኖች እንደሚኖሩዋቸው ስለሚታመን፣ ይህንን ሥጋት ለመቀነስ አሁንም ግልጽ ሕግ ሊቀመጥ እንደሚገባ የሚያመለክቱ አሉ፡፡ የአሁኑ ብዥታ የተፈጠረውም ዜግነት ከቀየሩ በኋላ የሚኖረው የሕግ አፈጻጸም ግልጽ ስላልሆነ ነው፡፡ በመንግሥት በኩል ግን ኢትዮጵያዊ ሆኖ ያገኘው መብት ዜግነቱን ሲቀይር መመለስ አለበት የሚል ነው፡፡

ብሔራዊ ባንክ የውጭ ዜግነት ያላቸው ትውልደ ኢትዮጵያውያን አክሲዮን ዋናው አክሲዮናቸውና የትርፍ ድርሻቸው ተመልሶላቸው ከባለቤትነታቸው እንዲሰረዙ እንዲሁም ይዘው የቆዩት አክሲዮን ደግሞ በግልጽ ጨረታ እንዲሸጥ ሲወሰን፣ ኢትዮጵያዊ ሆነው ባለአክሲዮን መሆናቸውን ግንዛቤ ውስጥ ማስገባት ነበረበት፡፡ አሁንም በእነዚህ ባለአክሲዮኖች ተይዘው የነበሩት አክሲዮኖች እንዲህ ባለው መንገድ መሸጥ አልነበረባቸውም የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡

ይህ መመርያ ከመውጣቱ በፊት ግን በባንኮችና በብሔራዊ ባንክ መካከል ሰፊ ውይይት  ተደርጎበት የነበረ ሲሆን፣ እነዚህ የውጭ ዜግነት አላቸው የተባሉ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ይዘውት ነበር የተባለውን አክሲዮን በጨረታ ከመሸጥ ባለአሲዮኖቹ ጥቅም እንዲያገኙበት ቢደረግ የሚል ሐሳብ ቀርቦ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቷል፡፡

አንዳንድ ወገኖችም እነዚህ አክሲዮናቸው ለጨረታ የወጣባቸው ግለሰቦችና ድርጀቶች በአብዛኛው የአክሲዮን ባለቤት የሆኑት ዜግነት ከመቀየራቸው በፊት እንደሆነ ስለሚታመን፣ ኢትዮጵያዊ ሆነው ያፈሩት ንብረት በዚህ መንገድ መተላለፍ አልነበረበትም ይላሉ፡፡

ዜጎች በአንድ አጋጣሚ ያፈሩትን ሀብት ያለ ምንም ጥቅም ማጣት አግባብ ስላልሆነ የቱንም ያህል ሕግ ተላልፈዋል ቢባል ቢያንስ በጊዜ ገደብ አክሲዮናቸውን ወደ ኢትዮጵያውያን እንዲያዛውሩ ዕድል ማግኘት ነበረባቸው ሲሉ ይከራከራሉ፡፡ ከባለአክሲዮንነታቸው ይሰረዙ ከተባለም አክሲዮኖቻቸውን ራሳቸው በመሸጥ ተጠቃሚ ሊሆኑ ይገባ እንደነበር ያመለክታሉ፡፡ አሁን እንደ መከራከሪያ የሚነሳውም ንብረቱን ማፍራት የጀመሩት ኢትዮጵያዊ ሆነው ነው በሚል ነው፡፡

ከአንዳንድ ባንኮች የተገኙ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ አንዳንድ ባለአክሲዮኖች አክሲዮኖቻቸውን ያላግባብ ሽጣችሁብናል የሚል ይዘት ያለው ክስ ባንኮቹ ላይ እያቀረቡ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

ከሰሞኑ የአክሲዮኖች ሽያጭ ጋር ተያይዞ የታየው በውጭ ዜግነት የተያዙ ናቸው የተባሉት አክሲዮኖች የግለሰቦች ብቻ ያለመሆናቸውንና ድርጅቶችም የሚገኙበት መሆኑ ነው፡፡ ሰርተፍኬታቸውን ያልመሰሉ ባለአክሲዮኖች ማንነት እንዲነገር በሚያዘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ መመርያ መሠረት፣ ቀርበው ሰርተፍኬታቸውን ያልመለሱና በይፋ ማስታወቂያ አክሲዮኖቻቸው የተሰረዘባቸው  ድርጅቶች ውስጥ አንዳንዶቹ በኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ ቢዝነስ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ድርጀቶች ናቸው፡፡

ከተለያዩ ባንኮችና ኢንሹራንሶች ከተሰበሰበው መረጃ የባንክና የኢንሹራንስ ኩባንያ ባለአክሲዮን ነበሩ ከተባሉት ኩባንያዎች ውስጥ እንዳለና ቤተሰቡ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ታፍ ኦይል፣ ኮኔልን ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበርና ሜሎስ ኢንጂነሪንግ የተባሉ ይገኙበታል፡፡ እነዚህ ኩባንያዎች አክሲዮናቸው ተሰርዞ ለሽያጭ የቀረበው በኩባንያዎቹ ውስጥ የውጭ ዜግነት ያላቸው ግለሰቦች በመኖራቸው ነው፡፡

በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታትም ቀሪዎቹ ባንክና ኢንሹራንስ ኩባንያዎች በውጭ ዜጎች የተያዙ አክሲዮኖቹን ሽያጭ ያካሂዳሉ፡፡ በርካታ ባለአክሲዮኖች ነበሩባቸው ከተባሉት ውስጥ ንብ ባንክ አንዱ ሲሆን፣ 221 የውጭ ዜግነት ባላቸው ባለአክሲዮኖች የተያዙና ከ63 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን አክሲዮኖች ለጨረታ አቅርቧል፡፡

በቅርቡ ከተቋቋሙ ባንኮች ውስጥ እናት ባንክ 158 የውጭ ዜግነት ባላቸው ባለአክሲዮኖች ሲኖሩት፣ ዓባይ ባንክም በ31 የውጭ ዜግነት ባላቸው ግለሰቦችና ድርጅቶች የተያዙ አክሲዮኖች ለሽያጭ አቅርቧል፡፡ ኦሮሚያ የኅብረት ሥራ ባንክ የ30 የውጭ ዜግነት ያላቸው ባለአክሲዮኖች አክሲዮኖችን ያጫርታል፡፡ ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ ደግሞ እያንዳንዳቸው አንድ መቶ ብር ዋጋ ያላቸውን 79,850 አክሲዮኖችን ይሸጣል፡፡

ከኢንሹራንስ ኩባንያዎች ውስጥም ግሎባል ኢንሹራንስ 13 የውጭ ዜግነት ባላቸው ተይዘው የነበሩና እያንዳንዳቸው 500 ብር ዋጋ ያላቸውን 19,919 አክሲዮኖችን ለጨረታ አቅርቧል፡፡ አንበሳ ኢንሹራንስ ደግሞ 1.41 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸውን 56,676 አክሲዮኖች ለጨረታ እንደሚያቀርብ አስታውቋል፡፡

ከኢንሹራንስ ኩባንያዎች ንብ ኢንሹራንስ በ235 የውጭ ዜግነት ያላቸው ባለአክሲዮኖች ማግኘቱን ጠቅሷል፡፡ እነዚህ ባለአክሲዮኖች 7.21 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው 14,421 አክሲዮኖችን ይሸጣል፡፡

 

Standard (Image)

ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የኢትዮጵያ ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን ምርጫና ጠቅላላ ጉባዔ አገደ

$
0
0

  የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ እንዳይካሄድ እንቅፋት ነበሩ ከተባሉ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች መካከል አንዱ የሆነው፣ የአገር አቀፉ ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ያካሄደው ጠቅላላ ጉባዔና የአመራሮች ምርጫ ተሰርዞ አዲስ ምርጫ እንዲካሄድ ተወሰነ፡፡  

የዘርፍ ምክር ቤቱ ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ እንዲታገድና አዲስ ምርጫና ጠቅላላ ጉባዔ እንዲካሄድ የተወሰነው፣ የዘርፍ ምክር ቤቶችን ጉዳይ በቀጥታ ከሚመለከተውና ጉዳዩን ሲያጣራ በቆየው የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ነው፡፡

ሰኞ የካቲት 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ከኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የተጻፈው ደብዳቤ እንደሚያመለክተው፣ አገር አቀፉ የኢትዮጵያ ዘርፍ ምክር ቤት ያካሄደውን ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ ያገደው የምርጫ ሒደቱ ሕጋዊ ጥሰቶች ያሉበት መሆኑ በመረጋገጡ ነው፡፡ በተለይ ከዘርፍ ምክር ቤቱ መተዳደሪያ ደንብ ውጭ ከሁለት የምርጫ ዘመን በላይ በተደጋጋሚ የተመረጡ ግለሰቦች መኖራቸው ምርጫውን የሚያስደግም በመሆኑ፣ አዳዲስ አመራሮችን ለመምረጥ ድጋሚ ጠቅላላ ጉባዔ እንዲጠራ ሊወሰን ችሏል፡፡ በተለያዩ ደረጃዎች የተዋቀሩ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶችን ወቅታዊ ችግር በተመለከተ ንግድ ሚኒስቴር ለመጀመሪያ ጊዜ ማክሰኞ የካቲት 28 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ የዘርፍ ምክር ቤቱ ምርጫ ስለመታገዱ አረጋግጧል፡፡

ይኸው የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ደብዳቤ ላለፉት አሥር ዓመታት ዘርፍ ምክር ቤቱን በፕሬዚዳንትነት ሲያገለግሉ የቆዩትን አቶ ገብረ ሕይወት ገብረ እግዚአብሔርን ጨምሮ፣ አምስት የቦርድ አባላትን በስም በመጥቀስ ከመተዳደሪያ ደንባቸው ውጭ በተደጋጋሚ መመረጣቸው የሚያሳይ የሕግ ጥሰት መፈጸሙን የሚያመላክት ጭምር ነው  ተብሏል፡፡

በንግድ ሚኒስቴር የአክሲዮን ማኅበራትና የንግድና ዘርፍ ምክር ቤቶች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ኑረዲን መሐመድ በሰጡት ተጨማሪ ማብራሪያ፣ የኢትዮጵያ የዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የቀረበበትን አቤቱታ ይከታተል የነበረው የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ባደረገው ማጣራት የመጨረሻ ውሳኔውን ሰጥቷል ብለዋል፡፡ ዕርምጃው የተወሰደውም ከዘርፍ ምክር ቤቱ መተዳደሪያ ደንቡ ውጪ ከሁለት ጊዜ በላይ በምርጫ የተመረጡና ወደ አመራር የመጡ እንዳሉ በማረጋገጡ ነው ብለዋል፡፡ እንደ ዘርፍ ምክር ቤቱ ሁሉ ከታች ያሉ ምክር ቤቶች በአግባቡ ሳይወከሉ ወደ አመራር መጥተዋል ተብለው ቅሬታ በቀረበባቸው ንግድ ምክር ቤቶች ላይ ተመሳሳይ ዕርምጃ ተወስዷል ያሉት አቶ ኑረዲን፣ ከነዚህም ውስጥ በቀዳሚነት የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን ጠቅሰዋል፡፡ የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምርጫን በተመለከተ በተደረገ ማጣራት፣ የምርጫ ሕግንና የንግድ ምክር ቤቱን የምርጫ ደንብ ያልጠበቀ መሆኑን የአማራ ክልል ንግድ ኢንዱስትሪና ትራንስፖርት ቢሮ በማረጋገጡ፣ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ምርጫው እንዲደገም ከሦስት ሳምንታት በፊት ውሳኔ ስለመሰጠቱም አስታውሰዋል፡፡

እነዚህ እንቅስቃሴዎች የሚያሳዩት በተዋረድ ከታች ያሉ ምክር ቤቶች ምርጫ ያለመከናወኑ መሆኑን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሐዊ በሆነ አሠራር ያላለፉ መሆኑን ያሳያል ብለዋል፡፡ አሁን ግን በማጣራቱ ሥራ የተወሰነውን ውሳኔ ተከትሎ ምርጫዎቹ ከሥር ጀምሮ ይካሄዳሉ ተብሏል፡፡

ምርጫዎቹንም ለማካሄድ ንግድ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትና የክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮዎች በጋራ በመሆን የተዋረድ ምርጫዎችን እንዲያስፈጽሙ ውሳኔ ላይ መደረሱን የገለጹት አቶ ኑረዲን፣ ለዚህም አቅጣጫዎች ተቀምጠዋል ብለዋል፡፡

የሕግ ጥሰት ታይቶባቸዋል የተባሉት ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች ድጋሚ ምርጫ የሚያኬዱትም በንግድ ምክር ቤቶች መቋቋሚያ አዋጅና በንግድ ምክር ቤቶቹ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ይሆናል፡፡

ንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴሮች እንዲሁም የአማራ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ እንዲህ ያለው ውሳኔ ላይ የደረሱት ከየንግድ ምክር ቤቶቹ አባላት በተደጋጋሚ የቀረቡትን ቅሬታዎች በመመርመር ነው፡፡ ከየክልሉ በቀረቡ ቅሬታዎች ምክንያት የዋናው የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምርጫ ሊካሄድ አልቻለም ያሉት አቶ ኑረዲን፣ ጠቅላላ ጉባዔውና ምርጫው ታግዶ እንዲቆይ የተወሰነው በአዋጁ በግልጽ እንደተቀመጠው በተዋረድ ምርጫዎች ባለመደረጋቸው ነው ብለዋል፡፡ ከታች በወረዳ፣ በዞንና በከተማ የሚገኙ ምክር ቤቶች ፍትሐዊና አሳታፊ የሆኑ ምርጫዎች መካሄዳቸው ሲረጋገጥም የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምርጫ ይደረጋል ተብሏል፡፡ ከታች ያሉት በአግባቡ ምርጫቸውን ሳያካሂዱ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን ምርጫ ማካሄድ ስለማይቻል፣ ንግድ ምክር ቤት ጥር 30 ቀን 2009 ዓ.ም. ሊካሄድ የነበረውን ጉባዔና ምርጫ ንግድ ሚኒስቴር ማገዱን አስታውሰዋል፡፡

ንግድ ሚኒስቴር የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔው እንዳይካሄድ ምክንያት የሆኑትን ጉዳዮች በማጥራት ከ15 እስከ 30 ቀናት ባለው ጊዜ ውስጥ ጉባዔውን እንዲካሄድ የሚያደርግ መሆኑንም ንግድ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡

በአንዳንድ ወገኖች ንግድ ሚኒቴርም ሆነ የክልል ንግድ ቢሮዎች በንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች ጉዳይ ጣልቃ መግባት የለባቸውም የሚለውን አስተያየት ትክክል አለመሆኑንም አስረድተዋል፡፡

የንግድ ምክር ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ 341/95 እነዚህን ማኅበራት የማደራጀት፣ የመከታተልና የመቆጣጠር ሥልጣን የተሰጠው ለንግድ ሚኒስቴር በመሆኑ፣ ሚኒስቴሩ ይህንን ሥልጣኑን መጠቀም ይቻላል ተብሏል፡፡

በ2003 ዓ.ም. ንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ለሁለት ሲከፈል በአስፈጻሚ አካላት ማቋቋሚያ አዋጅ ላይ ደግሞ የንግድ ዘርፉን በተመለከተ ንግድ ሚኒስቴር፣ የኢንዱስትሪ ዘርፉን ደግሞ ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር እንዲመራ መደረጉን ዳይሬክተሩ አስታውሰዋል፡፡

ስለዚህ ካለፈው ዓመት ሚያዝያ ወር ጀምሮ እስከ ነሐሴ 2009 ዓ.ም.  ድረስ አምስት የሚሆኑ የንግድና ዘርፍ ምክር ቤቶች አባላት በአዋጁ መሠረት ምርጫ አለማድረጋቸውንና በተመዳደሪያ ደንባቸው መሠረት ሕጉን ሳይጠብቁ ምርጫዎች እየተካሄዱ ያለመሆኑን የሚገልጹ አቤቱታዎች የቀረቡትም በሕግ መሠረት የሚያገባው ንግድ ሚኒስቴር በመሆኑ ነው ተብሏል፡፡

ቅሬታ የቀረበባቸውም የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት፣ የአዲስ አበባ ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት፣ የትግራይ ክልል ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት፣ የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት፣ የደቡብ ንግድ ምክር ቤት ምርጫዎች እንደሆኑ ተጠቅሷል፡፡ የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትና የኢትዮጵያ ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ሌላ በቀሪዎቹ ላይ ተመሳሳይ መረጃ እየተሰበሰበ ስለመሆኑም ከገለጻው ለመረዳት ተችሏል፡፡

የአገሪቱ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች አሁን ያሉበት አቋም በርካታ ችግሮች የሚታይባቸውም ነው ተብሏል፡፡ ችግሮቹን ለመፍታት ግን ንግድ ሚኒስቴር አልዘገየም ወይ?  የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው አቶ ኑረዲን፣ ንግድ ሚኒስቴር እንዲህ ያሉ ጉዳዮችን መከታተል የጀመረው በሰኔ ወር 2007 ዓ.ም. ነው ብለዋል፡፡ ከዚያ በፊት ንግድ ሚኒስቴር ሲሠራ የነበረው ምርጫዎች ሲደረጉ መካሄዳቸውን፤ ከ2003 ወዲህ ደግሞ የጋራ መድረኩን የመምራት ሥራ ብቻ ነበር፡፡

አሁን ግን ባለፉት ሁለት ወራት የምናያቸው ነገሮች ንግድና ዘርፍ ምክር ቤቶች ከማቋቋሚያ አዋጁና ከራሳቸውም ደንብ የወጡ መሆናቸውን ነው ብለዋል፡፡ ስለዚህ በዚህ ጉዳይ ንግድ ሚኒስቴር የመጨረሻ ውሳኔ እየሰጠ ነው ያሉት አቶ ኑረዲን፣ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው በመሆኑም ምርጫ እንዲራዘም ጭምር ውሳኔ እስከመስጠት ደርሰዋል ብለዋል፡፡ ለውሳኔው መዘግየታቸውን ግን አምነዋል፡፡

የንግድ ኅብረተሰቡን የሚወክሉ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች አሉባቸው የተባሉትን ችግሮች ለመፈተሽ በማጣራት ሥራው ላይ ብዙ ችግሮች እንደገጠሟቸው የገለጹት አቶ ኑረዲን፣ ይህንን ችግር ለመቅረፍ ግን ንግድ ሚኒስቴር አስፈላጊውን ዕርምጃ ሁሉ እንደሚወስድና በትክክል ምርጫዎች እንዲካሄዱ ያደርጋል ብለዋል፡፡

በአንዳንድ ንግድ ምክር ቤቶች ያሉ አመራሮች ዕውን  ትክክለኛ ነጋዴዎች ናቸው ወይስ አይደሉም? የሚለው ጉዳይ የችግሩ ዋና ምንጭ መሆኑን በመጥቀስም፣ በንግድ ምክር ቤቶች አደረጃጀቶች ላይ ያሉ ክፍተቶችን ለመድፈን የሚያስችሉ ሥራዎች ላይ ትኩረት እንደሚደረግም በመግለጫቸው ገልጸዋል፡፡ አንዳንድ ንግድ ምክር ቤቶች አሉን የሚሏቸው አባላት ላይም የሚታዩ ችግሮች መኖራቸውን በማረጋገጥ፣ ከዚህ በኋላ አደረጃጀታቸው እንዲስተካከል ይደረጋል ብለዋል፡፡ አሁን ግን ምክር ቤቶች ላሉባቸው ችግሮች አንዱ የንግድ ምክር ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ መሆኑ ግንዛቤ ተወስዷል፡፡

ስለዚህ ይህንን አዋጅ ለማሻሻል የመጀመሪያው የማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጅቷል፡፡ በቅርቡም ውይይት ተደርጎበት እንዲፀድቅ ይደረጋል፡፡ ይህም በተደጋጋሚ የሚፈጠሩ ችግሮችን ይፈታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በአማራ ንግድ ኢንዱስትሪና ትራንስፖርት ቢሮ ዕገዳ የተጣለበት የአማራ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት አባላት በተሰጣቸው ጊዜ ገደብ ምርጫቸውን ለማካሄድ አልቻሉም፡፡

የተሰጠው የጊዜ ገደብ አንድ ሳምንት የቀረው ቢሆንም፣ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ አለመደረጉ ታውቋል፡፡ እንደውም በአቶ ጌታቸው አየነው የሚመራው  ቦርድ ቢሮው ይደገም ያለውን ትዕዛዝ በመቃወም ላይ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

ይህ ደግሞ የክልሉን ምርጫ በተሰጠው የጊዜ ገደብ እንዳይካሄድ እንቅፋት ሆኗል እየተባለ ነው፡፡ የንግድ ሚኒስቴር ግን በሕጉ መሠረት በክልሉ ንግድ ቢሮ በኩል ምርጫው በአጭር ጊዜ እንዲካሄድ ይደረጋል ብሏል፡፡ ካልሆነም በተሰጠው ሥልጣን መሠረት የምዝገባ ሰርተፍኬቱን እስከመሰረዝ የሚደርስ ዕርምጃ ሊወሰድ ይችላል ተብሏል፡፡

አሁን በተሰጠው ውሳኔ መሠረት ግን የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትና የክልሉ ንግድ ቢሮ ከንግድ ሚኒስቴር ጋር በመሆን ምርጫውን ለማስፈጸም ይሠራሉ ተብሏል፡፡

 

Standard (Image)

የአንድ ኪሎ ቲማቲም ዋጋ 40 ብር ደርሷል

$
0
0

ከሁለት ሳምንታት በፊት በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች ከስምንት እስከ 12 ብር ሲሸጥ የነበረው አንድ ኪሎ ቲማቲም ሰሞኑን ከ32 እስከ 40 ብር እየተሸጠ ነው፡፡  ለአንድ ኪሎ ቲማቲም የዚህን ያህል ዋጋ መሰጠቱ የተለያዩ ምክንያቶች እንዳሉት ቢገለጽም፣ የዋጋው መወደድ ጊዜያዊ እንደሆነ እየተገለጸም ነው፡፡

በአገሪቱ በከፍተኛ የቲማቲም አምራችነታቸው ከሚታወቁ አካባቢዎች አንዱ ከሆነው ከመቂ ባቱ የኅብረት ሥራ ማኅበራት ዩኒየን የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ ሰሞኑን በከፍተኛ ደረጃ የቲማቲም ዋጋ ሊጨምር የቻለው የምርት እጥረት በመፈጠሩ ነው፡፡

150 የኅብረት ሥራ ማኅበራትን የያዘው የመቂ ባቱ ዩኒየን ከፍተኛ የቲማቲም አምራቾች የሚገኙበት ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ከአካባቢው መቅረብ ያለበትን ያህል ቲማቲም ለማቅረብ ያልተቻለው በቲማቲም በሽታና በአየር ንብረት ለውጥ ምርቱ ላይ ተፅዕኖ ስላሳደረ እንደሆነ ገልጿል፡፡

በመቂና በአካባቢው ባሉ አምራቾች የቲማቲም እርሻ ላይ ከአንድ ወር በፊት ቱታ አብሱሉታ የተባለው የቲማቲም በሽታ ያስከተለው ጥፋት ምርቱን ቀንሶታል፡፡ ከበሽታው ከተረፈው ምርትም የተወሰነው ከጥቂት ሳምንታት በፊት በተፈጠረ ውርጭ ምክንያት፣ በቂ ምርት ለገበያ ባለመቅረቡ የተፈጠረ ችግር ስለመሆኑም አስረድተዋል፡፡

ከሁለት ሳምንት በፊት በመቂና አካባቢው ያሉ አምራቾች በጅምላ ዋጋ አንዱን ኪሎ ቲማቲም አራት ብር ድረስ ይሸጡ እንደነበር የሚያስታውሱት የዩኒየኑ ኃላፊዎች፣ አሁን ግን እጥረቱ የጅምላ መሸጫው ዋጋን ሳይቀር ከ25 ብር እስከ 30 ብር ሰቅሎታል፡፡ ቲማቲም ዋጋ በዚህን ያህል ዋጋ የተሸጠበት ጊዜ እንዳልነበርም ገልጸዋል፡፡ ዩኒየኑ እንደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ ላሉ ትላልቅ ተቋማት በየዕለቱ ለማቅረብ የተዋዋለውን ቲማቲም አሁን ባለው የገበያ ዋጋ እየገዛ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡

ይህ ችግር ግን ጊዜያዊ መሆኑን የሚጠቁሙት የዩኒየኑ የሥራ ኃላፊዎች፣ አዲስ የሚደርሰው የቲማቲም ምርት በ15 ቀን ውስጥ ስለሚወጣ ዋጋው ይወርዳል ተብሏል፡፡

ሆኖም ግን ከመቂ አካባቢ ውጭ ያሉ የቲማቲም አምራቾች የገጠማቸው ችግር ባይኖርም፣ እየሸጡ ያሉበት ዋጋ አጋጣሚውን በመጠቀም ዋጋው እንዲሰቀል ምክንያት እንደሆነም እየተነገረ ነው፡፡ 

Standard (Image)

ንግድ ባንክ በውኃ ጉድጓድ ቁፋሮ ለሚሰማሩ ያለ ማስያዣ ብድር ለማቅረብ እየመከረበት ነው ተባለ

$
0
0

- ከፍተኛ ገንዘብ ወጥቶባቸው የተቆፈሩ ጉድጓዶች ብክነት እየታየባቸው መሆኑ ተገለጸ

 በከርሰ ምድር የውኃ ጉድጓድ ቁፋሮ ለተሰማሩ የአገር ውስጥ ባለሀብቶችና ባለሙያዎች ለማሽነሪዎች መግዣ የሚሆን ብድር ያለ ተጨማሪ ማስያዣ ሊያገኙ የሚችሉበትን አሠራር ለመተግበር የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር እየመከረ መሆኑ ተገለጸ፡፡

የከርሰ ምድር ውኃ ቁፋሮ ከፍተኛ ኢንቨስትመንት የሚጠይቅና የማሽኖች ዋጋ ውድ የሚባል በመሆኑ፣ የአገር ውስጥ ባለሀብቶች ውስን ናቸው ተብሏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ለማሽኖች መግዣ ከባንክ ብድር ለማግኘት ተበዳሪዎች ከማሽኖቻቸው ውጪ ተጨማሪ ማስያዣ ስለሚጠየቁ፣ ባለሙያዎችም ሆኑ ባለሀብቶች በዘርፉ ለመሰማራት ፈታኝ እንደሆንባቸው የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር ገልጿል፡፡

ባለፈው ሳምንት የካቲት 25 ቀን 2009 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት በአዳማ ባዘጋጀው የምክክር መድረክ ላይ የተሳተፉ የውኃ ጉድጓድ ቁፋሮ ባለሙያዎችና በዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶች፣ ከብድር አቅርቦት ጋር ያለባቸውን ችግር በሰፊው ገልጸዋል፡፡ የሚኒስቴሩ ኃላፊዎችም ማሽኖቻቸውን ብቻ በማስያዝ ያለ ተጨማሪ ማስያዣ ብድር ማግኘት የሚያስችል አሠራር እንዲዘረጋ በባንኮች ጉዳዩን እየተፈተሹ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

በሚኒስቴሩ የከርሰ ምድር ውኃ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተሩ አቶ ተስፋዬ ታደሰ በምክክር መድረኩ ላይ ብድርን አስመልክቶ ከጋዜጠኞች ለተነሳላቸው ጥያቄ፣ በዘርፉ ለመሰማራት ከፍተኛ የገንዘብ አቅም ስለሚጠይቅ ጥቂት ገንዘብ ያላቸው ባለሀብቶች እንጂ ሙያው ያላቸው አልሚዎች በብድር እንኳ በኢንቨስትመንቱ ውስጥ መሳተፍ አልቻሉም በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

‹‹በተለይ ባለሙያዎች ዕውቀታቸውን ጨምረው በኢንቨስትመንቱ (በከርሰ ምድር ውኃ ቁፋሮ) ለመሰማራት ትልቅ ፈተና አለባቸው፡፡ ምክንያቱም የመቆፈሪያ ማሽኖች ውድ ናቸው፤›› ያሉት አቶ ተስፋዬ፣ ለምሳሌ ከ500 እስከ 600 ሜትር ጉድጓድ መቆፈር የሚችል ማሽን ለመግዛት ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ ይጠይቃል ብለዋል፡፡

አክለውም ሥራው በቀላሉ ኪሳራ ሊያመጣ የሚችል ቢሆንም አትራፊም እንደሆነ የገለጹት ዳይሬክተሩ፣ በአንድ ጉድጓድ ከ60 እስከ 65 በመቶ ትርፍ ሊገኝበት እንደሚችል ገልጸዋል፡፡ አልፎ አልፎ ግን ማሽኑ በቁፋሮ ላይ እያለ ተደርምሶበት ሊጠፋም የሚችልበት አጋጣሚ መኖሩን በመጥቀስ፣ አትራፊነቱንና ሥጋቱን ለማመላከት ሞክረዋል፡፡

 በነዚህና መሰል ምክንያቶች ባንኮች ማሽኑን ብቻ ይዘው ብድር ለመስጠት አለመቻላቸውን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ነገር ግን ከጥቂት ጊዜ ወዲህ በተለይ ንግድ ባንክ ማሽኖችን ወይም ሊብሬዎችን ብቻ በመያዝ ብድር መስጠት የሚችልበትን መንገድ ማጥናት ጀምሯል፤›› ያሉት አቶ ተስፋዬ፣ የብድር አቅርቦቱን ለመጀመር ግን የመጨረሻ ውሳኔ ለመስጠት የዘገየ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል፡፡

በምክክር መድረኩ ላይ የተገኙ ባለሙያዎች እንደገለጹትም፣ በጥልቅ የከርሰ ምድር ውኃ ቁፋሮው የዓመታት ልምድና ዕውቀት ቢኖራቸውም፣ ከገንዘብ አቅም ውሱንነት ጋር በተያያዘ በራሳቸው አቅም ኢንቨስት አድርገው መሰማራት አለመቻላቸውን ነው፡፡ በአንፃሩ ዕውቀቱና ልምዱ ሳይኖራቸው ገንዘቡ ብቻ ስላላቸው በቁፋሮ ለተሰማሩ ባለሀብቶች ተቀጥረው ለመሥራት ብቻ መገደዳቸውን ተናግረዋል፡፡

ይህ ደግሞ በባለሙያዎችና በባለሀብቱ መካከል ችግሮችን ማጫሩ ስለማይቀር፣ ብዙውን ጊዜ በከፍተኛ ወጪ የሚቆፈረው ጉድጓድ የታሰበውን ያህል የአገልግሎት ጥራት እንደማይኖረው የተናገሩት ባለሙያዎች፣ አልያም የአገልግሎት ዕድሜው ላይ እንከን እየፈጠረ መሆኑን ጨምረው ጠቁመዋል፡፡

ከከርሰ ምድር ውኃ ጋር ተያይዞ ከሚነሱ ‹‹አንገብጋቢ›› ከተባሉ ችግሮች መካከል፣  በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ቀደም ብለው የተቆፈሩ ጉድጓዶች ከፍተኛ ወጪ ቢወጣባቸውም የሚፈልገውን ያህል አገልግሎት እየሰጡ አለመሆናቸው ይገኝበታል፡፡ እንዲሁም የውኃ ጉድጓዶች በአግባቡ አለመያዛቸውና በቂ መረጃና የመረጃ ቋት (ዳታ ቤዝ) የሌላቸው በመሆኑ፣ መልሶ ለመጠገንና ጥናት ለማካሄድ አስቸጋሪ አድርጎታልም ሲሉ ባለሙያዎቹ ይገልጻሉ፡፡ በአዳማው የምክክር መድረክ ላይ የመወያያ መነሻ ሐሳብ በማቅረብ በዘርፉ የዓመታት  ልምዳቸውን ካቀረቡ ባለሙያዎች አንዱ የሆኑት አቶ ሁሴን እንድሬ እንደገለጹት፣ ረዘም ላለ ጊዜ አገልግሎት ላይሰጡ ወይም የአገልግሎት ጊዜያቸው የሚጠበቀውን ያህል ሳይቆይ የተበላሹ የውኃ ጉድጓዶች በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ይገኛሉ፡፡ ሌሎችም ባለሙያዎች ከዚሁ ችግር ጋር ተያያዥነት ያላቸውን አስተያየት የሰጡ ሲሆን፣ መንግሥትና የሚመለከታቸው አካላት ትኩረት ሊሰጡት እንደሚገባ ሳያሳስቡ አላለፉም፡፡

Standard (Image)

ማስተርካርድ ፋውንዴሽን ኢትዮጵያን ጨምሮ የ11 አገሮች አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የፋይናንስ ድጋፍ አደረገ

$
0
0

 

 ማስተርካርድ ፋውንዴሽን በአፍሪካ 11 አገሮች ውስጥ ለሚገኙ 1.1 ሚሊዮን አርሶ አደሮች የምርታማነት ማሻሻያና የገበያ ትስስር መፍጠሪያ ፕሮግራሞችን በሚያራምዱ ተቋማት በኩል ድጋፍ ማደረጉን አስታወቀ፡፡

ፋውንዴሽኑ ለሪፖርተር በላከው መግለጫ ይፋ እንዳደረገው፣ በአፍሪካ አነስተኛ ገበሬዎችን ለመደገፍ ከሚንቀሳቀሱ፣ የፋይናንስ እንዲሁም የአግሪ ቢዝነስ አገልግሎቶችን ለገበሬዎች ለማዳረስ ከሚጥሩ ሦስት ድርጅቶች ጋር ፋውንዴሽኑ ባደረገው ስምምነት መሠረት የ38.3 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ እንደሚሰጥ አስታውቋል፡፡

ቡርኪናፋሶ፣ ኮትዲቯር፣ ኢትዮጵያ፣ ጋና፣ ማላዊ፣ ሞዛምቢክ፣ ሩዋንዳ፣ ሴኔጋል፣ ታንዛንያ፣ ኡጋንዳ እንዲሁም ዛምቢያን የሚያካትተው የማስተርካርድ ፋውንዴሽን ድጋፍ፣ ለአነስተኛ ገበሬዎች ልዩ ትኩረት በመስጠት ምርታማነታቸው እንዲጨምር በማገዝ ከእጅ ወደ አፍ የሆነውን አሠራራቸውን ለመቀየር እንዲቻል ለማድረግ ያለመ መሆኑን፣ የማስተርካርድ ፋውንዴሽን ፋይናንሺያል ኢንክሉዥን ዳይሬክተሯ አን ማይልስ አስታውቀዋል፡፡

ከአንድ ሚሊዮን በላይ ገበሬዎች የፋይናንስና ሌሎችም ድጋፎችን ማግኘት እንዲችሉ ለማድረግ በአፍሪካ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉ ሦስት ኩባንያዎች ጋር በመዋዋል 38 ሚሊዮን ዶላሩን እንዲያንቀሳቅሱ የተመረጡት ‹‹አፍሪካ አግሪካልቸር ዲቨሎፕመንት ካምፓኒ››፣ ‹‹ሩት ካፒታል›› እንዲሁም ‹‹አይሲሲሲኦ ኮኦፕሬሽን›› የተባሉ ሦስት ድርጅቶች ናቸው፡፡ እነዚህ ድርጅቶች ኢትዮጵያን ጨምሮ በ11ዱም አገሮች ውስጥ ለሚገኙ ገበሬዎች የሥልጠናና ጥራት ያላቸው የግብርና ግብዓቶችን ማቅረብ፣ የሞባይል ቴክኖሎጂዎችን መተግበር፣ ከ150 ሺሕ እስከ 300 ሺሕ ዶላር ካፒታል የሚጠይቁ ነገር ግን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖራቸው ለሚታመንባቸው የግብርና ነክ ቢዝነሶችን ከመደገፍ በተጨማሪ ሌሎችም ተግባራትን ማከናወን ይጠበቅባቸዋል፡፡

ማስተርካርድ ፋውንዴሽን እስካሁን በአፍሪካ ለሚገኙ አነስተኛ ገበሬዎች ከ300 ሚሊዮን ዶላር ያላነሰ ድጋፍ ለመስጠት የሚያስችለው ገንዘብ መመደቡን አስታውቆ፣ ከዚህ ውስጥ 175 ሚሊዮን ዳላሩ በገጠር አካባቢዎች እንዲሁም በግብርና መስክ ፋይናንስ የሚያቀርቡ ፕሮጀክቶችን ለመደገፍ የሚውል ድጋፍ እንደሆነ ገልጿል፡፡

ማስተርካርድ ፋውንዴሽን ከአሥር ዓመት በፊት በካናዳ የተቋቋመ የበጎ አድራጎት ተቋም ሲሆን፣ የፋይናንስ ተካታችነትን፣ የትህምርትና ሥልጠናን፣ የወጣቶች ኑሮ መሻሻልን መሠረት አድርጎ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ ዓለም አቀፍ ድርጅት ነው፡፡

ይኸው ተቋም ከጥቂት ወራት በፊት በኢትዮጵያ ከ12 ሺሕ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች በንብ ማነብ እንዲሁም በሐር የፈተል ክር የምርት ሥራ ላይ መሳተፍ የሚችሉበትን የሥልጠናና የቢዝነስ ድጋፍ ለመስጠት የሚያስችል የፋይናንስ ድጋፍ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

 

 

Standard (Image)

ዮቤክ ኩባንያ ከስዊዘርላንዱ ሞቨንፒክ ጋር የባለአስምት ኮከብ ሆቴል ስምምነት ፈጸመ

$
0
0

በስዊዘርላንድ ሆቴል በማስተዳደር አገልግሎት ከሚታወቁ ኩባንያዎች መካከል አንዱ የሆነው ሞቨንፒክ ሆቴልና ሪዞርት በኢትዮጵያ ከ1.2 ቢሊዮን ብር በላይ የሚፈጀውን ባለአምስት ኮከብ ሆቴል ለማስተዳደር ከዮቤክ ኢንተርፕራይዝ ጋር ስምምነት ተፈራረመ፡፡

ባለአምስት ኮከብ ሆቴሎችን በማስተዳደር የሚታወቀው ሞቨንፒክ ሆቴልና ሪዞርት ኩባንያ፣ በኢትዮጵያ የሆቴል ኢንዱስትሪ ውስጥ ተሳታፊ የሚያደርገውን ይህንን ስምምነት ከዮቤክ ኢንተርፕራይዝ ጋር ሐሙስ የካቲት 29 ቀን 2009 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ተፈራርሟል፡፡

አዲሱ ስቴዲየም እየተገነባ በሚገኝበት ገርጂ አካባቢ በዮቤክ እየተገነባ ያለውን ባለ 14 ፎቅ ሆቴል ለማስተዳደር በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚንቀሳቀሱ ስምንት ኩባንያዎች ሲያወዳደሩ ቆይተው፣ ሞቨንፒክን ሊመርጥ እንደቻለ ሁለቱን ኩባንያዎች በማደራደር ወደ ስምምነት ያመጣው የኦዚ ቢዝነስ ኤንድ ሆስፒታሊቲ ግሩፕ ኩባንያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ቁምነገር ተከተል ገልጸዋል፡፡

ሞቨንፒክ ሆቴል ዋና መቀመጫውን በስዊዘርላንድ በማድረግ በተለያዩ የዓለም ከተሞች የሚገኙ ሆቴሎችን በጋራ የማስተዳደር ስምምነት መሠረት እንደሚያንቀሳቅስ የሚታወቅ በመሆኑ እንደተመረጠ ተገልጿል፡፡ ሞቨንፒክ በዓለም አቀፉ የሆቴል ኢንዱስትሪ ውስጥ በተለይም ባለአምስት ኮከብ ደረጃ ባላቸውና ለላይኛው ወይም ውድ በሚባለው የሆቴል ደረጃ መሠረት አገልግሎቶችን በማቅረብ ትልቅ ስም ካተረፉ የሆቴል ብራንዶች መካከል አንዱ እንደሆነም ተነግሯል፡፡

የዮቤክ ኢንተርፕራይዝ መሥራችና ፕሬዚዳንት አቶ ብርሃኔ ግደይ እንደገለጹት፣ ኩባንያቸው ሞቨንፒክን የመረጠው መልካም ስምና ዝናው ከመመልከት ባሻገር በሆቴል አስተዳደር ሥራ መስክ ያላቸውን መርኅ እንዲሁም ዝርዝር የሥራ አመራር ልምዶችን የሚገልጹ መረጃዎችን በማጥናት ነው፡፡ በተለያዩ ከተሞች የሚገኙ የሞቨንፒክ ሆቴሎችን በአካል በመጎብኘት ጭምር ምዘና ማድረጋቸውን የገለጹት አቶ ብርሃኔ፣ የሞቨንፒክ ብራንድ ለሆቴላቸው ተመራጭ ሆኖ እንዳገኙት ገልጸዋል፡፡

ሆቴሉ 252 የተለያዩ ደረጃ ያላቸው የእንግዳ ክፍሎች የሚኖሩት ሲሆን፣ ከፕሬዚደንሻል እስከ ስታንዳርድ ክፍሎችን ያካተተ ዘመናዊ ሆቴል እንደሆነም ተገልጿል፡፡ ከመንታ ክፍሎች ባሻገር ሦስት የምግብ አዳራሾች፣ አንድ የሙሉ ጊዜ ምግብ ቤትንም ያካትታል፡፡ ሁለት የጣልያንና የእስያ ምግብ ቤቶች፣ ሦስት የመጠጥ አገልግሎት መስጫ ባሮች፣ 1,600 ሰው መያዝ የሚችል የስብሰባ አዳራሽና ስድስት የተለያዩ ስፋት ያላቸው የስብሰባ አዳራሾች እንደሚያካትትም ተጠቅሷል፡፡ 1,350 ካሬ ሜትር ስፋት ያለውና በወር እስከ 300 ተገልጋዮችን ማስተናገድ የሚችል የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማካሄጃ ጂም በሆቴሉ ግንባታ ውስጥ ተካቷል፡፡

ከ140 በላይ መኪኖችን የሚያስተናግድ ማቆሚያ የያዘ ስለመሆኑም አቶ ብርሃኔ ተናግረዋል፡፡ የሆቴሉ ሕንፃ ግንባታ በአሁኑ ወቅት 60 በመቶ የተጠናቀቀ ሲሆን፣ ቀሪውን የፊኒሺንግና አጠቃላይ የመገልገያ መሣሪያዎች የገጠማ ሥራ በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ውስጥ ተሟልተው ሆቴሉ በ2011 ዓ.ም. አገልግሎት እንደሚጀምር ገልጸዋል፡፡ ሆቴሉ ለ700 ቋሚና 450 ጊዜያዊ ሠራተኞች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥርም ይጠበቃል፡፡

ዩቤክ በአዲስ አበባ በዓለም አቀፍ ደረጃ ይሠራል ተብሎ ከተጠበቀው ሆቴል በተጨማሪ በመቐለ ከ160 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የሚጠይቅ ባለአራት ኮከብ ሆቴል ግንባታ በማጠናቀቅ ላይ ነው፡፡ ዮቤክ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የተባለው የፒፒ ከረጢት፣ ኮንድዊት፣ ፒቪሲ ቧንቧና የኤሌክትሪክ ኬብሎች ማምረቻና ልዩ ልዩ የኤሌክትሪክ ዕቃዎች አስመጪና አከፋፋይ መሆኑን የኩባንያው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

በ1999 ዓ.ም. የተመሠረተው ዮቤክ፣ በ2004 ዓ.ም. ወደ ሪል ስቴት ልማት በመግባት በአዲስ አበባ ከተማ ለተለያዩ የንግድና የቢሮ አገልግሎት የሚውሉ ባለ 14 ፎቅ መንትያ ሕንፃዎችን በሰንጋተራ አካባቢ አስገንብቶ፣ ለአገልግሎት ማብቃቱም ይታወሳል፡፡  

ሞቨንፒክ ሆቴሎችና ሪዞርቶች ከፍተኛ ምክትል ፕሬዚዳንት አላን ኦዲዬ ስምምነቱን በፈረሙበት ወቅት እንደገለጹት፣ የሞቨንፒክን ብራንድ ሆቴል በኢትዮጵያ ለማስተዳደር የሚያስችላቸውን ስምምነት የፈረሙት ለመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡ ከኢትዮጵያ ባሻገር በሞሮኮ፣ በቱኒዝያ፣ በኬንያ፣ በናይጄሪያ እንዲሁም በኮትዲቯር ከዚህ ቀደም የሞቨንፒክ ብራንዶች መከፈታቸውን ምክትል ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል፡፡

በዓለም 35 አዳዲስ ሆቴሎችን በመክፈት ለማስተዳደር የሚጠባበቀው ሞቨንፒክ፣ በዓለም ላይ የሚያስተዳድራቸው ሆቴሎች ብዛት 83 እንደሆኑ ሲገልጽ፣ በመጪዎቹ ሦስት ዓመታት ውስጥም ከ100 በላይ እንደሚያደርሳቸው ይጠበቃል ተብሏል፡፡

 

Standard (Image)
Viewing all 720 articles
Browse latest View live